Monday, 02 March 2015 08:55

ለኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የአለም ባንክ ምላሽ እንዲሰጥ ተጠየቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

    በአለም ባንክ እና በሌሎች አለማቀፍ ተቋማት የገንዘብ ድጋፍ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚከናወኑ ፕሮጀክቶች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እየተፈጸሙ ነው በሚል የባንኩ የውስጥ መርማሪ ቡድን ያወጣውን ሪፖርት ባንኩ በትኩረት ተመልክቶ ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጠው ሂውማን ራይትስ ዎች ጠየቀ፡፡
ባንኩ በበኩሉ፤ መርማሪ ቡድኑ ባወጣው ሪፖርት ላይ የተጠቀሱ ለሰብአዊ መብት ጥሰቶች በር የሚከፍቱ በርካታ የአሰራር ችግሮች እንደሌሉበት ገልጾ፣ ጥናቱ እንደገና ሊከለስ ይገባል ብሏል፡፡ የአለም ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ የመርማሪ ቡድኑን ሪፖርት ለመገምገምና የማኔጅመንቱን ምላሽ ለማሰማት በትናንትናው ዕለት ስብሰባ አድርጓል፡፡
ሂውማን ራይትስ ዎች ለአለም ባንክ የአፍሪካ ምክትል ፕሬዚደንት በላከው ደብዳቤ እንዳለው፣ የባንኩ ገለልተኛ የተጠያቂነት ስልት መርማሪ ቡድን በጉዳዩ ዙሪያ ባደረገው ምርመራ በኢትዮጵያ በሚከናወኑ ፕሮጀክቶች ላይ ተግባራዊ የሚያደርገውን የራሱን ፖሊሲ እንደሚጥስ ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ቡድኑ ባለፈው ወር ባወጣው ሪፖርት፤ በአለም ባንክ ፕሮጀክቶችና በኢትዮጵያ መንግስት የመልሶ ማስፈር ፕሮግራም መካከል የአሰራር ግንኙነት እንዳለ ማረጋገጡንና ይህም የአለም ባንክ ለነባር ህዝቦች መብቶች መከበር የቆመውን የራሱን ፖሊሲ እየጣሰ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ እንደሆነ ማስታወቁንም አክሎ ገልጧል፡፡
መርማሪ ቡድኑ መሰረታዊ አገልግሎቶችን የማስፋፋት ዓላማ ያላቸውንና በአለም ባንክ፣ በእንግሊዝ መንግስት የአለማቀፍ ልማት ድርጅት፣ በአፍሪካ ልማት ባንክ እና በሌሎች ለጋሾች የገንዘብ ድጋፍ የሚደረግላቸውን ፕሮጀክቶች በተመለከተ ከጋምቤላ ክልል ስደተኞች የቀረበለትን ቅሬታ መነሻ በማድረግ ባደረገው ማጣራት፣ የአለም ባንክ በፕሮጀክቶቹ ውስጥ ለሚታዩ የሰብአዊ መብት ጥሰት አደጋዎች ይህ ነው የሚባል ትኩረት እንዳልሰጠ ማረጋገጡን የሂውማን ራይትስ ዎች አለማቀፍ የገንዘብ ተቋማት ከፍተኛ ተመራማሪ የሆኑት ጀሲካ ኢቫንስ ገልጸዋል፡፡
የአለም ባንክ በኢትዮጵያ የሚያከናውናቸውን ፕሮጀክቶች አካሄድ ማስተካከል የሚችልበት ዕድል አለ ያሉት ጀሲካ ኢቫንስ፣ ባንኩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሰለባ የሆኑ ስደተኞችን የመብቶቻቸው ተጠቃሚ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበትም ገልጸዋል፡
ኢትዮጵያ የሚሊኒየሙን የልማት ግቦች በማሳካት ረገድ አበረታች ውጤት ማስመዝገቧ፣ አገሪቱ ጠንካራ የኢኮኖሚ እና የአገር ውስጥ ገቢ እድገት እያሳየች መሆኗን ያመላክታል ያለው የእንግሊዝ መንግስት በበኩሉ፣ ይህም የአገሪቱን ፍላጎት ባገናዘበ መልኩ የሚሰጠውን እርዳታ ከመሰረታዊ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ስራ ፈጠራና ራስን የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች ለማዞር እንዳነሳሳው ከትናንት በስቲያ አስታውቋል፡፡ የእግሊዝ መንግስት የእርዳታ አቅጣጫ ለውጡ ለኢትዮጵያ በሚሰጠው የገንዘብ መጠን ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድርና በኢትዮጵያ ድህነትን ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ውስጥ አጋርነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል መግለጹን ተከትሎ፣ የኢትዮጵያ መንግስትም ለእንግሊዝ መንግስት ያለውን አድናቆት ገልጿል፡፡

Read 1712 times