Saturday, 31 January 2015 13:05

ኩባ፤ አሜሪካ በውስጥ ጉዳዩዋ ጣልቃ እንዳትገባ አስጠነቀቀች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

አሜሪካ በኩባ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እንዳትገባ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ፤ መሰል ጣልቃ ገብነቶች በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረውን ግንኙነት ትርጉም አልባ ያደርጉታል ሲሉ  መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ከ40 አመታት በኋላ ኩባን በመጎብኘት የመጀመሪያው የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ረዳት ጸሃፊ ሮቤርታ ጃኮብሰን ባለፈው ሳምንት አገሪቱን መጎብኘታቸውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ የአሜሪካ አካሄድ በኩባ ላይ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጫና ለመፍጠር ማሰቧን ያመላክታል  ብለዋል፡፡
አሜሪካ ይህንን አካሄዷን የማታስተካክል ከሆነ በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ትርጉም ያጣል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ አሜሪካ በውስጥ ጉዳያችን ጣልቃ ለመግባት የምታደርገውን ማንኛውም አይነት ሙከራ አገራቸው በዝምታ እንደማታልፈው አስጠንቅቀዋል፡፡
አሜሪካ በኩባ ውስጣዊ የፖለቲካ ተቃውሞን ለማቀጣጠል እያሴረች ነው ያሉት ራኡል ካስትሮ፣ ይሄም ሆኖ ግን ከዚህ የጣልቃ ገብነት ተግባሯ መታቀብ በምትችልበት ሁኔታ ዙሪያ ከአሜሪካ ጋር ለመምከር ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አገራቸው በኩባ ላይ የጣለችውንና ለአስርት አመታት የዘለቀውን የኢኮኖሚ ማዕቀብ እንድታነሳ ጫና እንዲያሳድሩ ጥሪ ያቀረቡት ራኡል ካስትሮ፣ ኩባንያዎቿ በኩባ የቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ላይ እንዲሰማሩ የፈቀደችው አሜሪካ፣ በሌሎች የኢኮኖሚ መስኮች ላይም እንደምትሰራ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡

Read 2163 times