Saturday, 29 November 2014 11:18

“ሙሽራን ያላችሁ እስቲ እንያችሁ…”

Written by  ኤፍሬም እንዳለ
Rate this item
(9 votes)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሀሳብ አለን…ስብስባዎች ሁሉ… አለ አይደል… “እንዴት ሰነበታችሁ…” በሚል ብቻ ይከፈትና ወደ ጉዳዩ ይገባ! አሀ…“ክቡር እከሌ እከሌ፣” “ክብርት እከሊት እከሌ፣” “የተከበሩ እከሌ እከሌ”…ምናምን ሲባል የስብሰባው ሲሦ እያለቀ ነዋ! ለነገሩ… (“ለምን ይዋሻል!” የሚሉት ነገር ነበረ አይደል!) ብዙ ስብሰባዎች ላይ “እንትንህን እንደ ዳናኪል እንፋሎት እንዳላቦንልህ!” አይነት “የጉልበት ግማሹ ምላስ ነው…” ነገር በዝቷላ! (እኔ የምለው…አንዳንዱ መድረክ ላይ ወጥቶ እንዴት ነው እንዲህ ‘ልክ ልክ ማጠጣት’ የሚዋጣለት!)
አንድ ወዳጃችን ሲነግረን አለቅየው ‘መጠመቁን’ ለበላዮቹ ለማስመስከር የማይሞክረው ነገር የለም፡፡ በተለይ ስብሰባዎች ላይ የሚናገረው ‘ቦተሊካ’ ነክ ንግግር ካርል ማርክስን ጢሙንና ጸጉሩን አርግፎለት ‘አይ ሮቦት’ ነገር ያስመስለው ነበር፡፡ እናላችሁ…በቅርብ ጊዜ ሚጢጢና የሰማይ ስባሪ አለቆችና አለቆች ነገሮችን ይሰበስብና…“እዚህ ክፍል ውስጥ የግንዛቤ ችግር ያለባችሁ ሰዎች እንዳላችሁ ይታወቃል፡፡ የኒኦ ሊበራሊዝም አስተሳሰብ መሥሪያ ቤታችን ውስጥ እንዲገባ መፍቀድ የለብንም…” ምናምን እያለ እሱ ራሱ ባልገባው ነገር ግራ እንዳጋባቸው ሲነግረን ነበር፡፡ ወዳጃችን በሆዳችን ግን ሁላችንም ቂ…ቂ… ብለናል…” ብሎናል፡፡
እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ለነገሩ በሆዳችን ቂ…ቂ… የሚያሰኙ ነገሮች መአት ናቸው፡፡ ጮክ ብለን ቂ…ቂ…ብንል አበሳ ነው፣ ዝም እንዳንል  እንዴት አስችሎን — በሆድ እንኳን እንሳቅ እንጂ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ፡፡ ሰውየው ንግግር እያደረገ ነው አሉ… እናላችሁ …ሦስት አራቱ አንድ ላይ በመናገር በየመሀሉ ያቋርጡታል፡፡ ብሽቅ ይላል፡፡ ተራ በተራ እንዲናገሩ ለማድረግም ምን ይላል… “ዛሬ እዚህ አዳራሽ ውስጥ ብዙ ደደቦች አሉ፡፡ በአንድ ጊዜ አንድ ደደብ ብቻ ቢናገር አይሻልም…” ይላል፡፡
ተሰብሳቢዎቹ ምን ቢሉት ጥሩ ነው  “…እኮ ቀጥላ!” አሪፍ አይደል! ዘንድሮ በየቦታው “…እኮ ቀጥላ!” መባል የሚገባንን ቤቱ ይቁጠረን፡፡
ስሙኝማ…“ክቡራንና ክቡራት፣ ደህና  ሁኑ፣ አትሁኑ የእኔ ጉዳይ አይደለም…ምን አግብቶኝ ነው እንደምን አደራችሁ የምለው? አሁን ወደ ስበሰባችን እንገባ፣” የሚል የክብር እንግዳ የመጣ ቀን… ያኔ የምር ዘመኑ እየገባን ነው ማለት ነው፡፡ እንደምን ብንውል ብናድር ማንም ግዴለውማ! አይደለም የእኛ ቤጤ የዓለም ሰዎችን ቀርቶ አባቶች እና ምዕመናን እንደምን አደራችሁ!... እንደምን ዋላችሁ!... እንደምን አመሻችሁ…” ሲለን እንኳን አንዳንዴ እንደው ግድ ሆኖባቸው ነው እንላለን፡፡
እኔ የምለው…አርቲስቶች (እና ‘ሴሌብሪቲዎች’…) ምናምን…አለ አይደል…በሬድዮ፣ በቲቪ ምናምን ሲቀርቡ… “እወዳችኋለሁ…” የሚሏት ነገር አሁን፣ አሁን ቂ…ቂ…ቂ… ታሰኘን ጀምራለች፡፡ ልክ ነዋ… ከዘመድ፣ አዝማድ ጋር ሁሉ ተጠማምዶ “ሸንኮራ ጠበል ቢጠመቅ ይሻላል ወይስ አርሴማ ገዳም ቢገባ…” እየተባለ ምክክር እየተደረገበት… እኛን “እወዳችኋለሁ…” ሲለን አሪፍ አይደለም፡፡ እኔ የምለው…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…አሁን አንድ አንድ ‘ቶክ ሾው’ ምናምን የሚባሉ ዝግጅቶች ላይ እየተለመደች የመጣች አባባል አለች፡፡ “እንዲህ ያሳመረኝ እንትን እንትን ቡቲክ ነው…” አይነት ነገር ይባላል፡፡ ደስ የሚል ዘመን ነው፡፡ ድሮ አፍ አውጥቶ “አምራለሁ…” ቢል የሰፈር ዕድር ሁሉ ባያድምበት ነው! ሀሳብ አለን…አንዳንድ ጊዜ… አለ አይደል… “ይህን የሚያምር ልብስ ያለበሰኝ…” ይባልልንማ! አሀ…እንደዛ ስናስብስ!  ቂ…ቂ…ቂ…
ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ዘንድሮ የ‘ቲፎዞ ነገር’ አልበዛባችሁም! የምር አስቸጋሪ ነው…ጥሩ ነገር መሥራት ብቻውን በቂ ያልሆነበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ “ስማ እንትን ኤፍ ኤም የምታውቀው ሰው የለህም!” መባባል ለመደብን፡፡ ምን ይደረግ!…‘ቲፎዞ’ ከሌለን ነገርዬው…አለ አይደል…“ከሌለህ የለህም…” አይነት ይሆናል፡፡
እናላችሁ…አሪፍ መጽሐፍ መጻፍ ብቻ፣ አሪፍ ዘፈን መዝፈን ብቻ፣ ብዙ የግጥም መድበል ማውጣት ብቻ፣ ጥሩ መተወን ብቻ ወዘተ. በቂ አይሆንም፡፡ በምላሳቸው “ወንድምና እህትን ማጋባት ይቻላል…” የሚባሉ አይነት ‘ሎቢይስቶች’ ያስፈልጋሉ፡፡
የምር ግን…አንዳንድ ሥራዎች ቆይተርው እናንተ ዘንድ ይደርሱና… አለ አይደል… “ይሄን ነገር እንዴት እስከ ዛሬ ድረስ አላየሁትም...” አይነት ነገር ትላላችሁ፡፡ መልሱ አጭር ነው… ‘ኖንቼ ቲፎዞ!’
ስሙኝማ… ብዙ ሠርግ ምናምን ላይ አይታችሁልኛል…ጠጁ ምናምኑ በ‘መሬት በታች መተላለፊያዎች’ (ቂ…ቂ...ቂ….) የሚሄደው ወደሚታወቁ ሰዎች፣ ወደ ሰፈር ሰዎች፣ ወደ መሥሪያ ቤት ባልደረቦች፡ ምናምን ነው፡፡ ዘመኑ የ‘ቲፎዞ’ ነዋ!
ደግሞላችሁ…አንዳንድ ቦታ የደረጃም ሆነ የደሞዝ እድገት የሚገኘውም በ‘ቲፎዞ’ ነው ይባላል፡፡ ዘንድሮ ደግሞ ለ‘ቲፎዞነት’ የሚያመቹ መመዘኛዎች በዝተዋል፡፡ ከሁሉ በላይ ግን ‘የአገር ልጅነት’ ዋናው ነው፡፡ እኔ እኮ አንዳንዶቹማ ከሰፊው ‘የአገር ልጅነት’ ወደ ሰፈርነት ሲወርዱ ስታዩ ነገ ደግሞ ‘በግቢ’ እንዳይሆን ትላላችሁ፡፡
ስሙኝማ…ዘንድሮ መንደሮች ‘መደብ’ የሚለይባቸው እየሆኑ አይደል…እዛም ለየት ያሉ ‘ቲፎዞነቶች’ ይኖራሉ ማለት ነው፡፡ ለመደብና! “ዘመድ ከዘመዱ…” ምናምን የሚባል ነገረ አለ አይደል፡፡ ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው አንዱን ጎብኚ እያዟዟረ ኒው ዮርክን ያስጎበኘው ነበር፡፡ እናላችሁ… አንድ ቤተ መንግሥት የሚያክል መኖሪያ ቤት ይደርሳሉ፡፡
አስጎብኚውም እንዲህ ይላል… “ይህ በኒው ዮርክ እጅግ ሀብታም የሆነው ሰው መኖሪያ ቤት ነው፡፡ አብሳዩ ጀርመናዊት ነች፣ የቤት ሠራተኛዋ ፈረንሳዊት ነች፣ ዕቃ አመላላሹ ጃፓናዊ ነው፣ ሜካኒኩ ስኮትላንዳዊ ነው፣ የቤት ጽዳት ሠራተኛዋ ስዊድናዊት ነች፣  ፀሀፊው ደግሞ አሜሪካዊት ነች፡፡”ጎብኚው ሲመልስ ምን አለ መሰላችሁ… “ይሀ መኖሪያ ቤት ሳይሆን የዓለም ፍርድ ቤት ነው፡፡” ኧረ እዚህ በመጣ፣ ቤተ መንግሥት ሊያስንቁ ምንም የማይቀራቸው ቤቶች ባይኖሩ ነው! እንደውም አንዳንዶቹ እንዲህ አይነት ቤቶች ባሉባቸው አካባቢዎች ሲያልፉ የመኪና ጥሩምባ ማሰማት ክልክል እንደሆነ በቀደም ወዳጄ እየነገረኝ ነበር፡፡ “ገና ምን አይተሽ!” አለ ባል ሚስት ላይ ሲፎክር!
እኔ የምለው…እግረ መንገዴን…ደግሞ የት አካባቢ ነው…“ከጥራት በታች የተሠራ መንገድ እየፈረሰ ነው…” ምናምን ሲባል ሰማን ልበል! …‘ማፍረስ’ ቀላል የሆነባት አገር! ሀሳብ አለን… ለማፍረስ ጥቅም ላይ የሚውሉ ዲጂኖ ምናምን አይነት መሣሪያዎች ከውጪ ይገቡ እንደሆነም፣ እዚሁ ይመረቱ እንደሆነም ብዛታቸው ይቀነስልንማ! አሀ…ችግር የሚፈጥርው እኮ ‘እንደ ልብ’ የሚገኝ ነገር ነው፡፡ ለነገሩ ዲጂኖውም ቢጠፋ… አለ አይደል… “በጥፍሬ እየቧጠጥሁ ካላፈረስኵ ሞቼ እገኛለሁ…” የምንል አንጠፋም፡፡ ዘመኑ እንዲህ ነዋ!
እናላችሁ…‘የቲፎዞነት’ ዘመን ነው፡፡ እኛ “የለም…” የተባልነው የለስላሳ መጠጥ አይነት እዛው በዛው ለ‘ቲፎዞ’ ሲሰጥ ያየንበት ሬስቶራንት ነገር አለ፡፡
ታዲያላችሁ…በየስብሰባውም የሚገጥማችሁ ነገር ‘የቲፎዞ’ ነገር ነው፡፡ ያው ያቺ ከድሮ ጀምሮ የተለመደች ‘በተንተን ብሎ የመቀመጥ’ ስትራቴጂ አለች አይደል… ሰበሳቢውም “አንድ ከዚህ ጫፍ፣ አንድ ከመሀል፣ አንድ ከወዲያኛው ጫፍ…” ምናምን ይልና ስትራቴጂያዊ ቦታቸውን የያዙ ‘የቲፎዞ ስብስቦች’ ….ይቆጣጠሩታል፡፡
እናላችሁ…ሰዉ ከሁሉ አስቀድሞ “እንትን መሥሪያ ቤት ሰው ታውቃለህ…” ምናምን የሚባለው ዘመኑ ‘የቲፎዞ’ ስለሆነ ነው፡፡
አሁን፣ አሁን የሆነ ነገር፣ በተለይ የጥበብ ሥራ፣ ሲያደንቁልን ከሥራው ይልቅ “ሰውዬዋ ፕሮፓጋንዳ እየነሰነሰች ነው እንዴ!” እንላለን፡፡
እናማ…“ሙሽራን ያላችሁ እስቲ እንያችሁ…” አይነት የመጠቃቀስ፣ በምስጢር የመጠራራት ‘ቲፎዞነት’… አለ አይደል… ‘በጨው ደንደስ በርበሬውን እያስወደሰ’ ስለሆነ ጦሳችንን ይዞ ይሂድልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Read 3237 times