Saturday, 27 June 2015 08:26

እነዋሽንግተን ፖስት የኦባማን የኢትዮጵያ ጉብኝት አብጠለጠሉ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(8 votes)

“የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት ስለዲሞክራሲ የተሳሳተ መልዕክት ያስተላልፋል”
 
   የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በቀጣዩ ሐምሌ ወር ኢትዮጵያን ይጐበኛሉ መባሉን ተከትሎ ታላላቅ አለማቀፍ ሚዲያዎችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቸ ተቋማት ተቃውሞአቸውን እየገለፁ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ ፕሬዚዳንቱን እንዲመጡ የሚያደርጋቸው የአገራችን የውስጥ ስኬት ነው ሲል ተቃውሞውን አጣጥሎታል፡፡ የኦባማ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትን ርዕሰ ጉዳያቸው ካደረጉ የአሜሪካ ሚዲያዎች አንዱ የሆነው ዘ ዋሽንግተን ፖስት በርዕሰ አንቀፁ ባሰፈረው ተቃውሞ፤ “የኦባማ ኢትዮጵያን መጐብኘት
ስለዲሞክራሲ የተሳሳተ መልዕክት ያስተላልፋል” ብሏል፡፡ በእንግሊዝ ከፍተኛ ተሰሚነትና ተነባቢነት ያለው ዘ ጋርዲያንም ጉብኝቱን አስመልክቶ በርዕሰ አንቀፁ ባሰፈረው ሃተታ፤ የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት ዲሞክራሲያዊ ላልሆኑ ስርአቶች እውቅና መስጠት ነው ሲል ክፉኛ ተችቷል፡፡ ኦባማ ጋናን በጎበኙበት ወቅት፤ “መጀመሪያ የምንደግፈው የተጠናከረ ዲሞክራሲያዊ መንግስትን ነው” በሚል የተናገሩትን ዘንግተውታል ያለው ዋሽንግተን ፖስት፤ የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት ኢትዮጵያን የመሳሰሉ በሰብአዊ መብት ረገጣ ለሚታሙ ሃገራት እውቅናና ከለላ መስጠት ነው ሲል ተቃውሟል፡፡ “በቅርቡ ሠላማዊና ዲሞክራሲያዊ የመንግስት ሽግግር ያደረገችው ናይጄሪያን የመሳሰሉ በዲሞክራሲ ጐዳና ላይ እየተጓዙ ላሉ ሀገራት እውቅና መንፈግ ነው” ሲልም የታቀደውን የኢትዮጵያ ጉብኝት ጋዜጣው አብጠልጥሎታል፡፡ ጉብኝቱ ኢትዮጵያና አሜሪካ ያላቸውን የዘመናት ግንኙነት እንዲሁም ሃገሪቱ በቀጠናው ያላት የፀጥታ አስከባሪነት ሚናና ፈጣን የኢኮኖሚ እድገቷን ታሳቢ ያደረገ ነው መባሉን ያስታወሰው ዋሽንግተን ፖስት፤ የሀገሪቱ መንግስት በዚያው ልክ ነፃ ሚዲያ የማያበረታታ እንደውም ያሉትንም እያጠፋና የፖለቲካ ጫናዎች እያሳደረ የሚገኝ መሆኑን ጠቅሶ ጉብኝቱን ተቃውሟል፡፡
ባለፈው ዓመት ከሰኔ ወር ጀምሮ 34 ጋዜጠኞች ከሀገር እንዲሰደዱ መደረጋቸውን ጋዜጣው ጠቁሞ፣ ሃገሪቱ ጋዜጠኛ አሳሪ በመባል ከሚታወቁ የአለም ሀገራት በቀዳሚነት መሰለፏን ጠቅሶ የኦባማን ጉብኝት ተችቷል፡፡
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ዊንዲ ሸጋርማን በቅርቡ ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት “ኢትዮጵያ ዲሞክራሲዋን እያጠናከረች ነው፣ የምታከናውነው ምርጫም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ ነው” የሚል ምስክርነታቸውን በሰጡ ማግስት፣ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት የምርጫ ውጤቱን ከ99.6 በመቶ ወደ መቶ በመቶ ማሳደጉ፣ ዲሞክራሲውን ጥያቄ ውስጥ ከትቶታል ሲል ነቅቷል ዋሽንግተን ፖስት፡፡በዘንድሮ ምርጫ ተቃዋሚዎች እንግልትና እስራት እንደተፈፀመባቸው፣ አለማቀፍ ታዛቢዎች ምርጫውን እንዳይታዘቡ መከልከላቸውን፣ በምርጫው ማግስትም ሁለት የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ እጩ ተወዳዳሪ የነበሩ ፖለቲከኛ እንደተገደሉ የጠቀሰው ጋዜጣው፤ ሆኖም መንግስት ስለተገደሉት ሰዎች ኃላፊነት አልወሰደም ብሏል፡፡ የተረጋጋ፣ ሰላማዊና በህዝብ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ምርጫ ያካሄደችው ናይጄሪያ እያለች ፕሬዚዳንቱ ኢትዮጵያን መጎብኘታቸው ለለውጥ ላልተዘጋጀው የኢትዮጵያ መንግስትና ለአሳፋሪው
የምርጫ ውጤት እውቅና መስጠት ነው ያለው ዋሽንግተን ፖስት፤ ለአፍሪካውያንም ዲሞክራሲ ጠቃሚ አይደለም የሚል መልዕክት ያስተላልፋል ሲል ጉብኝቱን አጥብቆ ተቃውሟል፡፡ ታዋቂው የእንግሊዝ ጋዜጣ ዘ ጋርዲያን በበኩሉ፤ የኦባማ ኢትዮጵያን መጎብኘት ለጨቋኝ መንግስት ስጦታ ነው ሲል ፅፏል፡፡ “ሃገሪቱ በኢኮኖሚ እያደገች ቢሆንም በዜጎች ሰብአዊ መብት አያያዝና በፕሬስ ነፃነት እንዲሁም ዲሞክራሲያዊ ምርጫ በማካሄድ በኩል ተወቃሽ ነች፣ የዲሞክራሲ ተምሳሌት ልትሆንም አትችልም” ብሏል ጋዜጣው በርዕሰ አንቀፁ፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችም የፕሬዚዳንቱን የኢትዮጵያ
ጉብኝት አበክረው ተቃውመዋል፡፡ “የኢትዮጵያ ምርጫ በአፈና ስር ያለ የፖለቲካ ልምምድ ነው”
ያለው ‹ፍሪደም ሃውስ› የተሰኘ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ቡድን፤ የኦባማ ጉብኝት ለፖለቲካና ዲሞክራሲያዊ መብቶች መቀጨጭ አጋርነትን ማሳየት ነው ሲል በመግለጫው ተችቷል፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን፤ አንዳንድ ወገኖች የኦባማን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት እየተቃወሙ መሆኑን እንደሚያውቁ ጠቁመው፤ ፕሬዚዳንቱን እንዲመጡ የሚያደርገው የሀገራችን የውስጥ ስኬት ነው ብለዋል፡፡
“የኦባማ መምጣት ትልቅ ትርጉም አለው” ያሉት አቶ ሬድዋን፤ ፕሬዚዳንቱ ኢትዮጵያን ለመጐብኘት
የማቀዳቸው ሚስጥር የኢኮኖሚ እድገቱ እንዲሁም ሀገሪቱ ለሠላም እያበረከተች ያለው አስተዋጽኦ ስኬታማና አይነ ግቡ መሆኑ ነው ብለዋል፡፡ “በ112 አመታት የዲፕሎማሲ ታሪክ የአሜሪካ 44ኛው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ኢትዮጵያን መጐብኘት ትልቅ የገጽታ ግንባታ ይኖረዋል፤ ቤታችን መጽዳትና መሞቅ መጀመሩንም ያረጋግጣል” ብለዋል ሚኒስትሩ፡፡

Read 8424 times