አዲስ አበባ ለወደፊት በኢንቨስትመንት ዘርፍ ተመራጭ የሆኑ የአፍሪካ 10 ቀዳሚ አገራት በሚል ግሎባል ኢኮኖሚ ዎች በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት ውስጥ መካተቷን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ተቋሙ በአህጉሪቱ በቀጣይ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎች ይሆናሉ ባላቸው ከተሞች ዝርዝር ውስጥ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ ኢባዳንና ካኖ የተባሉትን የናይጀሪያ ከተሞች፣ የቡርኪናፋሶዋን ኡጋዱጉ፣ የሴኔጋሏን ዳካር፣ የኬንያዋን ናይሮቢ፣ የኮትዲቯሯን አቢጃኒን፣ የሱዳኗን ካርቱም፣ የአንጎላዋን ሉዋንዳና የታንዛንያዋን ዳሬ ሰላም ማካተቱን ሚኒስቴሩ በድረገጹ ያወጣው መረጃ ያሳያል፡፡
ተጨባጭ የኢንቨስትመንት አማራጭ ያለባቸው ከተሞች በቀጣዮቹ ሁለት አስርት አመታት በእጥፍ ያህል እንደሚያድጉ የተነበየው የተቋሙ ሪፖርት፣ እነዚህ ከተሞች ወደሌሎች አገራት የመስፋፋት ጥረት በማድረግ ላይ የሚገኙ የንግድ ተቋማት ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እንደሚሆኑም አመልክቷል፡፡
በእነዚህ ከተሞች የሚካሄደውን የመሰረተ ልማት አውታሮች የማስፋፋት እንቅስቃሴ በተፋጠነ ሁኔታ አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ያለው ሪፖርቱ፣ የመሰረተ ልማት አውታሮች መስፋፋት በአህጉሪቱ እድገትን ለማፋጠን ቁልፍ ሚና እንደሚጫወትና ማህበረሰቡን ያቀፈ ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ ወሳኝ እንደሆነ ጨምሮ ገልጧል፡፡