Monday, 02 March 2015 08:58

ሩብ ሚሊዮን ብር መዝብሯል የተባለው በፖሊስ እየተፈለገ ነው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

ተቀጣሪ ላልሆኑ 56 ወዳጅ ዘመዶቹ ደሞዝ ይከፍል ነበረ

      በደቡብ ክልል በስልጤ ዞን፣ ስልጤ ወረዳ፣ ቤተሰቦቹን ጨምሮ 56 የቅርብ ዘመዶቹንና ወዳጆቹን የመንግስት ተቀጣሪ በማስመሰል የደሞዝ መክፈያ መዝገብ ላይ አስፍሮ በየወሩ ደሞዝ በመክፈል የወረዳውን ሩብ ሚሊዮን ብር መዝብሯል የተባለው ተጠርጣሪ በፖሊስ እየተፈለገ ነው፡፡
የወረዳው የፋይናንስ ግዢና ክፍያ ሠራተኛ የነበረው ቢኒያም አካሉ የተባለው ተጠርጣሪ አባቱን፣ እህት ወንድሞቹንና ባለቤቱን ጨምሮ የስጋ ዘመዶቹን ስም ከተለያዩ የወረዳው ሠራተኞች ስም ጋር ቀላቅሎ በመመዝገብ፣ ከጥቅምት 2007 ዓ.ም ጀምሮ ደሞዝ ሲከፍላቸው እንደነበር ፖሊስ ደርሶበታል፡፡
መጀመሪያ ሁለት ግለሰቦችን ከግብርና ባለሙያዎች ዝርዝር ጋር በመቀላቀል ደሞዝ እንዲከፈላቸው ያደረገ ሲሆን በየወሩ የሰው ቁጥር እየጨመረ ለ56 ሰዎች መንገድ በተመሳሳይ ደሞዝ ያስከፍላቸው እንደነበር የፖሊስ መረጃ ይጠቁማል፡፡
ተጠርጣሪው ገንዘቡን በዳሽን ባንክ ያስገባ እንደነበር የጠቆመው ፖሊስ፤ ሲደረስበት ገንዘቡን ከባንኩ አውጥቶ መሰወሩን ገልጿል፡፡ ተጠርጣሪው ለህገወጥ የደሞዝ ክፍያ ይጠቀምባቸው የነበሩ ሠነዶችን ፖሊስ ያገኘ ሲሆን ግለሰቡን ለመያዝ ፎቶግራፉ እንደተሰራጨ፣ ከሃገር እንዳይወጣ የእግድ ትዕዛዝ መተላለፉንና ጠንካራ ፍለጋ እየተከናወነ መሆኑን የወረዳው ፖሊስ አዛዥ ምክትል ኢንስፔክተር አብዱ አደም ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡  
የወረዳው ፖሊስ የተጠርጣሪውን ወላጆች ጨምሮ 10 በግብረአበርነት የተጠረጠሩ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር አውሎ ፍ/ቤት ያቀረበ ሲሆን ለምርመራ 10 ተጨማሪ ቀናት መጠየቁንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Read 2200 times