Saturday, 24 January 2015 12:54

ዩኤስኤአይዲ በተለያዩ ዘርፎች ያሠለጠናቸውን ሴቶች ሸለመ

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(0 votes)

የአሜሪ ካ ዓለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅት (ዩኤስኤአይዲ) የሴቶችን የግብርና ምርቶች ተጠቃሚነትን ለማሳደግና አገራዊና ዓለማቀፋዊ ግብይታቸውን ለማሻሻል በዘረጋው ዩኤስኤአይዲ ኤጂፒ አምድ ፕሮግራሙ በተለያዩ ዘርፎች (በእቅድ አዘገጃጀት ቢዝነስ ፕላን፣ ሂሳብ አያያዝ፣ ቢዝነስ አመራር፣ …) ለ6 ወር ያሠለጠናቸውን ሴቶች ሸለመ፡፡ እንዲሁም ብዙ ሴቶችን በአባልነት የያዙ ዩኒዬኖችና ገበሬ ማኅበራት ከሽልማቱ ተቋድሰዋል፡፡
ቀዳማይ እመቤት ሮማን ተስፋዬና የአሜሪካ አምባሳደር በተገኙበት በዚህ ሳምንት በሂልተን ሆቴል በተካሄደው የሽልማት ሥነ - ሥርዓት፣ ከአዲስ አበባ፣ ከትግራይ፣ ከአማራ፣ ከኦሮሚያና ከደቡብ ክልሎች የተመረጡ 100 ሴቶች፣ ወደየመጡበት ሲመለሱ፣ እያንዳንዳቸው፣ ከሥልጠናው ያገኙትን እውቀትና ልምድ ለአምስት አምስት ሴቶች ለማካፈል ወይም ለማሠልጠን ቃል ገብተዋል፡፡
የዚህ ፕሮግራም ዓላማ በግብርና ዘርፎ የተሰማሩ ሴቶችን በማሠልጠን ችግሮቻቸውን በመቅረፍ ተሳትፎአቸው ማሳደግ ነው ያሉት በፕሮግራሙ የአግሮቢዝነስና ዲቨሎፕመንት ም/የቴክኒክ ዳይሬክተር አቶ ታደለ ገላን፤ ሴቶቹ በቡና፣ በሰሊጥ፣ በስንዴ፣ በበቆሎ፣ በማር፣ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግና የእሴት ሰንሰለት ለመጨመር፣ የገንዘብ ችግር ላለባቸው የብድር አቅርቦት በማመቻቸት፣ በየተሰማሩበት ፈጠራ ያሳዩትን በማበረታታት፣ የአመጋገብ (ኑትሪሽን) ሥርዓትን በማሳደግ፣ የባህርይ ለውጥ እንዲያደርጉና የመግባባት ችሎታቸውን ለማሻሻል ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልፀዋል፡፡
በዚሁ መሰረት ከአዲስ አበባና ከአራቱ ክልሎች በስልጠናው የተሳተፉ ሴቶች በተማሩት መሰረት ራሳቸው ባዘጋጁት ቢዝነስ ፕላን ተወዳድረው ያሸነፉ 5 ሴቶች፣ ሽልማት የተሰጣቸው ሲሆን አንደኛ የወጣችው ለቢዝነስ ስራዋ የሚያግዝ መሳሪያ መግዣ 200 ሺህ ብር ተሸልማለች፡፡ 2ኛ የወጣችው 150 ሺህ ብር፣ 3ኛ 100 ሺህ ብር፣ 4ኛ 75 ሺህ ብርና 5ኛ የወጣችው 50 ሺህ ብር ተሸልማለች፡፡  
በዚሁ ወቅት የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላክ ባደረጉት ንግግር፣ በእርሻው ዘርፍ ማለትም ቡና፣ ሰሊጥ፣ በቆሎ፣… ወደ ውጭ በመላክ የወንዶች ተሳትፎ በጐላበትና ተፅዕኖው በበዛበት ማኅበረሰብ ውስጥ፣ ነጋዴ የሆናችሁና የእርሻ ምርት ወደ ውጭ የምትልኩ አብዛኞቹ ሴቶች፣ በጣም ጠንካራና ደፋር ናችሁ፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገሪቷ ተንሰራፍቶ ያለውን ሁኔታ በመጋፈጣችሁ በእርሻው አመራር ትክክለኛው አርአያና ሞዴል ናቸው፡፡ ዛሬ በቢዝነስ አመራር ፕሮግራም ለመሳተፍ ላደረጋችሁት ቁርጠኝነት እውቅና የምንሰጥበት ቀን ነው ብለዋል፡፡
ከዩኒየኖች መካከል ከፍተኛውን የሴት አባላት ቁጥርና ስም በተሰጠው ፎርም ከወረዳው ሴቶች መካከል 25 በመቶ መዝግቦ በማቅረብ 1ኛ የሆነው በደቡብ ክልል የየም ልዩ ወረዳ ተባበር ሁለገብ የገበሬዎች የኅብረት ሥራ ማኅበራት ዩኒዬን ሲሆን፤ በዱባይ በተዘጋጀው የገልፍ 2015 ዓለም አቀፍ የንግድ ግብይት ላይ የኤክስፖርት ምርቱን እንዲያስተዋውቅና የንግድ ትስስር እንዲፈጥር ሙሉ ወጪው እንደሚሸፈንለት ታውቋል፡፡
ከደቡብ፣ ከትግራይ፣ ከአማራና ከኦሮሚያ ክልሎች 1ኛ እና 2ኛ የሆኑት የገበሬዎች ኅብረት ሥራ ማኅበራት፣ እያንዳንዳቸው በእጅ የሚገፋ ትራክተር፣ 3ኛ እና 4ኛ የወጡት እያንዳንዳቸው ሞተር ቢስክሌት የተሸለሙ ሲሆን፣ የመጀመሪያዎቹ 8ሺህ አዲስ የሴት አባላት እያንዳንዳቸው የአንገት ሻርፕ፣ አምስትና ከዚያ በላይ ሴቶች እንዲመዘገቡ ያደረጉ 500 ሰዎች እያንዳንዳቸው አንድ ዣንጥላ ተሸልመዋል፡፡

Read 1976 times