Saturday, 24 January 2015 12:53

ሀበሻ ቢራ በሳምንታት ውስጥ ወደ ገበያ ይገባል

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(3 votes)

300 ዓመት ዕድሜ ያለው የጀርመኑ ባባሪያ 40 በመቶ ድርሻ አለው
ሀበሻ ቢራ፣ የፋብሪካው ግንባታና የመሳሪያዎች ተከላ 99 በመቶ ተጠናቆ፣ ኢንጂነሮች አንዳንድ የማጣሪያ ሥራ እያከናወኑ ስለሆነ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ወደ ገበያ እንደሚገባ የፋብሪካው ኮሜርሻል ዳይሬክተር አቶ ዮናስ ዓለሙ አስታወቁ፡፡
አቶ ዮናስ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ከጀርመን፣ ከቼኮዝሎቫኪያ፣ ከሆላንድ፣ ከቻይናና ከኢትዮጵያ የተውጣጡ ኢንጂነሮች፣ አንዳንድ የማጣሪያና የለቀማ ሥራ እያጠናቀቁ ስለሆነ፣ ከማጣራቱ ሂደት በኋላ ቢራ እየተጠመቀ ሙከራ (ፍተሻ) ከተደረገ በኋላ ምርት እንደሚጀምር ተናግረዋል፡፡
ሥራ ሲጀምር የፋብሪካው የማምረት አቅም በዓመት 30 ሚሊዮን ሊትር ወይም 300 ሺህ ሄክቶ ሊትር እንደሆነ የጠቀሱት ዳይሬክተሩ፤ ፋብሪካው ተጨማሪ ማስተካከያ ተደርጎለት በዓመት 500ሺህ ሄክቶ ሊትር ቢራ እንደሚያመርት፣ አብዛኛው መሳሪያ KRONS ከተባለ የጀርመን ኩባንያ፣ ጋኖቹ ከቻይና፣ ሌሎች መሳሪያዎች ደግሞ ከዴንማርክና ከስዊድን መገዛታቸውን አስታውቀዋል፡፡
እኛ የቢራ ፋብሪካ ለማቋቋም ስንነሳ፣ በኢትዮጵያ ያለው የቢራ ኢንዱስትሪ ሁኔታ ተቀየረ፡፡ በመንግስት ይዞታ ስር የነበሩ የቢራ ፋብሪካዎች በሙሉ ለግል የቢራ ኢንዱስትሪዎች ተሸጡና በዓለም ታዋቂ የሆኑ የቢራ ፋብሪካዎች ወደ ኢትዮጵያ ገቡ ያሉት አቶ ዮናስ፤ በኢትዮጵያ በነበረው የቢራ የፋብሪካ ማስተዳደር አቅም (ማኔጅመንት) በዓለም ታዋቂ፣ ከፍተኛ ልምድና እውቀት ካላቸው የቢራ ፋብሪካዎች ጋር መወዳደር ስለማይችል በቢራ ፕሮጀክት አስተዳደር፣ በቢራ ገበያ፣ በገበያና ልማት ስራ፣ …የሚያግዛቸው፣ በሽርክና አብሯቸው የሚሰራ ስትራቴጂክ አጋር መፈለጋቸውን፣ በዚሁ መሰረት፣ በአውሮፓ ከ300 ዓመት በላይ ዕድሜ ካለው ባባሪያ  ጋር ለመስራት ወስነው፣ የሀበሻ ቢራ ባለአክሲዮኖችም ይሁንታ እንደሰጧቸው አስረድተዋል፡፡
አቶ ዮናስ ለምን የጀርመኑን ባባሪያ እንደመረጡ ሲያስረዱ፤ ባባሪያውያን፣ በአገራቸው በአንድ ቦታ ላይ ብቻ በዓመት 600 ሚሊዮን ሄክቶ ሊትር የሚያመርት ፋብሪካ አላቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች አንድ ፋብሪካ እንዴት በዘመናዊ መንገድ መመራት እንዳለበት ያውቃሉ፡፡ ለዚህ ማስረጃ የሚሆነን ጠንካራ በሆነው የአውሮፓ ውድድር ከዓመት ዓመት እየተሻሻሉና እያደጉ 300 ዓመት መዝለቃቸው ነው፡፡ ባባሪያ የቤተሰብ ድርጅት ሲሆን አሁን ድርጅቱን እየመራ ያለው 7ኛ ትውልድ ነው ብለዋል፡፡
ባባሪያ በ17 ሚሊዮን ዩሮ፣ 40 በመቶ አክሲዮን ገዝቶ ከሃበሻ ቢራ ጋር በሽርክና በቅርበት እየሰራ ስለሆነ እውቀትና ልምዳቸው ወደ አገራችን ገብቷል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ በሰራተኛ ቅጥርና ስልጠና በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን፣ በእነሱ አማካይነት 10 ሰራተኞች ወደ ሆላንድ ተልከውና ሰልጥነው መጥተው በፕሮጀክት ተከላና ጠመቃ እየተሳተፉ መሆኑን፣ ከማርኬቲንግ ክፍልም 5 ሰራተኞች ወደ ውጭ ተልከው የሽያጭ፣ የገበያና ልማት ስራ ተከታትለው መመለሳቸውን  ተናግረዋል፡፡
የገበያ ልማትና ሽያጩን በተመለከተ ባባሪያ ከ10 አገራት በላይ ቢራ ኤክስፖርት ስለሚያደርግ፣ ቢራ መጥመቅ ብቻ ሳይሆን መሸጡንም ያውቅበታል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ በእውቀትና ልምድ ሽግግር፣ በስልጠና፣ በቢራ ፋብሪካ አስተዳደር፣ በቢራ ሽያጭ፣ በገበያ ልማት ስራ ከፍተኛ እገዛ እያደረገልን ነው ብለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በቢራ ገበያ ያለው ውድድር ጠንካራ ስለሆነ እንዴት ወደገበያው ለመግባት እንዳሰቡ ተጠይቀው ሲመልሱ፣ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው የነፃ የንግድ ውድድር ያለው በቢራው ዘርፍ መሆኑን ጠቅሰው፣ በዚህ ውድድር ውስጥ ማነው የሚዘልቀው? የሚለው፣ የገበያውን ሁኔታና የደንበኛውን ስሜት በትክክል እያጠና የተጠቃሚው ወዳጅ የሆነ ደንበኛው የሚፈልገውን አገልግሎት አሟልቶ የሚያቀርብ፣ ሰራተኞቹ በባለቤትነት ስሜት የሚሰሩ፣ ሙያዊ ብቃት፣ ጥራት ያለውና አስደሳች አገልግሎት የሚሰጡ ሰራተኞች ያሉት ድርጅት እንደሆነ፣ ገልጸዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በገበያው ውስጥ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመዝለቅ፣ በፋብሪካው ውስጥ ብክነትን የሚቀንስ ወጪ ቆጣቢ ሥርዓት ስለዘረጋን፣ በዘመናዊ መንገድ ጥራት ያለው ምርት ስለምናቀርብ፣ ከሁሉም በላይ ሰራተኞቻችን ከፋብሪካው አክሲዮን እንዲገዙ ዕድሉ ስለተሰጣቸውና በባለቤትነት ስሜት ስለሚሰሩ፣ በአሸናፊነት ገበያው ውስጥ እንቆያለን የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡
ቀደም ሲል በነበሩት ዓመታት በቢራው ዘርፍ ነፃ የገበያ ውድድር የሚባል ነገር አልነበረም ያሉት አቶ ዮናስ፤ አንድ ፋብሪካ በግሉ ወይም ፋብሪካዎች ተሰብስው ዋጋ የመጨመር ሁኔታ፣ አንዱ የሌላውን ዋጋ እየተከተለና በመገናኛ ብዙሃን (ቲቪ፣ ራዲዮና ጋዜጦች) በማስታወቂያ ጋጋታ ህዝቡን ግራ ያጋቡና ያዋክቡ ነበር ብለዋል፡፡ ዋልያ ቢራ ወደ  ገበያ ከመግባቱ ሁለት ወር በፊት ዋጋ እንዲቀንሱ ሲጠየቁ “አያዋጣንም” ያሉ ፋብሪካዎች፣ በየምርቶቻቸው ላይ የዋጋ ቅናሽ አድርገዋል፡፡ እያንዳንዱ ፋብሪካ የሚከተለው የራሱ የዋጋ ፖሊሲ አለው፡፡ እኛም  በራሳችን መንገድ ትክክለኛ ነው፣ የህዝቡን አቅም ያገናዘበና በተወዳዳሪነት ገበያው ውስጥ ሊያቆየን ይችላል የምንለውን ዋጋ ይዘን እንቀርባለን ብለዋል፡፡
በመጨረሻም አቶ ዮናስ ወደ ገበያ እንገባለን ብለው ያቀዱት በሚያዝያ 2014 ቢሆንም ከአቅም በላይ በሆኑ ችግሮች፣ ለምሳሌ የውጭ ምንዛሪ እጥረት፣ ብድር ማጣት፣ በ2010 ዓ.ም የተደረገው የዶላር ዋጋ ቅነሳ፣ ባለአክሲዮኖች የሚፈለግባቸውን ገንዘብ በወቅቱ ያለመክፈል፣ … የፋብሪካውን ግንባታ እንዳጓተቱት ጠቅሰው፣ ባለአክሲዮኖች በትዕግስት በመጠበቃቸው አመስግነው አሁን ወደ ገበያ ልንገባ ስለሆነ ደስ ብሎናል፤ ደስ ይበላችሁ ብለዋል፡፡


Read 4126 times