Saturday, 24 January 2015 13:00

በ2015 ማራቶኖች ኢትዮጵያውያን ትኩረት እየሳቡ ናቸው

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

   2015 እኤአ ከገባ በኋላ ባለፈው አንድ ወር የኢትዮጵያ ማራቶኒስቶች በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የተካሄዱ የማራቶን ውድድሮችን እያሸነፉ ናቸው፡፡ የትናንቱን የዱባይ ማራቶን ጨምሮ ከአራት በላይ ውድድሮችን የኢትዮጵያ አትሌቶች በፍፁም የበላይነት አሸንፈዋል፡፡ በሌላ በኩል ኢትዮጵያውያኑ በሚቀጥሉት አራት ወራት በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች በሚደረጉ ትልልቅ ማራቶን ውድድሮችም በብዛት እና በከፍተኛ ደረጃ የተሳትፎ ግብዣ እያገኙ ናቸው፡፡
ዱባይ ማራቶን
ትናንት በተካሄደው የዱባይ ማራቶን ኢትዮጵያዊ አትሌቶች ፍፁም የበላይነት አሳይተዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንዶች ምድብ ከ1 እስከ 10 ደረጃ ሲያገኙ፤ በሴቶች ደግሞ ከ1 እስከ 10 ባለው ደረጃ ስምንት ገብተዋል፡፡ ከዓለም ማራቶን ውድድሮች ከፍተኛ ሽልማት በሚቀርብበት የዱባይ ማራቶን ከ1 እስከ  10 በሁለቱም ፆታዎች ለሚወጡ አትሌቶች ከተዘጋጀው 800ሺ ዶላር ኢትዮጵያውያኑ 678800 ዶላሩን አፍሰዋል፡፡ በወንዶች 399400 ዶላር እንዲሁም በሴቶች 279 400 ዶላር ማለት ነው፡፡ በሴቶች ምድብ አስደናቂ ድል ያስመዘገበችው ልጅ ከወለደች ከ18 ወራት በኋላ የመጀመርያ ማራቶኗን ያደረገችው አሰለፈች መርጊያ ናት፡፡ አሰለፈች መርጊያ  በዱባይ ማራቶን ስታሸንፍ ዘንድሮ ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን በውድድሩ ታሪክ ይህን ማሳካት ከቻሉት ኬንያዊው ዊልሰን ኪቤት እና ኢትዮጵያዊው ኃይሌ ገብረስላሴ ጋር ክብረወሰን ተጋርታለች፡፡ አሰለፈች መርጊያ የዱባይ ማራቶንን ያሸነፈችው ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ02 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በማጠናቀቅ ነው፡፡ አሰለፈችን ተከትለው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃን ሁለት ኬንያውያን አትሌቶች ሲያስመዘግቡ ከአራተኛ እስከ አስርኛ ያለውን ደረጃ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አግኝተዋል፡፡ በወንዶች ምድብ ያሸነፈው  ደግሞ ሌላው ኢትዮጵያዊ አትሌት ብርሃኑ ሃይሌ ሲሆን ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ28 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነው፡፡ እሱን በመከተል እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃ ኢትዮጵያውያን አከታትለው ወስደዋል፡፡
በማራቶን ለሶስተኛ ጊዜ ለመወዳደር ዱባይ ማራቶንን የተሳተፈው እና ከፍተኛ ውጤት እንደሚያመጣ ተጠብቆ የነበረው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ከ36 ኪሎሜትር በኋላ አቋርጦ ወጥቷል፡፡ ከዓመት በፊት የመጀመርያ የማራቶን ቅውድድሩን በፓሪስ ማራቶን አድርጎ የቦታውን ሪከርድ በማስመዝገብ ካሸነፈ ከ27 ሳምንታት በኋላ ቺካጐ ማራቶንን በመሮጥ አራተኛ ደረጃ አግኝቶ የነበረው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፤ ከ15 ሳምንታት በኋላ የዱባይ ማራቶንን ቢሳተፍም ውድድሩን ለማቋረጥ ግድ ሆኖበታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ከ13 ሳምንታት በኋላ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ሊሰበርበት ይችላል በተበለው የ2015 ለንደን ማራቶን እንደሚሮጥ ይጠበቃል፡፡
በሙምባይ እና ሂውሰተን ማራቶኖች
በሌላ በኩል ባለፉት ሳምንታት ሁለት ማራቶኖች በተለያዩ ሁለት አህጉራት ተካሂደው ኢትዮጵያዊ ማራቶኒስቶች ድንቅ የበላይነት አሳይተዋል፡፡ በኤስያ አህጉር ህንድ ላይ ተደርጎ በነበረው የሙምባይ ማራቶን በሁለቱም ፆታዎች ኢትዮጵያውያኑ ተሳክቶላቸዋል፡፡
በወንዶች ምድብ የመጀመርያ የማራቶን ውድድሩን የሮጠው አትሌት ተስፋዬ አበራ ርቀቱን በ2 ሰዓት 09 ደቂቃ ከ46 ሰከንዶች በመሸፈን ሲያሸንፍ የቦታውን ክብረወሰን ለማሻሻል ከፍተኛ ጥረት አድርጎ በ14 ሰከንዶች ዘግይቶ በመግባቱ ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡ እሱን በመከተል በሁለተኛ ደረጃ ያጠናቀቀው ሌላው ኢትዮጵያዊ አትሌት ደረጄ ደበሌ ነው፡፡ በሴቶች ምድብ ደግሞ ለሁለተኛ ተከታታይ ዓመት የሙምባይ ማራቶንን በማሸነፍ ክብሯን ያስጠበቀችው ርቀረቱን በ2 ሰዓት ከ30 ደቂቃዎች የሸፈነችው ድንቅነሽ መካሻ ስትሆን ሌሎቹ ኢትዮጵያውያውያን ኩምሺ ሲቻላ እና ማርታ ዋግራ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ አግኝተዋል፡፡ የሙምባይ ማራቶን አሸናፊዎች ለእያንዳንዳቸው በሁለቱም ፆታዎች 41ሺ ዶላር ይበረከትላቸዋል፡፡ በተያያዘ በዚያው ሰሞን ለ43ኛ ጊዜ በአሜሪካ በተደረገው የሂውስተን ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለሰባተኛ ተከታታይ አመት በውድድሩ ያለመሸነፍ ክብራቸውን አስጠብቀዋል፡፡ በሂውሰተን ማራቶን ላይ በወንዶች ምድብ ብርሃኑ ገደፋ በ2 ሰዓት ከ08 ደቂቃዎች ከ30 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ የግሉን ምርጥ ሰዓት አስመዝግቦ ሲያሸንፍ በሴቶች ደግሞ ያበሩኛል አራጌ ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ23 ደቂቃዎች ከ33 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመጨረስ ድል አድርጋለች፡፡
በለንደን ማራቶን
የ2015 ለንደን ማራቶን ከ13 ሳምንታት በኋላ ምርጥ አትሌቶች የሚካሄድ ነው ፡፡
 ከኃይሌ ገ/ስላሴ በኋላ የዓለም ማራቶን ሪከርዱን አፈራርቀው የሰሩበት ኬንያዊያኑ ዊልሰን ኪፕ ሳንግና ዴኒስ ኮሚቴ ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ከኢትዮጵያ ደግሞ ፀጋዬ መኮንን (2፡04፡32) አየለ አብሽሮ (2፡04፡27) ይጠቀሳሉ፡፡  በ2015 ለንደን ማራቶን ላይ ለወንዶች ምድብ የሚሳተፉት ምርጥ አትሌቶች ከ2፡05 በታች የሚገቡ 8 አትሌቶች፣ ለዓለመ የማራቶን ምርጥ ሰዓት ደረጃ ከ1-10 ካለው 5ቱ እንዲሁም 4ኛ ማራቶን ውድድሩን የሚያደርገውና የ10ሺህ የ5ሺሜ ሪኮርዶችን ከያዘ ከ10 ዓመት በላይ ያስቆጠረው ቀነኒሣ በቀለ ናቸው፡፡ በሴቶች ምድብ ኢትዮጵያን ወክለው የሚወዳደሩት ሁለት አትሌቶች ብቻ ሲሆኑ ፋይሴ ታደሰ እና ትግስት ቱፋ ናቸው፡፡
በፓሪስ ማራቶን
 ከ13 ሳምንታት በኋላ በሚደረገው የ2015 የፓሪስ ማራቶን ከ1 ዓመት በፊት በቀነኒሣ በቀለ የመጀመሪያ ማራቶን የተሻሻለውን የቦታውን ክብረወሰን ለመሰበር ከባድ ተወዳዳሪዎች ይገባሉ፡፡ በወንዶች የሚሳተፉት ኢትዮጵያውያን ደሬሳ ቺምሣ (2፡05፡42) ባዙ ወርቅ (2፡05፡25) ፣ ሰቦቃ ቶላ (2፡06፡17)፣ ራጂ አሰፋ (2፡06፡24) ናቸው፡፡ በሴቶች ደግሞ ሙሉ ሰቦቃ (2፡23፡13) እና አማን ጐበና (2፡23፡50) ናቸው፡፡
በቦስተን ማራቶን
ከዓለማችን የማራቶን ውድድሮች አንጋፋው በሆነው የቦስተን ማራቶን 9 የኢትዮጵያ አትሌቶች ተሳታፊ ናቸው፡፡ በወንዶች ምድብ ለሁለት ጊዜያት የቦስተን ማራቶንን ያሸነፈው ሌሊሳ ዴሲሳ፤ የማነ ፀጋዬ፤ ታደሰ ቶላ እና ገብረእግዚአብሄር ገብረማርያም ሲሳተፉ፤ 20154 ከገባ በኋላ በቻይና የተደረገውን የዣይናሜን ማራቶንን ያሸነፈችው ማሬ ዲባባ፤ አምና የቦስተን ማራቶን አሸናፊ የሆነችው ብዙነሽ ዳባ፤ አበሩ ከበደ፤ ማሚቱ ደስካ እና እጅጋየሁ ዲባባ ይወዳደራሉ፡፡




Read 2418 times