Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Friday, 06 January 2012 08:38

ሜሪል ስትሪፕ ለበርካታ ሽልማቶች እየታጨች ነው

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ሰሞኑን በእንግሊዝ ለዕይታ በበቃ “ዘ አይረን ሌዲ” የተሰኘ ፊልሟ በሃያሲያን ዘንድ ከፍተኛ ሙገሳዎች የተቀዳጀችው ሜሪል ስትሪፕ፤ ለበርካታ ሽልማቶች እየታጨች እንደሆነ ተጠቆመ፡፡ “ዘ አይረን ሌዲ” በቀድሞ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርጋሬት ታቸር ህይወት ዙርያ ያጠነጥናል፡፡ ስትሪፕ በፊልሙ ላይ ባሳየችው የትወና ብቃት በእንግሊዝ መገናኛ ብዙሃን ተወድሳለች፡፡ የ62 ዓመቷ ሜሪል ስትሪፕ በዚህ ወር በሚካሄዱት የጐልደን ግሎብና የስክሪን ራይተርስ ጊልድ አዋርድ በምርጥ ተዋናይት ዘርፍ ሰፊ የማሸነፍ ዕድል እንዳላት እየተገለፀ ነው፡፡

ከሁለት ሳምንት በኋላ በጀርመን በሚከናወነው የበርሊን ፊልም ፌስቲቫል ላይ ሜሪል ስትሪፕ የህይወት ዘመን የክብር ተሸላሚ በመሆን “ጎልደን ቢር” የተባለውን ሽልማት እንደምትቀበልም ይጠበቃል፡፡በቀድሞዋ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርጋሬት ታቸር ጠንካራ ሰብእና፣ የፖለቲካ አቋምና ልዩ ልዩ ፖሊሲዎች መማረኳን የገለፀችው ስትሪፕ፤ ገፀባህርያዋን በቅጡ ለማወቅና ለመተዋወቅ የተለያዩ ጥናታዊ ዘገባዎችና የቪድዮ ፊልሞችን ለወራት እንደተመለከተች ተናግራለች፡፡ ማርጋሬት ታቸር ለ11 ዓመት ያህል የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ሰርተዋል፡፡ 10 ሚሊዮን ዶላር በጀት በወጣበት በዚህ ፊልም ላይ የተወነችው ሜሪል ስትሪፕ ኦስካር ልትሸለም እንደምትችል የተገመተ ሲሆን ግምቱ እውን ከሆነ ለስትሪፕ ሦስተኛ የኦስካር ሽልማት ይሆንላታል፡፡በኦስካር የሽልማት ታሪክ የዘንድሮውን ሳይጨምር ለ16 ጊዜያት በምርጥ ተዋናይት ዘርፍ በዕጩነት በመቅረብ ክብረ ወሰን ያላት ሜሪል ስትሪፕ፤ በሁለት ፊልሞች የኦስካር ሽልማት የወሰደች ሲሆን ለ26 ጊዜያት በጎልደን ግሎብ ሽልማት እጩ ሆና ቀርባ ሰባት ጊዜ ተሸላሚ  ሆናለች፡፡ ከ44 በላይ ፊልሞች ላይ የተወነችው ስትሪፕ፤ በጠቅላላው 2.7 ቢሊዮን ዶላር ማስገባቷንና በአንድ ፊልም በአማካይ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንደምታስገኝ ቦክስ ኦፊስ ሞጆ ጠቁሟል፡፡

 

 

 

Read 2611 times Last modified on Friday, 06 January 2012 08:42