ቴዎድሮስ፡- ዘፈኖቻችን ሁሉ “ልቤ፣ ልቤ” ነው የሚሉት፡፡ እርስዎ ሲሰሟቸው ምን ይላሉ?
ዶ/ር በላይ፡- ይህ ከሰው ልጅ መፈጠር ጀምሮ በዘልማድ የሚነገር፤ ነገር ግን ምንም ሳይንሳዊ መሰረት የሌለው አባባል ነው፡፡ ለልብ የተሰጠው ገለጻ በሙሉ ለአንጎል መሰጠት ያለበት ነው፡፡ ምክንያቱም አንጎል ነው የሚወደው፤ የሚጠላው፤ የሚያስበው፤ የሚራራው፤ የሚጨክነው፡፡ ልብ አይደለም፡፡
ቴዎድሮስ፡- በእግዚአብሔር መኖር ያምናሉ?
ዶ/ር በላይ፡- አዎን፡፡ ማን አለኝ?
ቴዎድሮስ፡- ማንም ስለሌለዎት ነው ወይስ የእርሱ በእርግጥም መኖር ነው እንዲያምኑ ያደረግዎት?
ዶ/ር በላይ፡- እግዚአብሔር አለ፡፡ በእግዚአብሔር አምናለሁ፡፡ ለዚህ ደግሞ ምንም ተጨማሪ መረጃ አያስፈልገኝም፡፡
ቴዎድሮስ፡- የአንድ ኃይማኖት ተከታይ መሆን በእግዚአብሔር ለማመን ይረዳዎታል?
ዶ/ር በላይ፡- በእግዚአብሔር ለማመን ምንም አያስፈልገኝም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም፤ ቁርዓንም አያስፈልጉኝም፡፡ እነዚህ መጻሕፍት ምን ያስተምሩኛል? ከግራ ወደ ቀኝ፤ ከታች ወደ ላይ፤ ከቀኝ ወደ ግራ ብታነባቸው … አንዳንድ ጊዜ እንደውም ጥሩ የፍልስፍና መጻሕፍት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ከእናቴ የሰማሁትን አንድ አባባል አለ፡፡
“ጽድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም
ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም”
ይህ አባባል ለእኔ ያለው ትርጉም ኃይማኖት ቢኖርም ባይኖርም፤ እግዚአብሔር ቢኖርም ባይኖርም፤ ጽድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም ከክፋት ደግነት መሻሉን የሚገልጽ ነው፡፡ እኔ ለእናቴ “እንኳንስ መጽሐፍ ቅዱስ ላነብ ይህም በዛብኝ” አልኳት፡፡ “ከክፋት ደግነት ይሻላል” ኡፍ! ይህ ቀለል አለኝ፡፡ ግን ደግሞ ሳስበው ይህም በዛብኝ፡፡ ቁርዓኑን ብታመጣው፤ መጽሐፍ ቅዱስን ብታገላብጠው የሚያስተምርህ ነገር ቢኖር ደግነትን ነው፡፡ ኃይማኖት ቢኖርህም ባይኖርህም ደግሞ ጥሩ ስሜት ይሰጥሀል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር በሀዋርያት አርፎ በእነሱ የተጻፈ ነው፡፡ እግዚአብሔር እነሱን ለማስተማር ይሆናል የተናገረው፡፡ እርሱ ኃያል ነው፤ በሁሉም ስፍራ ይገኛል፡፡ ሁሉንም በአንድ ጊዜ ማድረግ የሚችል ከሆነ ለእኔ የሚበቃኝን አዕምሮዬ ውስጥ ያስገባልኛል፡፡
ስለዚህ በእግዚአብሔር አምናለሁ፡፡ ብዙም ጣጣ አታብዛብኝ፡፡
ቴዎድሮስ፡- ጉዳዩ የደስታና እርካታ ብቻ ሳይሆን የነፍስም ነገር አለበት፡፡ አንድ ሰው ደግሞ ደግነት ካለው እምነት ባይኖረውም ችግር የለውም
(ከቴዎድሮስ ተ/አረጋይ “ፍልስምና” መፅሃፍ ላይ ከዶ/ር በላይ አበጋዝ ጋር ከተደረገው ቃለምልልስ የተቀነጨበ)