Saturday, 25 April 2015 10:48

የሰው ልጅ አውሬነትና የሰው ልጅ ቅዱስነት በሊቢያ!

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(25 votes)
  • ለክርስቲያን ወገኖቹ ሲል የተሰዋው ኢትዮጵያዊ ሙስሊም
  • አራት ኤርትራውያን “ሙስሊም ነን” ብለው ከISIS አመለጡ
  • በሊቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን መንግስት አላነጋገረንም አሉ    

    ባለፈው እሁድ ነበር በአረመኔው የአሸባሪ ቡድን (ISIS) 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች መቀላታቸውን የሰማነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ሦስቱ ጥገኝነት ተከልክለው ከእስራኤል የመጡ ኤርትራውያን ነበሩ ተብሏል፡፡ አንደኛው ደግሞ ኢትዮጵያዊ ሙስሊም ነው፡፡ ጀማል ራህማን ይባላል፡፡ ሶማሌላንድፕሬስ ድረገጽ እንደዘገበው፤አሸባሪው ቡድን ጀማል ሙስሊም በመሆኑ ለጊዜው አልፈለገውም ነበር፡፡ ሆኖም ቡድኑ የጀማልን ጓደኛ ጨምሮ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን መርጦ ሲወስድ አላስቻለውም፡፡ በፈቃደኝነት ተቀላቅሏቸው ሄደ፡፡ በኢትዮጵያውያኑ ላይ ግድያ እንዳይፈጽም የቻለውን ያህል ቢያደርግም አልተሳካለትም፡፡ በመጨረሻም ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ ተጠይቀው “አይሞከርም!”ካሉት ኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ጎን በISIS አሸባሪ ቡድን ተቀልቷል፡፡ ሶማሌላንድፕሬስ የሐረር ተወላጁን ጀማል ራህማንን የገለጸው፤ “ኢትዮጵያዊው ሙስሊም ሰማዕት!” በማለት ነው፡፡ (ከዚህ በላይ ቅድስና ከየት ይመጣል!?) በአንድ ቦታ ነው የሰው ልጅ አውሬነት እና የሰው ልጅ ቅድስና የተገለጠው። በአንድ በኩል አረመኔው ISIS፤ በሌላ በኩል ለክርስቲያን ወገኖቹ ሲል የተሰዋው ኢትዮጵያዊ ሙስሊም!
አሁንም ግን በሊቢያ የኢትዮጵውያን ስደተኞች መከራ አላበቃም፡፡ አሁንም አሸባሪው ቡድን በርካታ ኢትዮጵያውያንን መያዙ ተሰምቷል፡፡ በትሪፖሊ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ወደ አገራቸው መመለስ ቢፈልጉም ማን እንደሚወስዳቸውና የት እንደሚመዘገቡ እንደማያውቁ ጠቁመው እስካሁን ከመንግስት ወገን ያነጋገራቸው እንደሌለ ሰሞኑን ለቪኦኤ ገልጸዋል፡፡ በግብጽ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሙሃሙድ ድሪል ስልክ ላይ ደጋግመው ቢደውሉም እንደማይነሳ በምሬት ተናግረዋል- ስደተኞቹ፡፡ አንድ በጣም ተስፋ የቆረጠ ኢትዮጵያዊ፤“የኢትዮጵያ መንግስት የሚረዳን አይመስለኝም” ብሏል - ለቪኦኤ፡፡ ዜጎች እንዲህ በባዕድ አገር፤ “ከአሁን አሁን እያዝ ይሆን?” እያሉ ከሞት ጋር በተፋጠጡበት የጭንቀት ሰዓት መንግስት “አለሁላችሁ” ሊላቸው ይገባል፡፡ (ዜጎችን ከሞት ከመታደግ የላቀ ልማት የለም!)
በነገራችሁ ላይ በሊቢያ በከፍተኛ ስጋት ውስጥ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ብቻ አይደሉም፡፡ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ስደተኞች በጀልባ ወደ አውሮፓ ለመሻገር እየተጠባበቁ ሲሆን በአሸባሪው ቡድን ተይዘው  አሰቃቂ የሞት እርምጃ እንዳይወሰድባቸው በመፍራት በርካታ ስደተኞች በአንድ ጀልባ ላይ እየተሳፈሩ የባህር ሲሳይ በመሆን ላይ ናቸው፡፡ ባለፈው ቅዳሜ በሜዲትራኒያን ባህር በሰጠመችው ጀልባ ከ800 በላይ ስደተኞች ለሞት የተዳረጉ ሲሆን ከሟቾቹ መካከል ኤርትራውያን፣ ሶማሊያውያንና ኢትዮጵያውያን-ይገኙበታል ተብሏል፡፡ በቁጥር የሚበዙት ግን  ኤርትራውያን እንደሆኑ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ (ለእነሱም ዜጎቼ የት ገቡ የሚል መሪ ይስጣቸው!)
ወንድማማቾቹ ከ ISIS አመለጡ
የ19 ዓመቱ ሃቤን እና የ14 ዓመት ታዳጊ ወንድሙ ሳሙኤል፤ከኤርትራ ተሰደው ሊቢያ የገቡት የአውሮፓ አገራትን አልመው ነበር፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ግን በአይምሬው አሸባሪ ISIS እጅ ውስጥ ገቡ፡፡ ታጣቂዎቹ ሃይማኖታቸውን ሲጠይቋቸው፣ሙስሊም መሆናቸውን ተናገሩ፡፡ ክርስቲያን ነን ቢሉ የሚጠብቃቸውን ያውቃሉዋ፡፡  
“ክርስትያኖች ነን፤ ነገር ግን እምነታችንን መካድ ነበረብን፡፡ ያለበለዚያ ታጣቂዎቹ ይገድሉናል፡፡ ወይ በጥይት ይመቱናል አሊያም  ይቀሉናል” በማለት ሃቤን ለሜይልኦንላይን ድረገፅ አስረድቷል፡፡ ሃቤን እንደሚለው፤ጓደኞቹ ክርስቲያን በመሆናቸው በISIS ግድያ ተፈጽሞባቸዋል፡፡
“ጓደኞች ነበሩኝ - ኤርትራዊና ግብፃዊ - ክርስትያን መሆናቸውን በመናገራቸው ተገድለዋል”
እነ ሃቤን የጓደኞቻቸው መገደል ጥልቅ ሃዘን ውስጥ እንደሚከታቸው ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ነገር ግን እነሱም እንደማይቀርላቸው ያውቃሉ፡፡
“ክላሺንኮቭ የታጠቁ ሰዎች ይመጡና እምነትህን ይጠይቁሃል፡፡ ክርስትያን ከሆንክ ወስደው ይገድሉሃል፡፡ አንገትህን ይቀሉሃል ወይም በጥይት ጭንቅላትህን ይመቱሃል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ክርስትያኖችን እንደዚያ አድርገዋል” ብሏል - ሃቤን ለሜይልኦንላይን፡፡
ሃቤን እና ወንድሙ ህይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው ከኤርትራ ሊቢያ ድረስ የተጓዙት የነገን ብሩህ የአውሮፓ ህይወት አልመው ነው፡፡ ሁለቱ ታዳጊዎች አንገታቸው ላይ ያሰሩትን የእንጨት መስቀል ከልብሶች ስር ደብቀው ክርስቲያን መሆናቸው እንዳይታወቅ በማድረግ ከሞት ተርፈዋል፡፡ ሌሎች ኤርትራውያን ክርስትያኖች ደግሞ ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ መገደዳቸውን ለሜይልኦንላይን ተናግረዋል፡፡
የ18 ዓመቱ አማን ሲናገር፤ “አንገቴ ላይ የእንጨት መስቀል አስሬ ነበር፤ ለህይወቴ ስል ግን መጣል ነበረብኝ፡፡ ታጣቂዎቹ ክርስትያኖችን ፍለጋ ነበር የመጡት፡፡ አህዛብን እንገድላለን ሲሉ ከአንገቴ ላይ በጥሼ ጣልኩት” ብሏል፡፡
“አረብኛ እናገራለሁ፤ ስለዚህ ክርስትያን እንዳልሆንኩና የእነሱ እምነት ተከታይ እንደሆንኩ አስመስዬ ቀረብኩ፤ እነሱም አመኑኝ” ሲል ከቡድኑ አሰቃቂ ግድያ ያመለጠበትን ሁኔታ አስረድቷል፡፡
ሃቤን እና ታናሽ ወንድሙ ሳሙኤል እንዲሁም አማን እና ተስፋለም፤የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታዮች ሲሆኑ ከ15 ቀናት በፊት አስቸጋሪውን የሜዲትራንያን ባህር በጀልባ በማቋረጥ አውሮፓ ለመግባት ችለዋል፡፡ ባለፈው እሁድ በአሸባሪው ቡድን ISIS አንገታቸውን የተቀሉት ኢትዮጵያውያንም ባህር ተሻግረው አውሮፓ ለመግባት ሲጠባበቁ ነበር ተብሏል፡፡
 ለሟቾች ቤተሰቦችና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መጽናናትን እንመኛለን!!

Read 7657 times