Saturday, 31 January 2015 13:03

የእንግሊዝ መንግስት በአንዲት ፊደል ግድፈት የ9 ሚ. ፓውንድ ካሳ ሊከፍል ነው

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   ቴለር ኤንድ ሰንስ የተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ፣ የአገሪቱን ኩባንያዎች የመመዝገብ ስልጣን በተሰጠው ካምፓኒስ ሃውስ የተሰኘ የመንግስት ተቋም ላይ፣ ስሜን ሲመዘግብ የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ለተለያዩ ቀውሶች ዳርጎኛል ሲል በመሰረተው ክስ የ9 ሚሊዮን ፓውንድ ካሳ እንዲከፈለው ፍርድ ቤት እንደበየነ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፍርዱ የተላለፈበት የመንግስት አካል በአገሪቱ በኪሳራ ላይ የሚገኙ ተስፋ ቢስ ኩባንያዎችን በሚመዘግብበት ሰነድ ላይ፣ ከስድስት አመታት በፊት በማንችስተር የሚገኝን ቴለር ኤንድ ሰን የተባለ የከሰረ ኩባንያ ለመመዝገብ ፈልጎ፣ በስህተት የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ቴለር ኤንድ ሰንስ ብሎ በመመዝገቡና መረጃውን ለህዝብ ይፋ በማድረጉ ነው የኩባንያው ሃላፊዎች ክስ የመሰረቱበት፡፡
ኩባንያው ስሙ ተዛብቶ መመዝገቡንና በኪሳራ ላይ እንደሚገኝ የሚያሳየው መረጃ ለህዝብ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ 250 ሰራተኞቹ ስራ መልቀቃቸውን፣ የብድር አቅራቢ ተቋማትና 3ሺህ ያህል አቅራቢዎችም ከኩባንያው ጋር የነበራቸውን የስራ ግንኙነት ማቋረጣቸውን የኩባንያው ጠበቆች ተናግረዋል፡፡
በምህንድስና ስራ ላይ የተሰማራውና ከ100 አመታት ጀምሮ ወታደራዊ መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው  ቴለር ኤንድ ሰንስ ኩባንያ የቀድሞ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፍሊፕ ዴቪሰን ሰብሪ፣ ከስድስት አመታት በኋላ የፊደል ግድፈቱ መከሰቱን ሰምተው ከሁለት ወራት በፊት ከኩባንያው አመራሮች ጋር ስብሰባ ማድረጋቸውንና ክሱን መመስረታቸውን ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዙ ሮያል ኮርት ኦፍ ጀስቲስ ፍርድ ቤት ካሳ እንዲከፍል የተወሰነበት የመንግስት ተቋም በበኩሉ፣ የፊደል ግድፈቱን መፈጸሙን ቢያምንም፣ በኩባንያው ላይ ለፈጠረው ስህተት ይሄን ያህል ገንዘብ በካሳ እንዲከፍል የተጣለበትን ቅጣት ተቃውሟል፡፡

Read 1927 times