Saturday, 31 January 2015 13:09

የኢቦላ ቫይረስ ባህሪውን እየለወጠ ነው ተባለ

Written by 
Rate this item
(4 votes)

ቫይረሱ በትንፋሽ መተላለፍ ሊጀምር እንደሚችል ተሰግቷል

በምዕራብ አፍሪካ አገራት ተከስቶ ከ22 ሺህ በላይ ሰዎችን ያጠቃውና ወደ 9 ሺህ የሚደርሱትንም ለህልፈት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ፣ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝና ለውጡ ቫይረሱን ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ መዛመት እንደሚያስችለው ለማወቅ  ጥናት እየተካሄደ  መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፈረንሳዩን ፓስተር ኢንስቲቲዩት ተመራማሪዎች ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቫይረሱ የቀድሞ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝ የተረጋገጠ ሲሆን ተመራማሪዎቹ የቫይረሱ የባህሪ ለውጥ የከፋ አደጋ የሚያስከትል መሆኑን ለማወቅ  በጊኒ፣ በቫይረሱ በተጠቁ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የደም ናሙና ላይ ምርምር እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
የተመራማሪ ቡድኑ አባል የሆኑት ዶክተር አናቫይ ሳኩንታቢ እንዳሉት፤ የኢቦላ ቫይረስ በሚገርም ሁኔታ የተፈጥሮ ባህሪውን እየቀየረ እንደሚገኝ በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ ቫይረሶች በጊዜ ሂደት የተፈጥሮ ባህሪያቸውን መቀየራቸው የተለመደ ክስተት ነው ያሉት ዶክተሩ፣ ኢቦላም እንደ ኤች አይቪ ኤድስና ኢንፍሉዌንዛ ቫይረሶች ሁሉ በከፍተኛ ሁኔታ የባህሪ ለውጥ የማካሄድ ተፈጥሯዊ ባህሪ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ይህም ቫይረሱ ከሁኔታዎች ጋር የመላመድ አቅሙን ከፍ እንደሚያደርገውና የበለጠ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት እንደፈጠረ አክለው ገልጸዋል፡፡
ቫይረሱ በርካታ ሰዎችን እያጠቃና የባህሪ ለውጡን እየቀጠለ ከሄደ፣ በትንፋሽ የመተላለፍ ዕድል ሊኖረው ይችላል የሚል ስጋት መኖሩን የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይህም ሆኖ ግን ለጊዜው ቫይረሱ በትንፋሽ እየተላለፈ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የአለም ባንክ ፕሬዚደንት ጂም ያንግ ኪም፤ አለማችን በቀጣይ ሊከሰቱ ለሚችሉ ኢቦላን የመሳሰሉ ገዳይ በሽታዎች ይህ ነው የሚባል ዝግጅት አለማድረጓንና ይህም ከፍተኛ ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል አስታወቁ፡፡
መንግስታት፣ የእርዳታ ድርጅቶች፣ አለማቀፍ ተቋማትና ኩባንያዎች ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ የገዳይ በሽታዎች ወረርሽኞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር እጅ ለእጅ ተያይዘው መስራት ይገባቸዋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ ጥፋት ካደረሰው የኢቦላ ወረርሽኝ በመማር አለም ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል ብለዋል፡፡

Read 3415 times