Monday, 31 August 2015 08:53

በአዲስ አበባ: ሰበካ ጉባኤያት በአስተዳደር ሓላፊዎች መታገዳቸው አሳሳቢ ኾኗል

Written by 
Rate this item
(8 votes)

• በቅዱስ ዐማኑኤልና በአቡነ አረጋዊ አድባራት፤ አስተዳደሩና ሰበካ ጉባኤያት ተፋጠዋል
• ፓትርያርኩ የመሩበት ጥናታዊ ሪፖርት ለቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታ አለመቅረቡ አነጋጋሪ ኾኗል


    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በርካታ አድባራት፣ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በበላይነት ለመምራትና ለመቆጣጠር ሥልጣንና ተግባር ያላቸው የሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባኤ አባላት፣ በሙስናና ብልሹ አሠራር በሚታሙ የአስተዳደር ሓላፊዎች መታገዳቸው አደገኛ አዝማሚያ እየያዘ መምጣቱ ተገለጸ፡፡ ሀገረ ስብከቱም ተጣርተው በሚቀርቡለት ሪፖርቶች ላይ አፋጣኝ ውሳኔ አለመስጠቱ “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤” ይላሉ ምእመናኑ፡፡ባለፉት ሦስት ወራት ለአዲስ አድማስ የደረሱ ጥቆማዎች እንደሚያስረዱት፤ የሰበካ ጉባኤያቱ ምክትል ሊቃነ መናብርት፣ ከሓላፊነት ይታገዳሉ አልያም በአስተዳደር ተግባር የመሳተፍ ድርሻቸው ተዳክሞ ደመወዝና ሥራ ማስኬጃ በመፈረም ብቻ ተወስኗል፡፡ ከአስተዳደሩ ሓላፊዎች የተለየ ሐሳብ የሚያነሡ የማኅበረ ካህናት ተወካዮች፤ ከሥራና ከደመወዝ ይታገዳሉ፤ ከፈቃዳቸው ውጭ ወደ ሌሎች አድባራት ዝውውር ይጠየቅባቸዋል፤ የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራንና የንብረት አመዘጋገብን አጥብቀው የሚቆጣጠሩ የማኅበረ ምእመናን ተወካዮች ከአባልነት ከመታገዳቸውም በላይ “ለማበጣበጥ እየሠሩ ነው፤ አሸባሪዎች ናቸው” በሚል ለመንግሥታዊ አስተዳደርና የፍትሕ አካላት ክሥ ይቀርብባቸዋል ተብሏል፡፡
በደብረ ከዋክብት አቡነ አረጋዊና ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን፣ አስተዳዳሪው፤ የሰበካ ጉባኤውን ውሳኔ እንደማይተገብሩ የጠቆሙ ምዕመናን፤ በምክትል ሊቀ መንበሩ የማይታወቁ የባንክ ሂሳቦችን በደብሩ ስም እንደሚያንቀሳቅሱ፣ አግባብነት የሌለው የሠራተኞች ዕድገትና ዝውውር እንደሚፈፅሙ ተናግረዋል፡፡
አስተዳዳሪው ቀደም ሲል የቤተ ክርስቲያንን መሬት ለግል ጥቅም በማዋላቸው ከሓላፊነት ታግደው እንደነበር ያስታወሱት ምእመናኑ፤ ደብሩ ለሀገረ ስብከቱ መክፈል የሚገባውን የኻያ ፐርሰንት ፈሰስ ሳይከፍሉ በመቅረታቸው ለዕዳ እንደዳረጉት ይናገራሉ፡፡ የሰበካ ጉባኤው አባላት፣ በማኅበረ ካህናቱ ተቀባይነት እንዳይኖራቸው በተወላጅነት እንደሚከፋፍሉና ካህናቱን ከደመወዝና ከሥራ በማገድ ለችግር እንደሚያጋልጧቸው ምዕመናኑ ይገልፃሉ፡፡
የአለመግባባቱ መንሥኤ፣ የሰበካ ጉባኤው አባላት የደብሩን ገቢና ወጪ አጥብቀው በመቆጣጠራቸውና የፋይናንስ ሪፖርት፤ በመጠየቃቸው እንደኾነ የሚገልጸው የክፍለ ከተማው ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሪፖርት አባላቱ፣ ደመወዝ ፈርሞ ከማውጣት ውጭ በውሳኔ አሰጣጥ ረገድ በቃለ ዐዋዲው በተሰጣቸው ሥልጣንና ተግባር እየተሳተፉ እንዳልኾነ አረጋግጧል፡፡ የአስተዳዳሪውን አልታዘዝ ባይነት የሚገልጸው ሪፖርቱ፤ ለሀገረ ስብከቱ ማስተላለፉን ቢያውቁም ምንም ዐይነት ምላሽ አለመሰጠቱ ግራ እንዳጋባቸው - ምእመናኑ ይናገራሉ፡፡
በተመሳሳይ አኳኋን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በቅርቡ ባካሔደው የሕንጻ እና የመሬት ኪራይ ተመን ጥናታዊ ሪፖርት ከበድ ባለ ሙስና የተተቸው የደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል አስተዳደር፤ ከሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና ከንብረት ሽያጭ ጋር በተያያዘ ከምእመናኑ ጋር ፍጥጫ ውስጥ ገብቷል፡፡ በየካቲት 2007 የተመረጠው ሰበካ ጉባኤ፣ የደብሩን የአሠራር ክፍተቶች በመቅረፍ ገቢውን በተሻለ መልኩ ለመቆጣጠርና ለማሳደግ ቢንቀሳቀስም አንድ የካህናት ተወካይ ከሥራና ከደመወዝ፣ ኹለት የምእመናን ተወካዮች ደግሞ ከአባልነት መታገዳቸው ውዝግቡን እንዳካረረው ተጠቅሷል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብትና ንብረት ለመጠበቅ ሲባል ካህናትና ምእመናን የሥራ ሓላፊነታቸውንና የቤተ ክርስቲያን ልጅነት ግዴታቸውን ለመወጣት በሚያደርጉት ጥረት ለሚፈጠርባቸው ዕንቅፋት ሀገረ ስብከቱ ሓላፊነት እንደሚወስድ ቢገልጽም ልኡካኑ ችግሩን ለመፍታት ባለመቻላቸው “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤ ለሚደርሰው ማንኛውም ጥፋት ተጠያቂዎች አንኾንም” ሲሉ ምእመናኑ አሳስበዋል፡፡
በብሥራተ ገብርኤል፣ በካራ ቆሬ ፋኑኤል፣ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፣ በላፍቶ ቅዱስ ሚካኤል፣ በፉሪ ቅዱስ ገብርኤል፣ በደብረ ሲና እግዚአብሔር አብ፣ በሰሚት ቅ/ጊዮርጊስ፣ በሰሚት ኪዳነ ምሕረት፣ በሰሚት ቅ/ሩፋኤል፣ በጨፌ አያት ቅ/ገብርኤል፣ በአያት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ በፉሪ ቅ/ዑራኤል እና በሰሚት መድኃኔዓለም ከሰበካ ጉባኤ አባላት የሥራ ጊዜ መጠናቀቅ፣ የካህናትና ምእመናኑን ከአስተዳደሩ ጋር አለመግባባት ውዝግብ እንደፈጠረ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የሰበካ ጉባኤ አባላት በሥልጣናቸው አለመሥራት፣ የአስተዳደር ሓላፊዎች ብቃት ማነስ፣ ሙስና እና ብልሹ አሠራር እንዲኹም የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ መዳከም በዐበይት መንሥኤነት ተዘርዝረዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታውን እንዲሰጥበት ፓትርያርኩ የመሩበትና ሙሰኛ የአድባራት ሓላፊዎች ምዝበራ በሕግ አግባብ እንዲታይ የሚጠይቀው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጥናታዊ ሪፖርትና ውሳኔ በአጀንዳነት አለመቅረቡ አነጋጋሪ ሆኗል ተባለ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አስፈጻሚ አካል የኾነውና በፓትርያርኩ ሊቀመንበርነት የሚመራው ቋሚ ሲኖዶሱ፣ በዚኽ ሳምንት መደበኛ ስብሰባው ይኹንታውን እንደሚሰጥበት ቢጠበቅም፤ የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ የፓትርያርኩ ምሪት እንዳልደረሳቸው በመግለጻቸውና የተመራበት ሰነድም የትኛው አካል ጋር እንዳለ በስብሰባው ወቀት ባለመታወቁ በአጀንዳነት ሳይቀርብ መቅረቱን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ዘግይቶ በደረሰን ዜና፣ ጥናታዊ ሪፖርቱና የውሳኔው ቃለ ጉባኤ ትላንት ከቀትር በኋላ ለብፁዕ ዋና ጸሐፊ አሁነ ሉቃስ ዘግይቶ በመድረሱ በቀጣይ ሳምንት ማክሰኞ በአጀንዳነት ቀርቦ ይኹንታ እና የአፈጻጸም አቅጣጫ የሰጥበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡

Read 3987 times