Saturday, 13 September 2014 13:42

አገኘሁ አዳነ - ጣምራ ጠቢብ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

         ተወልዶ ያደገው ጎንደር ነው፡፡ በአባቱ የሥራ ጸባይ ምክንት በልጅነቱ አሥመራን፣ አቆርዳትን፣ ተሰኔን ጨምሮ ወደተለያዩ አካባቢዎች ተጉዟል፡፡ እናቱ በልጅ አስተዳደግ በጣም ጥብቅ በመሆናቸው ከቤት እንዲወጣ የሚፈቀድለት ወይ ወደ ትምህርት ቤት፣ ወይ ወደ ቤተክርስቲያን ብቻ ነበር፡፡ ያንን ዘመን ሲያስታውስ በኪነ ቅብ ሥራዎች ያሸበረቀችውን ሎዛ ማርያም ቤተክርስቲያንን ያነሳል፡፡ ዓይኑም ልቡም፣ ቀልቡም በሥዕል ሕብረ ቀለም የተወጋው ያኔ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ከዚያ ሕፃናት አምባ ገባ፡፡ አምባ የፈለግከውን ለመሆን ነገሮች የተመቻቹበት፣ ነፃነት ያለበት አካባቢ እንደነበር ይናገራል፡፡ አጥር ተበጅቶለት ላደገው አገኘሁ ሕፃናት አምባ የተመቸ ሥፍራ ሆነለት፡፡ አንድ ቦታ ላይ በትኩረት መቆየትን፣ ማንበብን፣ ማስተዋልን ቀድሞ ስለሚያውቃቸው በመጣበት መንገድ ቀጠለ፡፡ ለዛሬ ማንነቱ ያ ዘመን እርሾ እንደሆነውም አይጠራጠርም፡፡
ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ከመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት አንስቶ ሥዕልን ይሞክር ነበር፡፡ ዕድለኛም ስለነበር ከልጅነቱ ምርጥ ምርጥ የሚባሉ መምህራን ገጥመውታል፡፡
አገኘሁ ከልጅነቱ ጀምሮ ጠያቂ ባህሪይ እንደነበረው ያስታውሳል፡፡ አራተኛ ክፍል እያለ የሥዕል መምህሩ በውሃ ቀለም ይሥላል፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ አገኘሁ ያየውን ማመን አልቻለም፡፡ እጅጉን ተደነቀ፡፡
“የሚገርም ዓይነት፣ ዓይኑ እሳት የሚተፉ ጥቁር ሰውዬ ሳለ፡፡ ‘እንዴት ውሃ ሰው ይሆናል?’ ‘እንዴት ከሰው ዓይን እንደዚህ ዓይነት ኃይል የበዛበት ብርሃን ይረጫል?’ ስል በመደነቅ የጠየኩትን መቼም አልረሳውም፡፡”
የአገኘሁ ውስጣዊ ፍላጎት፣ ተሰጥዖውና ችሎታው እንዳለ ሆኖ ህፃናት አምባ ያንን የሚያለመልም ውሃ፣ አፈር እና ብርሃን እንደሆነው ይጠቅሳል፡፡ አገኘሁ ራሱን ወደ መንፈሳዊ ሰው አስጠግቶ ያስባል፡፡ ከአራት ማዕዘን ግድግዳ ውጪ ያለን ነገር የሚናፍቅ፣ በገሃድ የሚታይ፣ የሚጨበጠው የሚሰለቸው ዓይነት ሰውም ይመስላል፡፡
ሠዓሊነቱን ሳይቀር ወደዚ ቢወስደው ይወዳል፡፡ “ከሚዳሰስ እውነት ነገረ-ተረትን፤ ከዕለት ዜና ተረትን ልወድ እችላለሁ፡፡ ያለቀና የሚያልቅ ነገር ይሰለቸኛል፡፡ አገኘሁ ሠዓሊ ብቻ አይደለም፡፡ ገጣሚም ነው፡፡ “ጨለማን ሰበራ” እና “ለምን?” የተሰኙ ሁለት መድበሎች አሳትሟል፡፡ በባህርይው ማዳመጥ ደስ እንደሚለው የሚናገረው አገኘሁ አለማዊ ሰው ባይሆንም ይመስላል፡፡
“ሰውን ብደግፍ፤ ክርስቶሳዊ ስብዕና ቢሮረኝ እወዳለሁ፡፡ ማለም፣ ከሃሳብ ጋር መጫወት ደስ ይለኛል፡፡” ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ስፔይንን፣ ሆላንድን፣ ፈረንሳይን፣ ጀርመንን ፖርቹጋልን እና ቤልጂየምን ገብኝቷል፡፡ በነበረው ቆይታም ብዙ ነገሮችን ስለመማሩ ይናገራል፡፡
“በራሴ ፍጹምነት ታስሬ እንደነበር ተገንዝቤአለሁ፡፡ ለምለሚቷ ሀገሬ የሚለውን ሳይቀር ቀንሼአለሁ፡፡ ምክንያቱም በሌላው ሀገር ሃሪፍ ነገር ስላለ፡፡” ሠዓሊ አገኘሁ ባለትዳር እና የሦስት ልጆች አባት ነው፡፡ ቤተሰቦቹ ለሁለመናው ብርታቱ እንደሆኑም ይጠቅሳል፡፡
አገኘሁ ከልጅነቱ መምህርነትን ይመኝ ነበር፡፡ እንደፈለገው ግን ፈጥኖ አላገኘውም፡፡ በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች ሲሰራ ቆይቶ ቢዘገይም ከመምህርነት ጋር ተገናኝቷል፡፡ ዛሬ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ ፈለገ ሰላም የሥነ-ጥበብ እና ዲዛይን ት/ቤት መምህር ነው፡፡ ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ወደፊት ወደ መፈውሰ ጥበብ ወይም ‘Art Therapy’፣ ‘Physical Therapy’፣ ‘Spritual Therapy’ ቢገባ ደስ እንደሚለው፣ ሥዕሉንም ቢሆን ከሰው ልጅ ጋር በቀጥታ እንዲገናኝ ማድረግ ቢችል ደስ ይለዋል፡፡
ምንጭ፡- ነቢይ ግርማ፣ “ጋለሪያ ቶሞካ አገኘሁ አዳነን ያቀርባል” (2007 ዓ.ም) በሚለው መጽሄት ላይ ያሰፈረው፡፡

Read 1645 times