Saturday, 04 July 2015 09:56

የመንበረ ፓትርያርክ ቅ/ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ “ለሕይወት የሚያሰጋ የአድማ እንቅስቃሴ እየተደረገብኝ ነው” አለ

Written by 
Rate this item
(7 votes)

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መቀመጫ የኾነችው የቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፥ ጥፋቶች ታርመው ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሰራር እንዳይሰፍን በሚሹ ጥቂት የአስተዳደር ሰራተኞች፣ በህይወት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር ከአድማ ያልተናነሰ እንቅስቃሴ እየተደረገበት መኾኑን አስታወቀ፡፡ የመልካም አስተዳደር ጅምሩን ከፍጻሜ ለማድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ የአስተዳደር ክፍሎች እገዛ እንዲያደርጉለትም ጠይቋል፡፡
ለብክነት፣ ለዘረፋ እና ለሙስና ከተመቻቸ አሰራር እንዲሁም በገዳሟ ቀደም ሲል ከመልካም አስተዳደር ዕጦት የተነሳ የተከሰቱ ጥፋቶችን ለማረም ልዩ ልዩ መመሪያዎችንና የውስጥ ደንብ ረቂቆችን ማዘጋጀቱን ሰበካ ጉባኤው ለሀገረ ስብከቱ የዋና ሥራ አስኪያጅ ጽ/ቤት ባቀረበው ሪፖርት ገልጿል፡፡ ይኹንና ለቁጥጥር የሚያመች ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበትን አሰራር ለማስቀጠልና ለማስፈጸም እንዳይቻል ጥቂት የአስተዳደር ሰራተኞች ማኅበረ ካህናቱን በመከፋፈል፣ “ከሰበካ ጉባኤው ጋር ተባብራችኋል” በሚል ከሥራና ከደመወዝ በማገድ፣ በማስጠንቀቂያዎች በማሸማቀቅ፣ መረጃዎችን በማዛባት የሚፈጥሩት ግጭት ኹኔታውን አስቸጋሪ አድርጎብኛል ብሏል፡፡
መመሪያዎቹ እና የውስጥ ደንቡ “ቀድሞ ሲዘርፉበት የነበረውን አካሄድ የሚያስቀር እና አለአግባብ የሚያካብቱትን ጥቅም የሚያስቆም ነው” ያለው ሰበካ ጉባኤው፤ ለህይወት አስጊ ባላቸው ተፅዕኖዎች ሳቢያ በገዳሟ ጽ/ቤት ተገኝቶ በሰላማዊ መንገድ ስራዎቹን ለማከናወንና ሐላፊነቱን ለመወጣት ከማይቻልበት ደረጃ መድረሱን በሪፖርቱ አስታውቋል፡፡  
እንደ ሰበካ ጉባኤው ገለጻ፥ ቃለ ዐዋዲውን መሰረት አደርጎ ለቤተ ክርስቲያን በሚበጅ መልኩ ያዘጋጃቸው የሰው ኃይል አስተዳደር፣ የፋይናንስ፣ የንብረት እና የግዥ መመሪያዎች በጽ/ቤቱ ልዩ ትርጉም እየተሰጣቸው በመደበኛ ስብሰባ ላይ እንኳን አስተያየት እንዳይሰነዘርባቸው  ዕንቅፋት ተፈጥሯል፤ ማኅበረ ካህናትና ሰራተኞች ገንዘብንና ንብረትን የሚቆጣጠር አካል ቢመርጡም፣ የቆጠራ ሥርዓትን አስመልክቶ ከወራት በፊት በሀገረ ስብከቱ የተላከው መመሪያ ለኮሚቴው ቀርቦ ወደ ተግባር ሳይተረጎም በቢሮ ተሸሽጎ እንደተቀመጠ ነው፤ የቆጠራ ደንቡንና መመሪያውን ከማስፈጸም ይልቅ ከመመሪያው የተነሳ ህገ ወጥ ጥቅም የቀረባቸውን ግለሰቦች በማነሣሣት ለተቃውሞ እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡ያለፉት ስድስት ዓመታት የገንዘብ እና ንብረት እንቅስቃሴ በገለልተኛ ኦዲተር እንዲመረመር በፓትርያርኩ ቢታዘዝም “ከቃለ ዐዋዲው ውጭ ነው” በማለት ሒደቱ በሒሳብ ክፍሉ እና በጽ/ቤቱ ተጓትቷል፤ ይልቁንም የሒሳብ ፍተሻ ሒደቱ እና የሰበካ ጉባኤው የተሻሻሉ አሰራሮች ትግበራ ከሚያስከትሉት ተጠያቂነት ለማምለጥ የአስተዳደር ሐላፊዎቹ፣ “ሰበካው እየረበሸን ነው፤ የደመወዝና ጥቅማ ጥቅሞች ዕድገት እንዳናደርግላችሁ ዕንቅፋት ሆኖብናል፤ ከእኛ ጎን ከቆማችሁ ቢሮ አካባቢ እንመድባችኋለን፤ ወዘተ…” በማለት ከማኅበረ ካህናቱ ጋር ማጋጨትና መከፋፈል ስራዬ ብለው ከመያዛቸውም በላይ በዓመት ፈቃድ ሰበብ ከቢሯቸው ይሸሻሉ፡፡
በግንቦት ወር መጨረሻ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ አስኪያጅ ጽ/ቤት የተላከው ይኸው የሰበካ ጉባኤው ሪፖርት፤ ከተደጋጋሚ ጥያቄ በኋላ በቁጥጥር ክፍሉና በሒሳብ ክፍሉ በቀረቡ የገዳሟ የፋይናንስ አቋም ማሳያ ሪፖርቶች ላይ የተካሔደው ንጽጽራዊ ግምገማ፤ ገዳሟ በ2006 ዓ.ም ከየካቲት እስከ ነሐሴ ባሉት ሰባት ወራት ብቻ ከብር 1.5 ሚሊዮን በላይ ተመዝብራለች፤ በዚህ ከፍተኛ የገንዘብ ጉድለት እንቅስቃሴ ሂሳብ ሹሙ፣ ገንዘብ ያዡ፣ ፀሐፊው፣ ቁጥጥሩና የቀድሞው አስተዳዳሪ ተጠያቂዎች እንደሆኑ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም ከንዋያተ ቅድሳት ወርኀዊ ሽያጭ ጋር በተያያዘ ገዳሟ ከታህሣሥ ወር 2007 ዓ.ም በፊት ባሉት ጊዜያት በየወሩ በአማካይ ከብር 100ሺህ በላይ ስትመዘበር መቆየቷን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ለዚህም በዋናነት ተጠያቂው የንብረት ክፍል ሐላፊው እንደሆኑ ገልጿል፡፡
በገዳሟ በገንዘብ ዝውውርና በንብረት አጠባበቅ የሚታየው ከፍተኛ የአሠሰራር ድክመትና የሠራተኞች የአቅም ማነስ የመግባባት ችግር ከመፍጠሩም ባሻገር በልዩ ልዩ የአስተዳደር ክፍሎች ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን ሪፖርቱ አክሎ አብራርቷል፡፡
የገዳሟ ጸሐፊ መጋቤ ስብሐት ኃ/ጊዮርጊስ ዕዝራ በበኩላቸው፣ ሪፖርቱ እንዳልደረሳቸው ቢናገሩም የተጠቀሰውን የገንዘብ ጉድለት ጨምሮ የሪፖርቱ ይዘት “ሙሉ በሙሉ ውሸት ነው” በሚል አስተባብለዋል፤ ተጨማሪ ጥያቄዎችንም በስልክ ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡  

Read 4611 times