Print this page
Saturday, 20 September 2014 10:52

ፀሐይ ሪል እስቴት የቤቶች ሽያጭ ጀመረ

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(13 votes)

                     የቻይናውያን ባለሀብት ንብረት የሆነው ፀሐይ ሪል እስቴት፣ በየካ ክፍለ ከተማ ሲኤምሲ አደባባይ አጠገብ እየሰራ ያለውን የመኖሪያ ቤቶችና የንግድ ማዕከላት ሽያጭ በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡፡ ከዘጠኝ ወራት በፊት የተጀመረው የመኖሪያ ቤቶች መንደር ግንባታ 70 በመቶ በመጠናቀቁና ቀደም ሲል ቤት ለመግዛት የተመዘገቡ ሰዎች ለምን ሽያጭ አትጀምሩም እያሉ ስላስቸገሯቸው፣ የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፣ ከንቲባ ኩማ ደመቅሳና የቻይናው አምባሳደር ዢዢዮዋን ቤቶቹን መርቀው በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ሽያጭ መጀመራቸውን የፕሮጀክቱ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ይጆን ዋንግ በተለይ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ አዲስ አበባ፣ የአፍሪካ ህብረትና የተለያዩ የተባበሩት መንግስታት ድርጅቶች፣ ኤጀንሲዎችና የተለያዩ ዲፕሎማት መቀመጫ በመሆኗ፣ መዲናይቱን ዓለም አቀፍ ገጽታ ለማጎናፀፍና የነዋሪዎቿን የመኖሪያ መንደር ጥራት ደረጃውን የጠበቀ ለማድረግ ይህን የከተማ ውስጥ ከተማ ለመገንባት መነሳሳታቸውን ም/ሥራ አስኪያጅ ተናግረዋል፡፡ የከተማዋ ነዋሪዎች ያማረ ቪላ ሊኖራቸው ይችላል፡፡

ነገር ግን በሚኖሩበት አካባቢ ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ተቀናጅተው አያገኙም፡፡ ለምሳሌ ሲኒማ ቤት ወይም የገበያ ቦታ ቢፈልጉ፤ በመኪና ከ30 ደቂቃ በላይ መጓዝ ሊኖርባቸው ይችላል፡፡ የእኛ ፕሮጀክት ሲጠናቀቅ ለኑሮ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ተሟልተው ይገኛሉ፡፡ ባለኮከብ ሆቴል፣ ሲኒማ ቤት፣ ጂምናዚየም፣ የዋና ስፍራ፣ ትላልቅ የገበያ ማዕከላት (ሾፒንግ ሞልስ)፣ ሱፐር ማርኬቶች፣ መሰብሰቢያ አዳራሾች፣ ባንኮች፣ … አብዛኛው አስፈላጊ ነገሮች የተሟሉለት ይሆናል በማለት አስረድተዋል፡፡ የመኖሪያ መንደሩ 13 ህንፃዎች ሲኖሩት፣ ባለ 12 ፎቅ መሆናቸው ታውቋል፡፡ መንደሩ ከፊት ለፊት አራት ዋና ዋና የንግድ ማዕከላት ሲኖሩት እርስ በርስ የተገናኙ ባለሁለት ፎቅ ህንፃ እንዳላቸው ታውቋል፡፡ የመንደሩ ቤቶች ባለሁለት፣ ባለሦስት፣ ባለአራት ክፍሎችና እንግዳ ማረፊያ (ገስት ሩምስ) ሲኖራቸው ትልቅ አረንጓዴ ስፍራ፣ ፏፏቴ (ፋውንቴን ፑል)፣ ከህንፃው ስር መኪና ማቆሚያ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች፣ ለሕፃናትና ለአረጋውያን የሚያስፈልጉ ቁሶች፣ … የተሟሉለት እንደሚሆን ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ኢንቨስትመንት ከ1 እስከ 1.5 ቢሊዮን ዶላር (ከ20 እስከ 30 ቢሊዮን ብር) መሆኑን የጠቀሱት ሚ/ር ዋንግ፤ ባለፈው ታህሳስ ወር የተጀመረው የመኖርያ ቤቶች ግንባታ በዘጠኝ ወር 70 ከመቶው በመጠናቀቁ በቀጣዩ ሚያዝያ ወር የንግድ ማዕከላቱ ደግሞ በ2008 ዓ.ም ሙሉ በሙሉ ይጠናቀቃሉ ብለዋል፡፡ የቤቶቹ ዋጋ እንዳሏቸው ጥቅም (አድቫንቴጅ) የተለያየ መሆኑን የጠቀሱት ሚ/ር ዋንግ፤ አነስተኛው ዋጋ በካሬ ሜትር 22ሺ ብር፣ አማካይ ከፍተኛ ዋጋ 26ሺ ብርና ከዚያም በላይ ሊሆን እንደሚችል ገልፀዋል፡፡ በፀሐይ ሪል እስቴት ግንባታ 100 ቻይናውያንና ከ300-500 የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን እየተሳተፉ መሆኑ ታውቋል፡፡

Read 8580 times