Saturday, 13 September 2014 13:38

የሠዓሊ አገኘሁ “ቃልና ምስል” በቶሞካ እየታየ ነው

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(0 votes)

    ትላንት ምሽት በጋለሪያ ቶሞካ የተከፈተው የሰዓሊ አገኘሁ አዳነ “ቃልና ምስል” የተሰኘ የሥዕል ትርኢት ለሁለት ወር ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ተገለፀ፡፡ በቶሞካ ቤተ ሥዕል ማሳያ የቀረበው “ቃልና ምስል”፤ በድብልቅ ቁስ ጥበባት የተሰሩ የኪነ - ህትመትና የኪነ ቅብ ሥራዎች እንደሆኑ ትርኢቱን ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀው አነስተኛ መጽሔት ይጠቁማል፡፡
በመጽሔቱ ላይ “ቃልና ምስል፤ ምስልና ቃል” በሚል ስለ ሰዓሊው ስራዎች ማብራሪያ የፃፈው ሰዓሊ ጥሩነህ እሸቱ፤ “ለሰዓሊና ገጣሚ አገኘሁ አዳነ ሥነግጥማዊ ቃልና ሥዕላዊ ምስል ‹ነፍስና አካል፤ ቃልና ሥጋ› ናቸው፤ አይለያዩም፤ አይነጣጠሉም” ብሏል - ጣምራ ጠቢብነቱን ሲገልፅ፡፡
ሰዓሊው የስዕል ትርኢት በግሉ ሲያቀርብ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አንዱን በስፔን ማቅረቡ ተፀቁሟል፡፡ ሰዓሊ አገኘሁ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ ፈለገ ሰላም የሥነ ጥበብ እና ዲዛይን ት/ቤት መምህር ሲሆን፣ “ጨለማ ሲበራ” እና “ለምን?” የተሰኙ የግጥም መጻሕፍት ማሳተሙ ይታወሳል፡፡

Read 1705 times