Saturday, 13 September 2014 12:52

ዶ/ር ዳኛቸው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ሊከስሱ ነው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(4 votes)

      በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ የዩኒቨርሲቲው የአመት ፍቃድ አሰጣጥን በተመለከተ የተፈጠረው አለመግባባት ሊፈታ ባለመቻሉ በመ/ቤታቸው ላይ ክስ ሊመሰርቱ እንደሆነ ተናገሩ፡፡
በዩኒቨርስቲው ህጋዊ አሠራር መሰረት 6 አመት ያስተማረ አንድ አመት ፍቃድ የሚሰጠው ቢሆንም የጠየቁት ፍቃድ ከተሰጣቸው በኋላ መነጠቃቸውን የገለፁት ዶ/ር ዳኛቸው፤ አቤቱታቸውን እስከ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ድረስ ለሚመለከታቸው ሁሉ ቢያቀርቡም ምላሽ እንደተነፈጋቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“በአሜሪካ የሚገኙት ቤተሰቦቼ ስለናፈቁኝ እነሱን ሄጄ ማየት እፈልጋለሁ” ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ከዚህ በኋላ መብታቸውን ለማስከበር ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት መውሰድ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው ባለፈው ዓመት ሚያዚያ ወር ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ “እድሜህ ስልሳ አመት ስለሞላና የጡረታ ሂደቱ በደንብ ተካትቶ ፋይልህ ውስጥ ስለሌለ የአመት ፍቃድህን ሠርዘነዋል” እንደተባሉ ገልፀው የነበረ ቢሆንም ከኮንትራት ውልና ከደሞዝ እግድ ጋር በተያያዘ ከዩኒቨርስቲው ጋር የነበራቸው ውዝግብ እልባት ማግኘቱን መናገራቸው ይታወሳል፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው በኢህአዴግና በመንግስት አሰራር ላይ የሰላ ትችት በመሰንዘር የሚታወቁ ምሁር ቢሆኑም የማስተማር ሥራዬን ሳላቆም የየትኛውም ፓርቲ አባል መሆን አልፈልግም በሚል ራሳቸውን ከፓርቲ ፖለቲካ አግለው መቆየታቸው ይታወቃል፡፡

Read 3984 times