Saturday, 13 September 2014 13:41

“ፊውቸር ሜሞሪስ” በሚል ርዕስ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ይካሄዳል

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(1 Vote)

  በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት፤ “ፊውቸር ሜሞሪስ” በሚል ርዕስ ከመስከረም 6 እስከ 8 2007 ዓ.ም ዓለም አቀፍ ጉባኤ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ አሻግሬ ጉባኤውን ከጀርመኑ “ifa-institute for International Cultural Relation” ጋር በመተባበር ማዘጋጀታቸውን ጠቅሰው፣ የገንዘብ ድጋፍ ያደረገላቸው ደግሞ የጀርመን ፌደራል የውጭ ጉዳይ ጽ/ቤት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በሦስት ቀኑ ጉባኤ፣ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት በሥነ-ጥበብ ላይ የሚሰሩ 23 የዘርፉ ባለሙያዎች፣ የሥነ-ጥበብ ለባህላዊ ትውስታና ለእድገት በሚያበረክተው አስተዋፅኦና በወደፊት የከተሞች ገጽታ ላይ በሚኖረው እውነታ ላይ እንደሚወያዩ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡
ከውጭ አገራት የሚመጡትና የአገር ውስጥ የሥነ-ጥበብ ባለሙያዎች እንዲሁም፣ ጉዳዩ ያገባናል የሚሉ የህዝብ ተቋማት፣ “በተለያዩ የሥነ-ጥበብ ውበቶች ወይም ባህላዊ መለያዎች (ቅርፆች) ላይ በምን ነጥቦች ነው መወያየትና መደራደር የሚቻለው? የሥነ-ጥበብ ልምዶች አዲስ ቅርፅ፣ ህዝባዊ ባህል ወይም የወደፊት ትውስታ መፍጠር ይችላሉ? ከቻሉስ እንዴት?” በሚሉና ከተለያዩ አመለላከቶች በሚነሱ ነጥቦች ላይ ይወያያሉ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ፈጣን የአቀማመጥ ለውጥ፣ ከሥነ-ሕንፃ፣ ከማኅበራዊና ከከተማ ለውጥ አንፃር እንዴት ይታያል? ለሚሉ የሥነ-ጥበብ መሰረታዊ ቅሬታዎች (ያለመግባባቶች) ምላሽ እንደሚሰጡም ይጠበቃል፡፡
ጉባኤተኞቹ በመዲናዋ ውስጥ ያሉ የሥነ-ጥበብ ሥፍራዎችን እንደሚጎበኙ፣ተለያዩ ምሁራን ንግግር እንደሚያደርጉና፣የሥነ-ጥበብ፣የቅርስና የሙዚየም ባለሙያዎች ጥናታዊ ጽሑፎች እንደሚያቀርቡም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Read 1356 times