Saturday, 20 September 2014 10:37

የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት እና ኢትዮጵያ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

           የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በአዲስ አበባ ሲያካሂድ የቆየውን የ10 ቀናት ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባዔው ዛሬ ያገባድዳል፡፡ ፕሬዝዳንቱ ኢሳ ሃያቱ ያለፈውን ሳምንት ከጉባኤው ጎን ለጎን የተለያዩ የጉብኝት ፕሮግራሞች ነበራቸው፡፡ ከሳምንት በፊት ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር በመገናኘት ውይይት አድርገዋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ የእድገት እንቅስቃሴዎች እና የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀት ባላት ሁኔታ ያተኮር ነበር፡፡ በውይይቱ የተሳተፉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ ማዘጋጀት እንደምትችል ሲያስረዱ፤ ኢሳ ሃያቱ በበኩላቸው ኢትዮጵያ መስፈርቱን አሟልታ ብታዘጋጅ ደስተኛ ነኝ ብለዋል፡፡

የአህጉሪቱን ታላቅ የስፖርት መድረክ ማዘጋጀት ክብር እንደሆነ የገለፁት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአፍሪካ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ ቤታችሁ ነው ሲሉ ለካፍ ፕሬዝዳንት ነግረዋቸዋል፡፡ ካሜሮናዊው ኢሳ ሃያቱ ባለፈው ሃሙስ ደግሞ ከአፍሪካ ህብረት የወቅቱ ፕሬዝዳንት ንኮሳዛና ዳላሚኒ ዙማ ጋር ስብሰባ የነበራቸው ሲሆን በአዲስ አበባ የሚገኘውን የካፍ እግር ኳስ አካዳሚም ጎብኝተዋል፡፡ ኢትዮጵያ በመስተንግዶው፣ በትራንስፖርት አቅርቦት፤ በፀጥታና ደህንነት ብቁ ብትሆንም የጐደሉት ስታድዬሞች ነው፡፡ የአዲስ አበባ እና የባህር ስታድዬሞች ውድድሩን ለማስተናገድ የሚበቁ መሆናቸውን የተናገሩት የእግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ጁነዲን ባሻ ናቸው፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክልልሎች እየተገነቡ ያሉ ስታድዬሞች በግንባታቸው የመጨረሻ ምእራፍ ላይ እንደሚገኙ በመግለፅ የኢትዮጵያ መንግስት ውድድሩን ለማዘጋጀት የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል ብለዋል፡፡

የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ የ2017 31ኛው አፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት ባይፈቀድልን በ2019 እና በ2021 እኤአ የሚካሄዱት 32ኛው እና 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫዎችን ለማስተናገድ እንጠይቃለን ብለዋል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በአዲስ አበባ ዓመታዊ ጉባኤውን ሲያካሂድ በሴቶች እግር ኳስ፤ በአህጉራዊ ተቋም የማህበረሰብ ድጋፍ እንቅስቃሴዎች፤ በማርኬቲንግ እና የቴሌቭዥን ስርጭት ዙርያ፤ በቻን ውድድር ዝግጅቶች፤ በፉትሳል እና የባህ ዳርቻ ላይ የእግር ኳስ ውድድሮች ላይ ተከታታይ ስብሰባዎችን አድርጓል፡፡ በ2019 እና በ2021 እኤአ ለሚደረጉት 32ኛው እና 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫዎች ለማዘጋጀት ፍላጎት ያላቸው እያንዳንዳቸው በ30 ደቂቃ ገለፃቸው ተፎካክረዋል፡፡ አምስቱ ተወዳዳሪ አገራት አልጄርያ፤ ካሜሮን፤ ጊኒ ፤አይቬሪኮስት እና ዛምቢያ ናቸው፡፡ የሁለቱ አፍሪካ ዋንጫዎች አዘጋጆች የኮንፌደሬሽኑ አባል አገራት በሚያካሂዱት ምርጫ ዛሬ ይገለፃሉ፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በ2017 እኤአ ላይ ለሚደረገው 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫን ሊቢያን በመተካት ስለሚያዘጋጀው አገር ለሚወስነው ውሳኔ ማመልከቻ የሚገባበት ቀን 10 ቀን ቀርቶታል፡፡ ውሳኔው መቼ እንደሚተላለፍ ግን የታወቀ ነገር የለም፡፡

ይህን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት 9 አገራት አመልክተዋል፡፡ ኢትዮጵያ፤ ግብፅ፤ ጋና፤ ማሊ፤ ዚምባቡዌ፤ ኬንያ ለብቻዋ እና ከኡጋንዳ ሩዋንዳ እና ከታንዛኒያ ጋር በመጣመር መስተንግዶውን ጠይቀዋል፡፡ ኢትዮጵያና ተፎካካሪዎቿ የአፍሪካ ዋንጫን ከመሰረቱት አገራት አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በ1962 እኤአ ላይ 3ኛውን፤ በ1968 እኤአ 6ኛውን እንዲሁም በ1976 እኤአ ላይ 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ማዘጋጀቷ ይታወቃል፡፡ ለማስተናገድ እየጠየቀች ያለችው ለ4ኛ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማካሄድ ነው፡፡ኢትዮጵያ በ10 የአፍሪካ ዋንጫዎች ተሳትፎ አድርጋ አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ሁለት ጊዜ ሶስተኛ ደረጃ እንዲሁም ለአምስት ጊዜ ለግማሽ ፍፃሜ መድረስ ችላለች፡፡የምዕራብ አፍሪካዋ አገር ማሊ የተሟላ መሰረተ ልማቶች ስላሉኝ ውድደሩን ማስተናገድ ይገባኛል ትላለች፡፡ ኬንያ ደግሞ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማዘጋጀት ሁለት አማራጮች ይዛ ነው የቀረበችው፡፡ አንደኛው አማራጭ ውድድሩን በተናጠል ማስተናገድ ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ ደግሞ ከምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰብ አባል አገራት ሩዋንዳ፤ ኡጋንዳ እና ታንዛኒያ ጋር ለጣምራ አዘጋጅነት ማመልከቷ ነው፡፡

የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ይህን በጣምራ የማዘጋጀት ፍላጎት ከሳምንታት በፊት ይፋ ሲያደርጉ ከሩዋንዳ እና ከኡጋንዳ ፈጣን ምላሽ አላገኙም ነበር፡፡ ታንዛኒያም በተናጠል የማዘጋጀት ፍላጎት ነበራት፡፡ በ2002 እኤአ ላይ የማዘጋጀት እድል ተሰጥቷት መሰረተልማቶቿን በሚያስፈልገው የጊዜ ገደብ ባለማጠናቀቋ እድሏ በጣምራ ውድደሩን ላዘጋጁት ናይጄርያ እና ጋና ተላልፎባት ነበር፡፡ በ2010 እኤአ ላይ የአፍሪካ ዋንጫውን ለማዘጋጀት ተወዳድራም በድጋሚ አልተሳካላትም፡፡ ዘንድሮ ግን ዚምባቡዌ በ2017 እኤአ ላይ የአፍሪካ ዋንጫን ማስተናገድ ይገባኛል ብላ በከፍተኛ ደረጃ ዘመቻ እያደረገች ነው ከተሳካላት በ2034 እኤአ ላይ የዓለም ዋንጫን በአፍሪካ ምድር ለሁለተኛ ጊዜ እንዲስተናገድ እንቀሳቀሳለሁ የሚል እቅዷን ይፋ አድርጋለች፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት የአፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት የሚፈልጉ አገራት የማሸነፍ ከፍተኛ እድል እንዳላቸው የተወራላቸው የመስተንግዶ ፍላጎታቸውን የገለፁት ጋና እና ግብፅ ናቸው፡፡ በቂ ስታድዬሞች፤ ምቹ ትራንስፖርት እና የእግር ኳስ እድገት ያላት ጋና ቅድሚያ ግምት ተሰጥቷታል፡፡

በአንፃሩ በአፍሪካ ዋንጫ ስኬታ ግንባር ቀደም የሆነችው ግብፅ እንደጋና ሁሉንም መስፈርት በሟሟላት ለፉክክሩ ብትቀርብም በፀጥታ ችግር የመመረጥ እድል እንደማይኖራት ይገለፃል፡፡ እነማን አዘጋጆች ነበሩ የአፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከላይ ከተዘረዘሩት አገራት አዘጋጁን የማይመርጥ ከሆነ በምትክነት ውድድሮችን የማስተናገድ እድል ያላትን ደቡብ አፍሪካ ሊመርጥ እንደሚችል ይገለፃል፡፡ባለፉት 60 ዓመታት የተካሄዱትን 29 የአፍሪካ ዋንጫውን አንዴና ከዚያም በላይ ለማዘጋጀት የቻሉት 18 አገራት ናቸው፡፡ እኩል አራት ግዜ በማዘጋጀት የመጀመርያውን ስፍራ የሚወስዱት ግብፅ እና ጋና ናቸው፡፡ እያንዳንዳቸው ሶስት ጊዜ ማስተናገድ የቻሉት ሁለት አገራት ደግሞ ኢትዮጵያ እና ቱኒዚያ ናቸው፡፡ እያንዳንቻቸው ሁለት ጊዜ የውድደሩ አዘጋጅ በመሆን ደግሞ 4 አገራት ናይጄርያ፤ ሞሮኮ፤ ደቡብ አፍሪካ እና ሱዳን ተሳክቶላቸዋል፡፡ 10 አገራት ደግሞ የአፍሪካ ዋንጫን አንድ ጊዜ ያዘጋጁ ሲሆን እነሱም አልጄርያ፤ አንጎላ፤ ቡርኪናፋሶ፤ ካሜሮን፤ አይቬሪኮስት፤ ኢኳቶርያል ጊኒ፤ ጋቦን፤ ማሊ፤ ሴኔጋል እና ሊቢያ ናቸው፡፡

የአፍሪካ ዋንጫ እንዴት ይዘጋጃል? የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት ብቁ የሚላቸው አገራት በሆቴል እና መስተንግዶ፤ ቢየያንስ አራት አለም አቀፍ ደረጃ የጠበቁ ስታድዬሞች ከእነ ልምምድ ስፍራቸው፤ በቂ የአየር እና የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎት፤ አስተማማኝ ደህንነት እና ፀጥታን በዋና መስፈርቶቹ ይመለከታል፡፡ በ2013 እኤአ ላይ ደቡብ አፍሪካ ያዘጋጀችው 29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት መራቅ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ የተሳተፈችበት ነበር፡፡ ደቡብ አፍሪካ ይህን አፍሪካዋንጫ ያዘጋጀችው ለዓለም ዋንጫ ያቀረበቻቸው መሰረተ ልማቶችና ልምዶች በቂ በመሆናቸው ነበር፡፡ ሊቢያ በነበራት የፀጥታ ጉድለት ከውድድሩ አዘጋጅነት ተሰርዛ ደቡብ አፍሪካ መተካቷ የተሳካ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ከ38 ዓመት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲሁም በታሪክ ለአራተኛ ጊዜ ማስተናገድ ብትችል ከደቡብ አፍሪካ መሰናዶ ብዙ ልትማር ያስፈልጋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ለ2010 ለዓለም ዋንጫ የነበሩ እና ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የአዘጋጅ ኮሚቴ የቦርድ አባላት በማሰባሰብ ውድድሩ ከመዘጋጀቱ ቢያንስ ለ2 ዓመት ተንቀሳቅሳለች፡፡ ይሄ ብሄራዊ የአዘጋጅ ኮሚቴ ሚኒስትሮች፤ ዲኤታዎች፤ ባለሃብቶች፤ ታዋቂ ሰዎች፤ ትልልቅ እና ባለታሪክ ስፖርተኞች እና ሌሎችንም ያካተተ እና እስከ 30 አባላት በቦርድ አባልነት የሰሩበት ነው፡፡ ከዚሁ ቦርድ ስር ደግሞ ቢያንስ አምስት የተለያዩ ኮሚቴዎች ይኖራሉ፡፡

የውድድር አካሄድን፤ ፀጥታ እና ደህንነትን፤ የፋይናንስ ጉዳዮችን፤ የማርኬቲንግ እና የንግድ ተግባራትን፤ የሰው ሃይል ምደባን፤ የሆቴል እና የትራንስፖርት አቅርቦትን እንዲሁም የሚዲያ እና የዓለም አቀፍ ግንኙነትን ያንቀሳቅሳሉ፡፡ ደቡብ አፍሪካ 29ኛውን አፍሪካ ዋንጫ ስታስተናግድ ከመንግስት የበጀት ድጋፍ፤ ከካፍ የገንዘብ አስተዋፅኦ፤ ከስፖንሰርሺፕ እና ከተለያዩ የንግድ እንቅስቃሴዎች ገቢ ነበረው፡፡ የውድድር ማካሄጃ፤ የአስተዳደር ስራዎች፤ የጉዞ እና የሆቴል አገልግሎት እና ሌሎች ተግባራትን በማከናወን ወጭዎች ይኖሩታል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ አገር 6.2 ሚሊዮን ዶላር ያበረክታል፡፡ በሁሉም አዘጋጅ ከተሞች የውድድሩ ብሄራዊ ኮሚቴ አብሮ የሚሰራበት ምክር ቤት፤ ከአምስት በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር ተፈራርመው የሚሰሩ የመንግስት ተቋማት፤ ለ16 ብሄራዊ ቡድኖች በአዘጋጅ ከተሞች ሙሉ የስልጠና ሜዳ እና ከስታድዬም ከ5 እስከ ሰላሳ ደቂቃ ጉዞ ያላቸው የማረፊያ ሆቴሎች፤ዓለም አቀፍ ደረጃ ያሟሉ ቢያንስ አምስት ስታድዬሞች፤ ከ200 በላይ ከብሄራዊ ኮሚቴው ጋር የሚሰሩ ሰራተኞች፤ ከ2500 በላይ ውድድሩን የሚያስተናግዱ በጎፍቃደኞች ፤የውድድሩ ኦፊሴላዊ ድረገፅ ፤ ውድድሩን የሚገልፅ መርህ ፤ የውድድሩ መለያ የሆነ ምልክት እና ሎጎ፤ በከፍተኛ ደረጃ ውድድሩን የሚያስተዋውቁ ባነሮች፤ ቢልቦርዶች እና ፖስተሮችም አንድ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ አገር በተሰካ መንገድ ለማስተናገድ የሚያከናውናቸው ስራዎች መሆናቸውን በደቡብአፍሪካ የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሪፖርት መረዳት ይቻላል፡፡ አፍሪካ ዋንጫን በማስተናገድ ለሌሎች አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የስፖርት መድረኮች በቂ ተመክሮ እና አቅም ይገነባል፡፡ የስፖርቱን አስተዳደር ሁለገብ አቅም ያሳድጋል፡፡ አለም አቀፍ ትኩረት ይገኝበታል፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ምክንያት ይሆናል፡፡ የስፖርት እድገትን ለማቀላጠፍ ያግዛል፡፡

Read 4728 times