Saturday, 23 August 2014 11:17

በግድቡ ዙሪያ የሚካሄደው የሶስትዮሽ ድርድር ሰኞ ይቀጥላል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ለመምከር ታስቦ በኢትዮጵያ፣ በግብጽና በሱዳን መካከል የተጀመረውና ከስምንት ወራት በፊት ተቋርጦ የነበረው የሶስትዮሽ ድርድር፣ በመጪው ሰኞ በሱዳን ርእሰ መዲና ካርቱም እንደሚቀጥል ኢጅፕት ኢንዲፐደንት ትናንት ዘገበ።
ከግብጽ የመስኖ ሚኒስትር የተገኘውን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ የሶስቱ ሃገራት የውሃ ሚኒስትሮች በሚሳተፉበት በዚህ ድርድር፣ የግብጽ መንግስት በአባይ ወንዝ የመጠቀም ታሪካዊ መብቱን ባስከበረ መልኩ በአገራቱ መካከል ያለውን ወዳጅነት ለማጠናከርና ልዩነቶችን በውይይት ለመፍታት ተዘጋጅቷል፡፡
ድርድሩ ጊዜን የሚፈጅ፣ ተደጋጋሚ ስብሰባዎችን ማካሄድን እንዲሁም የሁሉንም ተደራዳሪ አካላት ፖለቲካዊ ይሁንታና በመተማመን ላይ የተመሰረተ አካሄድ የሚጠይቅ ከባድ ተልዕኮ እንደሚሆን ዘገባው ከሚኒስቴሩ ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ ገልጧል፡፡
የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝና የግብጹ ፕሬዚዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ባለፈው ሰኔ በኢኳቶሪያል ጊኒ በተካሄደው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ በተገናኙበት ወቅት፣ ተቋርጦ የነበረውን የሶስትዮሽ ድርድር እንደገና ማስቀጠል በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ መምከራቸውን ዘገባው አስታውሷል።

Read 1961 times