Saturday, 19 September 2015 09:32

በቡርኪናፋሶ መፈንቅለ መንግስት ተካሄደ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት መፈንቅለ መንግስቱን አውግዘው፣የታሰሩ ባለስልጣናት እንዲፈቱ ጠይቀዋል
   የቡርኪናፋሶ የቤተ-መንግስት ጠባቂዎች ከትናንት በስቲያ ምሽት በመዲናዋ ኡጋዱጉ ባደረጉት መፈንቅለ መንግስት፣በፕሬዚዳንት ሚሼል ካፋንዶ የሚመራውን የአገሪቱን የሽግግር መንግስት በማፍረስ፣ ጄኔራል ጊልበርት ዴንድሬን በፕሬዚዳንትነት መሾማቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የቤተመንግስቱ ጠባቂዎች ባለፈው ረቡዕ በተከናወነ የካቢኔ ስብሰባ ላይ የሽግግር መንግስቱን ፕሬዚዳንት ሚሼል ካፋንዶ እና ጠቅላይ ሚኒስትሩን አይዛክ ዚዳን በቁጥጥር ስር በማዋል ማሰራቸውንና በነጋታውም መፈንቅለ መንግስቱን ማድረጋቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡የአገሪቱን የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ጠባቂዎቹ በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር የሰዓት ዕላፊ አዋጅ በማውጣትና የአገሪቱ የየብስና የአየር ክልሎች ሙሉ ለሙሉ እንዲዘጉ በማድረግ ባከናወኑት በተኩስ የታገዘ መፈንቅለ መንግስት፣ የሽግግር መንግስቱን ጊዚያዊ መሪ ፕሬዝዳንት ሚሼል ካፋንዶን ከስልጣን አውርደዋል፡፡
አገሪቱን ለ27 አመታት ያህል የመሩት የቀድሞው ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬ፤ ባለፈው አመት ባጋጠማቸው የህዝብ ተቃውሞ ስልጣናቸውን መልቀቃቸውን ተከትሎ ስልጣኑን የተረከበውና በፕሬዝዳንት ሚሼል ካፋንዶ የሚመራው የአገሪቱ የሽግግር መንግስት በመጪው ጥቅምት ወር ይከናወናል ተብሎ በሚጠበቀው የአገሪቱ ምርጫ ለሚያሸንፈው አዲስ መንግስት ስልጣኑን ለማስረከብ አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ መፈንቅለ መንግስቱ ተካሂዶበታል፡፡የሽግግር መንግስቱ የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ብሌስ ኮምፓዎሬ ታማኞች እንደሆኑ የሚነገርላቸውን ፖለቲከኞች በመጪው ምርጫ እንዳይሳተፉ መከልከሉንና የፕሬዚዳንቱ ጠባቂ ሃይል እንዲበተን መገፋፋቱን የጠቆመው ዘገባው፣በዚህ የተቆጡ የፕሬዚዳንቱ ጠባቂዎች መፈንቅለ መንግስቱን ማካሄዳቸውን አመልክቷል፡፡ አገሪቱን በቅኝ ግዛት ታስተዳድር የነበረችዋ ፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ፍራንኮይስ ሆላንዴ በበኩላቸው፣ መፈንቅለ መንግስቱን አውግዘው በእስር ላይ የሚገኙት የሽግግር መንግስቱ ፕሬዚዳንት እና ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአስቸኳይ እንዲፈቱ ጠይቀዋል፡፡

Read 1654 times