Saturday, 06 September 2014 10:46

ለአዲስ ዓመት ዋዜማ የሙዚቃ ድግሶች ተዘጋጅተዋል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ዋዜማውን የት ለማሳለፍ አስበዋል?

በዘንድሮ የአዲስ ዓመት ዋዜማ ከቀድሞ ዓመታት በተለየ በርካታ የሙዚቃ ድግሶች እንደተዘጋጁ ያሰባሰብናቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ጃኪ ጎሲና አንጋፋው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ታደሰ ረቡዕ ምሽት በዋዜማው ታዳሚውን በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚያዝናኑ ይጠበቃል፡፡ አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴም በምሽቱ ዝግጅት ላይ የሚያቀነቅን ሲሆን “የተመስገን ልጆች” የባህል ውዝዋዜ ቡድን የኮንሰርቱ አካል እንደሆኑ ታውቋል፡፡ ኮንሰርቱን ለመታደም ቀደም ብለው ትኬት ለሚገዙ 500 ብር፣ በእለቱ በር ላይ በእለቱ ለመግዛት 600 ብር ነው ተብሏል፡፡ የቪአይፒ ትኬት 1500 ብር ሲሆን እራትን ይጨምራል፡፡
ሃርመኒ ሆቴል
ከኤድናሞል ዝቅ ብሎ በሚገኘው ሃርመኒ ኢንተርናሽናል ሆቴልም ለአዲስ ዓመት ዋዜማ ትልቅ የሙዚቃ ድግስ ተዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ድግስ ላይ ዋዜማውን የሚያደምቁት የጃኖ ባንድ አባላት ናቸው ተብሏል፡፡ በዚህ ድግስ ላይ ለመታደም ብቻዎን ከሄዱ በሰባት መቶ ብር የፍቅር ወይም የትዳር አጋርዎን ከያዙ ደሞ በ1200 ብር ይዝናናሉ፡፡
ሒልተን ሆቴል
በቅርቡ ስሙን ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ድርጅት ወደ ኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የቀየረው EBC፤ በዋዜማው ዕለት ከሒልተን በቀጥታ የሚያስተላልፈው የመዝናኛ ዝግጅት እንዳለው ታውቋል፡፡ በዋዜማ ዝግጅቱ ላይ እነማዲንጎ አፈወርቅ፣ ሃመልማል አባተ፣ ኤፍሬም ታምሩ፣ ንዋይ ደበበ፣ ማህሌት ገ/ጊዮርጊስ፣ ዘውዱ በቀለ፣ ሃይሉ ፈረጃና ሌሎች በርካታ አንጋፋና ወጣት ድምፃዊያን ይሳተፉበታል ተብሏል፡፡ በዚህ የዋዜማ ፕሮግራም የመግቢያ ክፍያ እንደሌለና እንግዶች በጥሪ ካርድ እንደሚገቡ ታውቋል፡፡  
ካፒታል ሆቴል
ከኡራኤል ወደ 22 በሚወስደው መንገድ ላይ የሚገኘው ካፒታል ሆቴልና ስፓ እንዲሁ ትልቅ የዋዜማ የሙዚቃ ድግስ ያዘጋጀ ሲሆን ምሽቱ በመሃሪ ብራዘርስ ባንድ ይደምቃል ተብሏል፡፡ በዚህ ምሽት አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴ ሥራዎቹን የሚያቀርብ ሲሆን መግቢያ 1300 ብር ነው፡፡
ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴል
ሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ የሚገኘውና በዓመቱ መጀመሪያ ላይ አካባቢ ስራ የጀመረው ባለ አራት ኮከቡ ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴልም ለአዲሱ ዓመት ዋዜማ የሙዚቃ ድግስ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ምሽት ገነነ ሃይሌ፣ የባህል ዘፋኙ ግዛቸው እሸቱ፣ ፀጋዬ ስሜ (ሆሴ ባሳ) እና ሌሎችም የትግርኛና ጉራጊኛ ዘፋኞች የበዓል ዋዜማውን አድምቀውት ያመሻሉ፡፡ መግቢያው 380 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡
ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽ
በአዲስ አበባ ከኢምፔሪያል አደባባይ ወደ 17 ጤና ጣቢያ በሚወስደው መንገድ የተገነባውና ባለፈው ቅዳሜ የተመረቀው አዲሱ “ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽ” ደግሞ የፊታችን ሐሙስ የአዲስ ዓመት ልዩ የሙዚቃና የባህል ዝግጅቶችን እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡

Read 3776 times