Saturday, 23 August 2014 11:34

አዲስ “ስማርት የኤሌክትሪክ ቆጣሪ” በአገር ውስጥ ማምረት ተጀመረ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

       የብሄራዊ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የስማርት ቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑ የኤሌክትሪክ ቆጣሪዎችን አምርቶ ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ማቅረብ የጀመረ ሲሆን ቴክኖሎጂው በሃገር ውስጥ መሰራቱ የሃገር ደህንነትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ፋይዳ አለው ተብሏል፡፡
ከውጭ በከፍተኛ ምንዛሬ የሚገቡትን ቆጣሪዎች ሙሉ ለሙሉ እንደሚያስቀር የተነገረለት የኤሌክትሪክ ቆጣሪ “አይቲ ፕላስ ስማርት ኢነርጂ ሜትር” በመባል የሚታወቅ ሲሆን እስካሁን ከሚሰራበት ቴክኖሎጂ በተሻለ ሁኔታ መስራት የሚችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን ያካተተት ነው ተብሏል፡፡
የብኢኮ ም/ዋና ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄነራል ጠና ቁርንዲ ከትናንት በስቲያ ከስራ ባልደረቦቻቸው ጋር በሒልተን ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት፤ ቆጣሪው የወደፊቱን የቴክኖሎጂ እድገት እያንዳንዱ ቆጣሪ ያለሰው ንክኪ ከዋና ማዕከል ጣቢያ ጋር በርቀት መቆጣጠሪያ እየተገናኘ የሚሰራበት በመሆኑ በኃይል አቅርቦት ላይ ያነጣጠሩ ሃገራዊ የደህንነት ስጋቶችን መቆጣጠርና መከላከል ያስችላል ብለዋል።
ደህንነትን ያስጠብቃል የተባለው የኤሌክትሪክ ቆጣሪው፤ ከንድፉ እስከ ምርት ድረስ በብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን እና በስሩ ባሉት ተቋማት የተፈበረከ ሲሆን የፕላስቲክ ክፍሉ በኢትዮ ፕላስቲክ ኢንዱስትሪ፣ የብረታ ብረት ክፍሉ ደግሞ በብረታ ብረትና ፋብሪኬሽን ኢንዱስትሪ እንዲሁም የተለያዩ ምርቶች በህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ግንባታ ኢንዱስትሪ የተመረተ ነው ተብሏል፡፡ ፋብሪካው ሙሉ ለሙሉ ወደ ስራ ሲገባም በቀን 1200 ቆጣሪዎችን የማምረት አቅም አለው ተብሏል፡፡
የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ ሲስተም ለጦርነት ጥቃት እንደሚውል ይታወቃል ያሉት ምክትል ዳይሬክተሩ፤ ብ/ጄነራል ጠና ቴክኖሎጂው ሙሉ ለሙሉ የሃገር ውስጥ መሆኑ በኃይል ላይ አነጣጥሮ የሚፈፀም የጦር ጥቃትን በቀላሉ ለመቆጣጠር እንደሚያስችል ገልፀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋየር ቢዝነስ ስራ አስፈፃሚ አቶ ቢትወደድ ገ/አሊፍ በበኩላቸው፤ “ቴክኖሎጂው በደንበኛውና በአገልግሎት አቅራቢው መካከል ጥብቅ ቁርኝትን ይፈጥራል፤ ቆጣሪ አንባቢነትን አስቀርቶም ደንበኞች የራሳቸውን ሂሳብ አውቀው በቢል መልክ እንዲከፈሉ ያስችላል” ብለዋል፡፡ ቆጣሪ አንባቢነት ቢቀርም የሚፈናቀል ሰራተኛ አይኖርም፤ ሌሎች ስራዎች ይሰጣቸዋል ሲሉ ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
አዲሱ ስማርት ቆጣሪ በርቀት መቆጣጠሪያ የሚታገዝ በመሆኑም አደጋ ሲያጋጥም በቀላሉ ለዋና ማዕከል መልዕክት ስለሚያስተላልፍ ኃይል በመቀነስ መቆጣጠር ያስችላል፤ ቆጣሪው ንክኪ ሲደረግበት በቀጥታ ለማዕከሉ መረጃ ያቀብላል ተብሏል፡፡
ኢብኮ አንዱን ቆጣሪ በ2500 ብር ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሚያቀርብ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን ቆጣሪው በቅርቡ አገልግሎት ላይ እንደሚውል ተገልጿል፡፡


Read 4824 times