Saturday, 21 February 2015 12:33

በስልጢ ለሳምንት የዘለቀው ቃጠሎ በደን ላይ ውድመት አደረሰ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(0 votes)

በደቡብ ክልል ስልጢ ዞን ስልጢ ወረዳ ውስጥ በተፈጥሮ ደን ላይ የእሳት ቃጠሎ ውድመት እየደረሰ መሆኑን ምንጮቻችን የጠቆሙ ሲሆን የወረዳው ግብርና ላይ በበኩሉ እሣቱ በቁጥጥር ስር መዋሉን ጠቅሶ የአደጋው መንስኤ በፖሊስ እየተጣራ ነው ብሏል፡፡
ከሳምንት በፊት የጀመረው የእሳት ቃጠሎ እስካለፈው ሐሙስ ድረስ አለመቆሙን የተናገሩት ምንጮች፤ ከወረዳው ዋና ከተማ ቂቢት በስተምዕራብ 5 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በዘቢዳር ሰንሰለታማ ተራራ ላይ የሚገኘው ይሄው ደን፤ በአራት አቅጣጫዎች በእሳት እየወደመ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
እስካሁን እሳቱን ለማጥፋት ከአካባቢው መስተዳድር የተደረገ ጥረት አለመኖሩን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ በግምት ከ20 ሄክታር በላይ ደን ሳይቃጠል እንደማይቀር ተናግረዋል፡፡ ወሌ 26 እና ቦሌ በሚባሉ ቀበሌዎች ውስጥ የሚገኘው ደኑ፣ የአካባቢው የተፈጥሮ ሃብት መሆኑን የጠቀሱት ምንጮች፤ ከዚህ በፊትም በተደጋጋሚ ቃጠሎ እንደደረሰበትና ግለሰቦች ለማገዶ ፍጆታ ሲሉ እሳት ለቀውበት ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን ገልፀዋል፡፡
የወረዳው የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ ከድር ስለጉዳዩ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ ከግብርና ቢሮና ከፖሊስ የተውጣጣ ግብረ ሃይል መሰማራቱንና እሳቱን በትናንትናው እለት መቆጣጠር መቻሉን ጠቅሰው ቃጠሎው በሰውና በንብረት ላይ ያደረሰው ጉዳት ባይኖረውም በደኑ ላይ ያደረሰው ውድመት መጠን እንዲሁም ፖሊስ የእሳቱን መንስኤ ፖሊስ እየመረመረ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

Read 2347 times