Saturday, 31 January 2015 13:01

ቱርክ ሜኒስታን ጥቁር መኪኖች ወደ ግዛቷ እንዳይገቡ ከለከለች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ፕሬዚዳንቱና 160 ባለስልጣናት ጥቁር መኪና ትተው ነጭ ሊሙዚን መጠቀም ጀምረዋል

 በመካከለኛው እስያ የምትገኘው ቱርክሜኒስታን፣ የአገሪቱ ዜጎች ከአሁን በኋላ ጥቁር ቀለም ያላቸው መኪኖችን ወደ ግዛቷ እንዳያስገቡ መከልከሏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የቱርክሜኒስታን የጉምሩክ ባለስልጣናት፣ የአገሪቱ ዜጎች ጥቁር ቀለም ያላቸውን መኪኖች ከውጭ አገራት ገዝተው እንዳያስገቡ የሚከለክል ህግ ከሰሞኑ ይፋ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ክልከላውን በምን ምክንያት ተግባራዊ እንዳደረጉት ግልጽ አለማድረጋቸውን አስታውቋል፡፡
ባለስልጣናቱ ከውጭ አገራት መኪና ገዝተው የሚያስገቡ ኩባንያዎችን፣ ከጥቁር መኪኖች ይልቅ ነጭ ቀለም ያላቸውን መኪኖች እንዲያስገቡ እያግባቡ መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፣ ነጭ ቀለም የመልካም ዕድል ተምሳሌት እንደሆነ መግለጻቸውንም ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉርባንጉላይ በርዲሞሃመዶቭ፤ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ ጥቁር መኪና መጠቀም ማቆማቸውንና ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎችም ነጫጭ ሊሙዚኖችን መጠቀም መጀመራቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ እሳቸውን ተከትለውም 160 ያህል የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት በነጭ ሊሙዚን መዘዋወር እንደጀመሩ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የቅንጦት መኪና እንዳይገባ የሚከለክል፣ የተለየ ታርጋ ቁጥር መለጠፍና እይታን የሚጋርድ ሽፋን የተለጠፈባቸውን መኪኖች ማሽከርከር የሚያግድ እንዲሁም ሌሎች ከመኪኖች ጋር የተያያዙ ጥብቅ ህጎችን ማውጣቱንና ተግባራዊ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ዘገባው ያመለክታል፡፡

Read 1674 times