Saturday, 24 January 2015 12:59

ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ለዕርዳታ የሚያሰባሰበውን ገንዘብ ማሳደግ ይፈልጋል

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 1.3 ሚሊዮን ብር  ከህጻናትና፣ ሴቶች፣ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን ጋር ለሚሰሩ  4 ሀገር በቀል ድርጅቶችን አበረከተ፡፡ ገንዘቡ ከወራት በፊት ከ40ሺ በላይ ስፖርተኞችን ባሳተፈው 14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 10ኪ.ሜ ሩጫ በተያያዘ በተደረገው የዕርዳታ ማሰባሰብ ስራ የተገኘ ነው ፡፡  ከዘንድሮ  4 ተጠቃሚዎች  ባለፈው ሐሙስ የገንዘብ ርክብክቡ የተፈፀመበት እና የመስክ ጉብኝት የተደረገበት በኦሮምያ ክልል ደብረሊባኖስ ገዳም አካባቢ የሚገኘው ሰዋሰው ገነት የልማትና የዕርዳታ ድርጅት የመጀመርያው ነው፡፡ ሌሎቹ ሶስት ድርጅቶች ደግሞ መሰረት የበጐ አድራጐት ድርጅት ፤ በጋምቤላ የሚገኘው ብራዘርስ ኤንድ ሲስተርስ ቺልድረን ኬር ሴንተር እንዲሁም የቤንሻንጉል ሴቶች ማህበር ናቸው፡፡የሴቶች ህጻናትና ወጣቶች ሚኒስቴር ላቀረበው የድጋፍ ጥያቄ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ፈጥኖ መድረሱን በርክክቡ ወቅት የገለፁት ሚኒስትሯ ወይዘሮ ዘነቡ ፤ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በየጊዜው ማህበራዊ ሃላፊነቱን በመወጣት የሚያደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ተወካይ ሚስተር ፖስቲ ያዮ በበኩላቸው ፤ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከሚያዘጋጀው ውድድር ጎን ለጎን ለእርዳታ በሚያሰባስበው ገንዘብ ብቻ እንዳልተወሰነ ጠቅሰው የሚሊኒዬም የልማት ግቦችን ለማሳካት የሚያስችሉ ጠቃሚ መልክቶችን በየክልሉ እና በየውድድሮቹ በማስተላለፍ አጋዥ ተቋም እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በእርዳታ ለአራቱ ድርጅቶች የተከፋፈለው ገንብ በአራት መንገዶች መሰባሰቡን  የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የውድድር ዲያሬክተር አቶ ኤርምያስ አየለ ገልጿል፡፡ ዘንድሮ ከተሰበሰበው ገንዘብ ግማሹ የተገኘው  በኖርዌይ ሩጫ ከሚያዘጋጅ ክለርቪክሚለር ከሚባል ድርጅት በአጋርነት በመንቀሳቀስ ነው፡፡ ውድድሩ ሲደርስ ለትልልቅ ድርጅቶች ደብዳቤ በመፃፃፍ ልገሳዎች ተገኝተዋል፡፡ የታላቁ ሩጫ መወዳደርያ ቲሸርቶችን በልዩ ዋጋ ጭማሪ በመሸጥና ተወዳዳሪዎች በግላቸው እርዳታ በማሰባሰብ እንዲሮጡ በማበረታታት የተቀረው ገንዘብ ገብቷል፡፡ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በተያያዘ ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ ለአገር በቀል የዕርዳታ ድርጅቶች ገንዘብ በማሰባሰብ ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በሴቶች ህጻናትና ወጣቶች ጉዳይ ሚኒስቴርና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ (UN Ethiopia) ጋር በመተባበር ይንቀሳቀሳል፡፡
 እስከ 6 ሚሊዮን ብር በላይ በመሰብሰብም ለ20 ድርጅቶች አከፋፍሏል፡፡ ተጠቃሚ ለመሆን ከቻሉት መካከል ሜሪ ጆይ፣ አበበች ጐበና የህጻናት ማሳደጊያ፣ ሜቄዶኒያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ይገኙበታል፡፡ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የውድድር ዲያሬክተር አቶ ኤርምያስ አየለ በሚቀጥሉት ዓመታት የሚሰበሰበውን ገንዘብ ለማሳደግ መታቀዱን አስታውቋል፡፡ ተጠቃሚ የሚሆኑ ድርጅቶች ከወዲሁ በሴቶች ህጻናትና ወጣቶች ሚኒስቴር ቢሮ አማካኝነት ይመረጣሉም ብሏል፡፡በመላው ዓለም የሩጫ አዘጋጅ ድርጅቶች ለበጎ አድራጎት ስራ የሚውል ከፍተኛ ገንዘብ የሚሰበሰብባቸው መድረኮች መሆናቸውን የሚያመለክተው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ይህን መልካም ልምድ በኢትዮጵያ ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ነው፡፡
 የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አዘጋጆች በአገራችን ከሩጫ ጎን ለጎን እርዳታ ለሚሹ የህብረተሰብ ክፍሎች መደገፍ ይቻል ዘንድ በሩጫ ውድድር ላይ ለጤናና ለመደሰት ከመሮጥ ባሻገር ለአንድ በጎ ምክንያት በመሮጥአስተዋፅኦ ማድረግ እንደሚቻል ይመክራሉ፡፡

Read 2480 times