Saturday, 13 September 2014 12:47

ባለ 5 ኮከቡ ‘ክራውን ፕላዛ’ ሆቴል ከ18 ወራት በኋላ ይከፈታል

Written by 
Rate this item
(6 votes)

የአለማቀፉ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴሎች አካል ነው

በሆቴል ኢንዱስትሪ ዘርፍ በአለማቀፍ ደረጃ በስፋት በመንቀሳቀስ ከሚታወቁ ታላላቅ ኩባንያዎች አንዱ የሆነው የእንግሊዙ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ፣ በአፍሪካ ከከፈታቸው ሆቴሎቹ 30ኛው እንደሚሆን የሚጠበቀውን ክራውን ፕላዛ የተሰኘ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል በአዲስ አበባ እንደሚከፍት ቬንቸርስ አፍሪካ ዘገበ፡፡
የሆቴሉ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ረዘነ አያሌው በበኩላቸው፣ የሆቴሉ ግንባታ በ18 ወራት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
አለማቀፍ ደረጃን የጠበቀው ይህ ዘመናዊ ሆቴል፣ ደረጃቸውን የጠበቁ የመኝታ ክፍሎችን፣ ዘመናዊ ሬስቶራንቶችን፣ መዋኛ ገንዳና ሰባት ግዙፍ የስብሰባ አዳራሾችን ጨምሮ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ክፍሎች ይኖሩታል ተብሏል፡፡
የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ የህንድ፣ የመካከለኛው ምስራቅና የአፍሪካ ዋና ስራ አስፈጻሚ ፓስካል ጎቪን እንዳሉት፣ በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለው ይህ ሆቴሉ በከተማዋ የሚደረገውን በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ላይ ያለውን የቱሪስቶችና የውጭ አገራት ዜጎች ፍሰት ታላሚ ያደረገ ነው፡፡
የሆቴሉ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ረዘነ አያሌው ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ በአዲስ አበባ ልደታ ኢትፍሩት አካባቢ የሚከፈተው ክራውን ፕላዛ ሆቴል ግንባታ ተጠናቆ የማጠናቀቂያ ሥራዎች እየተከናወኑ ሲሆን፣ ግንባታው በ18 ወራት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡የሆቴሉ አጠቃላይ ወጪ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ከተጠናቀቀ በኋላ የሚታወቅ ነው ያሉት አቶ ረዘነ፣ እስካሁን ድረስ የዓለም ባንክ ለግንባታው 19 ሚሊዮን ዶላር ማበደሩን ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ ተጠናቅቆ ስራ ሲጀምር፣ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል እንደሚከፍትና እያደገ ለመጣው የአገሪቱ የቱሪስት ፍሰትና ለአለማቀፍ ጉባኤዎች የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተናግረዋል፡፡አለማቀፉ ኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴልስ ግሩፕ፣ ሆቴሎቹን ክራውን ፕላዛ፣ ሆሊዴይ ኢን፣ ሆሊዴይ ኢን ኤክስፕረስ፣ ኢንተርኮንቲኔንታልና ስቴይብሪጅ ስዊትስ በተሰኙ አምስት ታዋቂ መጠሪያዎች በተለያዩ የአለም አገራት በመክፈት የሚታወቅ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በ12 የአፍሪካ አገራት 29 ሆቴሎች አሉት፡፡

 

Read 5378 times Last modified on Saturday, 13 September 2014 15:16