Saturday, 20 September 2014 10:48

“ሊፋን ሞተርስ” ኢትዮጵያን የምሥራቅ አፍሪካ ማዕከል ሊያደርግ አቅዷል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

    ኢትዮጵያ ጦርነት የሌለባት ሰላማዊ አገር በመሆኗ፣ ሕዝቧም ቀማኛ፣ ዘራፊና ነጣቂ ባለመሆኑ ኢትዮጵያን የምሥራቅ አፍሪካ ማዕከል አድርገን እየሠራን ነው ሲሉ የሊፋን ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ ሚ/ር ፍራንክ (በቻይናዊ ስማቸው ሊዩ ጂያንግ) ገለፁ፡፡ ሚ/ር ፍራንክ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ - ምልልስ፤ “የኢትዮጵያ ሕዝብ ጨዋ ነው፣ ስርቆት፣ ዝርፊያ፣ቅሚያና ነጠቃ የለበትም፡፡ ለዚህም ሕዝቡን፣ ደንበኞቻችንንና መንግሥትን በጣም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡ ወደፊት ወደ ምሥራቅ አፍሪካ ጐረቤት አገራት የመኪና ምርቶችን ለመላክ ኢትዮጵያን ማዕከል አድርገው ለመስራት ማቀዳቸውን በመግለጽም በዱከም ኢስተርን ዞን፣ በ400 ሚሊዮን ዶላር ዘመናዊ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ እየገነቡ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ እስካሁን 3,500 መኪኖች መሸጣቸውን የጠቀሱት ሥራ አስኪያጁ፤ ወደፊት እንደገበያው ሁኔታ በዓመት 5,000 መኪኖችና ከዚያም በላይ ለመገጣጠም ማቀዳቸውን ገልፀዋል፡፡

የዘንድሮው የመኪና ሽያጭ ገበያ በተለያዩ ምክንያቶች የጠበቁትን ያህል ባይሆንም ወደፊት እንደሚሻሻል የጠቆሙት ኃላፊው፤ ለገበያው አለመጨመር ዋነኛው ችግር ኢትዮጵያውያን ከአዲስ መኪና ይልቅ አሮጌ መግዛት ስለሚወዱ ነው ብለዋል፡፡ “አሮጌ መኪና የመጠቀሚያ ጊዜ ወሰን ስለሌለው አሁን በጐዳና ላይ የሚታዩት አብዛኞቹ አሮጌ መኪኖች ከ30 ዓመት በላይ ያገለገሉ ናቸው፡፡ በዚህም የነሳ የተቃጠለ ጋዝ በመልቀቅ አካባቢን ይበክላሉ፤ ከፍተኛ የድምጽ ብክለት ይፈጥራሉ፣ የመኪና አደጋ የመፍጠር ሚናቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ከዚህም በላይ የአረንጔዴ ልማት ኢኮኖሚ ፖሊሲን ስለሚፃረሩ መንግሥት ትኩረት ሊሰጠው ይገባል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ችግር እንዳለባቸው ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “የውጭ ምንዛሪ ችግር የለብንም፤ ምክንያቱም እኛ ወኪል ሳንሆን በ160 አገሮች ቅርንጫፍ ያለው የቻይናው ሊፋን ግሩፕ አካል ነን፡፡ ስለዚህ የውጭ ምንዛሪ እጥረት ሲኖር፣ ሌሎች ድርጅቶች ከ6 እስከ 8 ወር ሲጠብቁ፣ እኛ ከ15 ቀንና ቢበዛ ከሁለት ወር በላይ አንጠብቅም፡፡ ትንሽ ችግር የገጠመን በኤክሳይዝ ታክስ ነው፡፡

ለእኛ የተለየና ስሌቱም ግልጽ ስላልሆነ ትንሽ ቅሬታ ፈጥሮብናል፡፡ ነገር ግን ከገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት፣ ከኢንዱስትሪና ከውጭ ሚ/ር መ/ቤቶች ጋር እየተነጋገርንና እየተወያየን ስለሆነ በቅርቡ ውሳኔ እንደሚያገኝ ተስፋ አለኝ” ብለዋል፡፡ የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች እየበዙ ስለሆነ ውድድሩን እንዴት ለመቋቋም እንዳሰቡ ተጠይቀው፤ “የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች መጨመር አያስጨንቀንም፡፡ ምክንያቱም፣ አንደኛ በኢትዮጵያ ገበያ ለመቆየት ወስነን ከፍተኛ ካፒታል እያፈሰስን ነው፡፡ ሁለተኛ፣ በዘመናዊ መኪና ደረጃ ሊፋን ኢትዮጵያ ገበያ ውስጥ በመግባት የመጀመሪያው ብራንድ ነን፡፡ ከሌላ ኩባንያ ጋር ሆነን ኢትዮጵያ የገባነው በ2007 ቢሆንም ከ2009 ጀምሮ ለብቻችን መገጣጠም በመጀመር፣ ከሕዝቡ፣ ከደንበኞችና ከመንግሥት ጋር እንዴት መሥራት እንዳለብን የ7 ዓመት ልምድ አካብተናል፡፡ “ሌላው ደግሞ መኪና መሸጥ ብቻ ሳይሆን ከሽያጭ በኋላ የእኛን ያህል ሰርቪስ የሚሰጥ እንደሌለ ደንበኞቻችን ይመሰክራሉ፡፡ ለሰርቪስ ከሚያስፈልጉ ነገሮች አንዱ መለዋወጫ ነው፡፡ ምንም ዓይነት እጥረት እንዳያጋጥም ለመለዋወጫ 10 ሚሊዮን ብር መድበናል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ደንበኞቻችን ይመርጡናል ብለን እናምናለን” በማለት አስረድተዋል፡፡

Read 3756 times