Saturday, 06 September 2014 10:41

ኢትዮጵያ ባለፈው አመት ከአፍሪካ አነስተኛ ሙስና የተሰራባት አገር ናት ተባለ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

          ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም እ.ኤ.አ በ2013 በአለም ዙሪያ በሚገኙ 95 አገራት በሰራው ጥናት፣ ባለፈው አመት ከአፍሪካ አህጉር አነስተኛ ሙስና የተሰራባት አገር ኢትዮጵያ እንደሆነች ማስታወቁን የኬንያው ዘ ስታር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ አልጀዚራ በበኩሉ ትናንት ባወጣው ዘገባ፣ በኢትዮጵያ ንጹህ የመጠጥ ውሃ ማግኘት ቅንጦት ነው ብሏል፡፡
የአገራትን ዜጎች አስተያየትና ሌሎች መስፈርቶችን በመጠቀም ባወጣቸው የሙስና መለኪያዎች በ6 በመቶ ነጥብ ያገኘችው ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገራት አነስተኛ ሙስና ያለባት አገር እንደሆነች የገለጸው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል፣ ዴንማርክ፣ ፊላንድ፣ ጃፓንና አውስትራሊያም በተመሳሳይ ሁኔታ 1 በመቶ ነጥብ ይዘው በአለማችን አነስተኛ ሙስና ያለባቸው አገሮች መሆናቸውን በጥናቱ ማረጋገጡን ይፋ አድርጓል፡፡
በሙስና መለኪያዎች 84 በመቶ ውጤት ያገኘችው ሴራሊዮን በአለማችን ከፍተኛ ሙስና የሚፈጸምባት አገር እንደሆነች የገለጸው ተቋሙ፣ ላይቤሪያ፣ የመንና ኬንያ እንደሚከተሏት አስታውቋል፡፡
ከአፍሪካ ሁለተኛዋ አነስተኛ ሙስና ያለባት አገር ሩዋንዳ መሆኗን የገለጸው ተቋሙ፣ በምስራቅ አፍሪካ ከሚገኙ አገራት መካከልም ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያና ሱዳን በቅደም ተከተል ከሁለተኛ እስከ አራተኛ ደረጃ ይዘው እንደሚገኙ ተናግሯል፡፡
አልጀዚራ በበኩሉ ትናንት ለንባብ ባበቃው ዘገባው በኢትዮጵያ ንጹህ የመጠጥ ውሃ ማግኘት ቅንጦት እንደሆነ ገልጾ፣ ምንም እንኳን 52 በመቶ የአገሪቱ ህዝብ የንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት የተሟላለት ቢሆንም፣ የውሃ መስመር ቤታቸው ድረስ የተዘረጋላቸው የአገሪቱ ዜጎች 10 በመቶ ያህሉ ብቻ እንደሆኑ አስረድቷል፡፡በአገሪቱ የገጠር አካባቢዎች ከሚኖሩት ዜጎች የንጹህ የመጠጥ ውሃ ቧንቧ መስመር የተዘረጋላቸው አንድ በመቶ ያህሉ ብቻ እንደሆኑም ገልጧል፡፡የአገሪቱ መንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን ለማስፋፋት ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ ቢሆንም፣ የንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት አሁንም ድረስ በበቂ ሁኔታ አለመሟላቱንና ከፍተና ስራ መስራት እንደሚገባም አስታውቋል፡፡

Read 3105 times