Saturday, 20 September 2014 10:55

ኢቦላ የላይቤሪያን ህልውና አደጋ ላይ ጥሎታል

Written by 
Rate this item
(4 votes)
  • 160 ባለሙያዎች ህክምና ሲሰጡ በኢቦላ ተይዘው፣ ግማሽ ያህሉ ሞተዋል
  • 2 ሺህ 46 ዜጎቿ በቫይረሱ ተይዘዋል፤ 1ሺህ 224 ሞተዋል
  • የአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ተቃውሷል

         በላይቤሪያ በከፍተኛ ፍጥነት በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ቫይረስ፣ የአገሪቱን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በማቃወስ ብሄራዊ ህልውናዋን አደጋ ላይ የጣለ ከፍተኛ ችግር የሆነበት አስከፊ ደረጃ ላይ መድረሱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡የአገሪቱን የመከላከያ ሚኒስቴር ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ለ14 አመታት በዘለቀውና እ.ኤ.አ በ2003 በተቋጨው የእርስ በርስ ግጭት 250 ሺህ ያህል ዜጎቿ የሞቱባትና በመሰረተ ልማት አውታሮቿ ላይ ከፍተኛ ውድመት የደረሰባት ላይቤሪያ፣ አሁን ደግሞ ኢቦላ እንደ ሃገር መቀጠሏን ጥያቄ ውስጥ የሚከት የህልውና ፈተና ሆኖባታል፡፡ በቅርቡ በአገሪቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ በሽታ ከጊዜ ወደጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በበሽታው ከተጠቁ 2ሺህ 46 የአገሪቱ ዜጎች መካከል 1ሺህ 224 ያህሉ ተህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ገልጧል፡፡“ኢቦላ ለላይቤሪያ ብሄራዊ ህልውና እጅግ አደገኛ ስጋት እየሆነ ነው፡፡ በፍጥነት በመሰራጨት ላይ የሚገኘው ይህ በቀላሉ የሚተላለፍ ገዳይ ቫይረስ፣ በአገሪቱ አጠቃላይ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ቀውስ ፈጥሯል፡፡” ብለዋል የላይቤሪያ የመከላከያ ሚኒስቴር ብሮዊን ሳሙካይ፣ ባለፈው ማክሰኞ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አባላት ጋር ባደረጉት ውይይት፡፡

በሽታው በአገሪቱ ክፍተኛ ጥፋት እያደረሰ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በቂ የጤና መሰረተ ልማት ያልተሟላላት የላይቤሪያ የጤና ተቋማት በበሽታው ተጠቂዎች መጣበባቸውንና ተገቢውን የህክምና አገልግሎት መስጠትና የቫይረሱን ስርጭት መግታት የማይቻልበት ደረጃ ላይ መደረሱን አስረድተዋል፡፡ አለማቀፉ ማህበረሰብ በላይቤሪያ ለተከሰተው የኢቦላ ችግር የሰጠው ምላሽ እጅግ አናሳ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ላይቤሪያ ከፍተኛ የሆነ የጤና መሰረተ ልማት አውታሮች፣ የህክምና ቁሳቁስ፣ የህክምና ባለሙያና የገንዘብ እጥረት እንዳለባት የገለጹት ሚኒስቴሩ፣ ይህም አገሪቱ በፍጥነት እየተሰራጨ ያለውን የኢቦላ በሽታ ለመግታት እንዳትችል እንዳደረጋት ተናግረዋል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የላይቤሪያ ልኡክ በበኩሉ፣ የአገሪቱ የህክምና መስጫ ተቋማት በተገቢው ሁኔታ ያልተደራጁ መሆናቸው በቂ ህክምና ለመስጠት አለማስቻሉን ገልጾ፣ ተገቢውን ስልጠና ሳይወስዱና ጥንቃቄ ሳያደርጉ የህክምና ስራቸውን ሲያከናውኑ የነበሩ 160 የጤና ባለሙያዎች በሽታው መያዛቸውንና ግማሽ ያህሉም ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን አስታውቋል፡፡ላይቤሪያ ችግሩ ከተከሰተባቸው ሌሎች የምዕራብ አፍሪካ አገራት ጋር ሲነጻጸር፣ በሽታውን በመግታት ረገድ ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ ስራ አለመስራቷን ጠቆሞ፣ በቫይረሱ የተጠቁ ዜጎችን ለማከም በጤና ተቋማት የአልጋ እጥረት መኖሩንም ገልጧል፡፡የአለም የጤና ድርጅትም፣ በላይቤሪያ የተከሰተውን የኢቦላ በሽታ ችግር ለመፍታት ትኩረት ሰጥተው በመስራት ላይ ለሚገኙ አለማቀፍ ድርጅቶች፣ የጀመሩትን ጥረት በሶስትና አራት እጥፍ እንዲሳድጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡

Read 2736 times