Print this page
Saturday, 16 August 2014 12:32

የጳውሎስ መልእክት ወደ ኢትዮጵያ ሰዎች

Written by  ኦርዮን ወ/ዳዊት
Rate this item
(8 votes)

ርዕስ- ጳውሎስ ኞኞ (1926-1984)፣
የገፅ ብዛት - ከፎቶና ማጣቀሻ ጽሑፎች ዝርዝር ጋር 308፣
የሽፋን ዋጋ - 84 ብር (24 ዶላር)፣
የህትመት ዘመን - 2006 ዓ.ም
ህትመት - አርቲስቲክ ማተሚያ ድርጅት
ጸሐፊ - ደረጀ ትዕዛዙ
በዘመናችን ግለታሪኮችና ታሪኮች በብዛት ባይሆንም በተሻለ መጠን ለህትመት እየበቁ ናቸው፣ ይህ መልካም ጅምር መጠናከር ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም ዓለማችንን የቀየሩዋት ባለ ልዩ አዕምሮ ግለሰቦች ናቸው፤ በእነሱ ጥረትና የድካም ፍሬ ድምሩ ህዝብ ተጠቃሚ ሆኗል፤ ይሆናልም፡፡ እንኳንስ ተፈጥሮ አድልታ ባለ ምጡቅ አዕምሮ ያደረገቻቸው ግለሰቦች ይቅሩና የኔቢጤው በረንዳ አዳሪ ሁሉ ቀርቦ የሚያነበው ቢያገኝ ታላቅ መጽሐፍ ነው፤ ታላቅ መረጃ በውስጡ ይኖራል፡፡
ከነገስታትና ልኡላን ዜና መዋዕሎች በቀር እብዛም ያልተለመደ የነበረው የግለሰቦች ታሪክ በቤተሰቦቻቸው፣ ወይም መልካም ፈቃዱና ችሎታው ባላቸው ግለሰቦች አማካይነት እየተጻፈ ልምዳቸውን እንድንካፈል የላቀ ድርሻ እየተወጡ ናቸው፡፡ በቅርቡ ታትሞ ገበያ ላይ የዋለውና በጳውሎስ ኞኞ የህይወትና ሥራ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው መጽሐፍም ከእነዚህ የግለሰብ ታሪኮች የሚመደብ ነው፡፡
በዘጠኝ ምዕራፎች የተከፋፈለው የ“ጳውሎስ ኞኞ” መጽሐፍ፤ የተለያዩ ፎቶግራፎችንና ውሱን ሰነዶችንም አካትቷል፡፡ ስለጳውሎስ ልደት፣ ዕድገት፣ ትምህርት፣ ሥራና ባህርይ የሚያትተው ይህ መፅሀፍ፤ ከጳውሎስ ጋር ባላንጣ ስለነበሩት የወቅቱ የማስታወቂያ ሚኒስትር ደጃዝማች ግርማቸው ተክለሐዋርያትም የሚያካፍለን ቁም ነገር አለ፡፡
ጳውሎስ ያልሞከረው ሥራ የለም ማለት ይቻላል፤ ግለሰብ ሱቅ ውስጥ ተቀጥሮ መስራት የጀመረው ገና በልጅነት ዕድሜው ሲሆን ትምህርቱን ከአራተኛ ክፍል ያቋረጠውም በድህነት ምክንያት ነው፡፡ (ገፅ 16) ከግሪካዊው ኞኞ እና ከኢትዮጵያዊቷ ወ/ሮ ትበልጫለሽ ቁልቢ ገብርኤል አካባቢ የተወለደው ጳውሎስ፤ የልጅነት ህይወቱ የተመሰቃቀለ ነበር፡፡ እናቱ ፍጹም ድሃ በመሆናቸው እንደ እመጫት ድመት በየቦታው ይዘውት ስለሚዞሩ በትምህርቱ ላይ ጫና መፈጠሩ የግድ ነበር፡፡
እናቱ ወ/ሮ ትበልጫለሽ ከሸዋ ወደ ሐረርጌ የሄዱ ምስኪን በመሆናቸው የረባ ዘመድ አልነበራቸውም፤ እንኳን የእናቱ ዘመዶች ግሪካዊ ነጋዴ አባቱ እንኳ ልጁን ዞር ብሎ የማየት ዕድሉ አልነበረውም፡፡ ስለዚህ ጳውሎስ ድህነትን ገና በጨቅላ ዕድሜው ነው መልመድ የጀመረው። ድሃ ነበር፤ መናጢ ድሃ፡፡ ትምህርቱን ከአራተኛ ክፍል አቋርጦ እናቱን ለመደጎም፣ ራሱንም ለመርዳት ከአንድ ግለሰብ ሱቅ ተቀጠረ፡፡
ተቀጥሮ መስራት አላዋጣው ሲል ፓስቲ እያዞረ መሸጥ ጀመረ፡፡ ከሌሎች የተለየ ለመሆንም እንቁላል ይቀቅልና በተለያዩ ቀለማት አሸብርቆ፣ በባቡርና በመንገድ በመዞር እየሸጠ የተሻለ  ገቢ ማግኘት ቻለ፡፡ ከሁሉም የሚገርመው ግን አንበጣ እየሰበሰበ ለውጭ ዜጎች በመሸጥ ገቢ ማግኘቱ ነው፡፡ ጋዜጣ እያዞረ ይሸጣል፡፡ የተባይ ማባረሪያ ጭራ በመሸጥም እናቱን ይደጉም ነበር፡፡ ሎሚ እየጨመቀና በቀለም እየበጠበጠ ስኳር በመጨመር “ሸርፔቴ” በሚል ስያሜ ይሸጥ እንደነበር ታሪኩ ያወሳል፡፡
ጳውሎስ ሰዓሊም ነበር፤ የመላእክት፣ የጻድቃንና የሰማዕታትን ስዕሎች እየሳለ በየቡና ቤቱ በማዞር በሁለት ብር ሲሸጥ፤ የተለያዩ አርበኞችን ምስል በመሳልም ደህና ገቢ ያገኝ ነበር፡፡ ጳውሎስ ገና በልጅነት ዕድሜው ድህነት ቢፈትነውም እጁን አልሰጠም፤ አንዱን ሥራ ይሞክርና ተቀናቃኝ ሲበዛበት ሌላ ነገር ይፈጥራል፤  ያ ሲለመድበትም ወደ ሌላው ይዞራል፡፡ ሆኖም ሥዕሉን ወይም ዕንቁላሉን ወይም ፓስቲውንም ሆነ አንበጣውን ሲያዞር የጋዜጣ ብጣሽ ካገኘ በተአምር ጥሏት አያልፍም፤ ሱቅ ታዝዞ ሄዶ የገዛትን ቡናም ሆነች ስኳር ለእናቱ ካደረሰ በኋላ ዕቃዋ የተጠቀለለችበትን የጋዜጣ ብጣሽ ወይም ወረቀት ያነሳና ያነብባል፡፡ በንባብ የተለከፈው ገና በልጅነቱ ነው፡፡
የእንቁላሉን፣ የፓስቲውን፣ የአንበጣውን፣ የጭራውን፣ የሎሚ ጭማቂውን “ሸርፔቴ” ንግድ፣ ወይም የስዕሉን ንግድ እያፈራራቀ ሲያስሄድ ከቆየ በኋላ፣ በእርሻ ሚኒስቴር ውስጥ የእንስሳት መርፌ ወጊ ሆኖ በስምንት ብር የወር ደሞዝ ተቀጠረ፡፡ ለሶስት ዓመታትም በጨርጨር አውራጃ እንስሳትን መርፌ እየወጋ ሲያገለግል ቆየ፡፡ በእንስሳት ላይ ተግባራዊ ያደረገውን መርፌ የመውጋት ልምድ በመጠቀም “ደደር” ከተባለ ቦታ በአርባ ብር ደሞዝ ተቀጥሮ ሰዎችን መርፌ ለመውጋት ከሚሲዮኖች ጋር ይሰራ ጀመር፡፡
በ1964 ዓ.ም ደግሞ ዳግማዊ ምኒሊክ ሆስፒታል አውጥቶት የነበረውን የድሬሰርነት ውድድር አልፎ ወደ አዲስ አበባ መጣ፡፡ ደሞዙም ሰማንያ ብር ገባለትና ተደሰተ፡፡ በሂሳብና በጽሑፍ ሙያ ጭምር ሆስፒታሉን በማገልገልም ተወዳጅ ሆነ፡፡ ጋዜጠኝነትን በእውኑም ሆነ በህልሙ አስቦት አያውቅም፤ ግን አንድ አጋጣሚ ድንገት ገፈተረውና የዕድሜ ልክ ቁራኛ አደረገው፡፡
ጋዜጠኛ ለመሆን የበቃበት ምክንያት አስገራሚ ነው፤ ዳግማዊ ምኒሊክ ሆስፒታል እያለ እሱና ጓደኞቹ በብድር ልብስ ይሰፋላቸዋል፡፡ የወሰዱትን ብድር በስድስት ወር ክፈሉ ሲባሉ ወሽመጣቸው ተበጠሰ፤ ከዚያ “ሳንፈልግ አበድረውን ገንዘባችንን በሉን በቃሪያ ነው የምንዘልቀው” የሚል ይዘት ያለው ጽሑፍ “ለማን አቤት ይባላል?” በሚል ርዕስ ጻፈና ለኤርትራ ድምፅ ጋዜጣ ላከው፡፡ ጋዜጣውም ጽሑፉን ጥር 4 ቀን 1948 ዓ.ም ይዞት ወጣ፤ ጳውሎስ ደስ አለው፡፡
በዚህ ሁኔታ ላይ እያለ እዚያው ምኒሊክ ሆስፒታል ውስጥ ከምትሰራና “ፈለቀች” ከምትባል ቆንጆ ጋር በፍቅር ይወድቃል፡፡ ፍቅሩን የሚገልፅለት ግጥም ጽፎ ለጋዜጣ ላከው፤ እሱም እንዳለ ወጣለትና ፈነደቀ፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ጽሑፍ አዘነበለ፤ ትክክለኛ መክሊቱንም አገኘ፡፡
ጳውሎስ የጋዜጠኝነት ስራውን “ሀ” ብሎ የጀመረው በድምፅ ጋዜጣ ነው፡፡ ለዚያ ያበቁት ደግሞ በወቅቱ የማስታወቂያ ሚኒስትር የነበሩት አቶ መኮንን ኃብተወልድ ናቸው፡፡ ጋዜጣዋን በህዝብ ዘንድ ተወዳጅ በማድረጉም ከንጉሠ ነገሥቱ የጽህፈት መኪና (ታይፕራይተር) ተሸልሟል፡፡ ይህ ሽልማት ግን መኮንን ኃብተወልድን በተኳቸው የማስታወቂያ ሚኒስትሩ ዘንድ አልተወደደለትም፡፡
አዲሱ ሚኒስትር ደጃዝማች ግርማቸው ተክለሐዋርያት ሲሆኑ ጠባቸው እስከ መጨረሻ ዘልቋል፡፡ የጳውሎሷ “ድምፅ” ጋዜጣ በህዝብ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የመሆኗን ያህል በመንግስታዊው “አዲስ ዘመን” ጋዜጣ ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደር ጀመረች፡፡ ጳውሎስ ጋዜጣ አዟሪዎችን ሳይቀር የደንብ ልብስ አዘጋጅቶ በማሰራት ጋዜጣዋን ታዋቂ አደረጋት፡፡
ሆኖም የደንብ ልብስ እየለበሱ “ድምፅ” ጋዜጣን የሚያዞሩ ሁሉ እየተለቀሙ እስር ቤት እንዲታጎሩ ደጃዝማች ግርማቸው ለፖሊስ ትዕዛዝ በመስጠታቸው፣ ጳውሎስ በጣም ተበሳጨ፤ የኋላ ኋላ እሱም አልቀረለት፡፡ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋለና በስንት መከራ በዋስ ተለቀቀ።
ፍቅሩ ኪዳኔ፣ መሥፍን ወልደማርያም፣ መርቆሬዎስ፣ አጥናፍሰገድ ይልማ፣ አሳምነው ገብረወልድ፣ ከፍያለው ማሞ፣ ተፈራ ወልድአገኘሁ፣ ነጋ ወልደሥላሴ፣ ሰለሞን ተሰማ፣ ትዕዛዙ ሳህሉ፣ ፍቅረሥላሴ ወልደሐና፣ ማሞ ውድነህና ሌሎችም ዕውቅ ጋዜጠኞችና ጸሐፍት በ“ድምፅ” ጋዜጣ ላይ ይሳተፉ ነበር፡፡
ጳውሎስ ከ “ድምፅ” ጋዜጣ ወደያኔው “የወሬ ምንጭ” አሁን “ዜና አገልግሎት”፣ አዲስ ዘመን ጋዜጣ፣ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን፣ በመጨረሻም ኢትዮጵያ ሬዲዮ ተዘዋውሮ አገሩን አገልግሏል፡፡ ዝነኛ የነበረው ግን መጀመሪያ በ“ድምፅ” ጋዜጣ በኋላም በ “አዲስ ዘመን” ጋዜጣ ላይ ይጽፋቸው በነበሩ ጽሑፎቹ ነው፡፡ ጳውሎስ ያለመታከት ይጽፋል፤ ያለአንዳች ፍርሃት ይተቻል፤ እውነትን የህይወቱ መርህ ያደርጋል፡፡ በዚህ የተነሳ በርካታ ምስጋና፣ ጥቂት የማይባልም ወቀሳና ዘለፋ፣ ግፋ ሲልም ክስና በየፖሊስ ጣቢያው መጎተት ይደርስበት ነበር፡፡
“የተማርሁት ከነቃፊዎቼ ትችት ነው” የሚለው ጳውሎስ፤ ራሱን በራሱ በማስተማር፣ በንባብ ራሱን የተዋጣለት ጋዜጠኛ አድርጎ የፈጠረ ሰው ነው፡፡ ካላነበበ ያመዋል፤ ካልፃፈ እንደ ባለ ዛር ያቅበጠብጠዋል፡፡ ጠባዩ ሁሉ ይቀያየራል፡፡
“አንድ ጥያቄ አለኝ” በሚል ርዕስ ሥር ለሚመጡለት እጅግ በርካታ ጥያቄዎች በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ ተገቢውን መልስ በመስጠት ዝናን ያተረፈው ጳውሎስ፤ ጋዜጠኛ ብቻ ሳይሆን የታሪክ፣ የልብወለድ እና የግጥም ጸሐፊም ነበር፡፡ ከአራተኛ ክፍል ትምህርቱን አቋርጦ ይህን ሁሉ እውቀት ያገኘው ከንባብ ነው፡፡
በትዳር በኩል ጳውሎስ ብዙ ፈተናዎችን አይቷል፤ አራት ሴቶችን በተራ አፍቅሮ አልተሳካለትም፡፡ “ማሚቴ፣ እታፈራሁ፣ ፈለቀች፣ የሹምነሽ” የተባሉ ቆነጃጅትን በየተራ አፍቅሮ ከትዳር ወግ ሳይደርስ ቆይቶ ነበር፡፡ ከጊዜ በኋላ ግን የቤቱ አከራይ ልጅ ከነበረችና “አዳነች” ከምትባል ቆንጆ ጋር የሰመረ ትዳር መሥርቶ እስከ መጨረሻው መዝለቅ ችሏል፡፡ አዳነችን የወደዳት አባቷ ሞተው ደረቷን ገልጣ ስታለቅስ አይቶ ነው፡፡
በደረቷ ፍቅር ወደቀ፤ አገባት፣ እስከ መጨረሻውም አብረው ዘለቁ። ጳውሎስ በሐይማኖት ረገድ በአባልነት የተሰለፈበት ቡድን አልነበረም፣ የእግዚአብሔርን ስም የሚጠራ ሁሉ ትክክል ነው ብሎ ስለሚያምን፣ ኦርቶዶክስም፣ ፕሮቴስታንትም፣ ካቶሊክም፣ ሙስሊምም፣ ባህላዊ ሃይማተኛም ሆኖ ህይወቱን ገፍቷል፡፡ ህዝብ የሚያምነው ሁሉ ትክክል ነው የሚል አቋም የነበረው ይመስላል፡፡
በማህበራዊ ህይወቱ ታላላቅ ተግባራትን በማከናወን የሚታወቀው ጳውሎስ፤ የጋዜጠኞችን ማህበር አይወደውም ነበር፤ እንዲያውም “ማኅበሩ ለአረቄ የተቋቋመ ነው፤ ሙያችንን የማያዳብር፣ የጋዜጠኞች ሙያ ምን እንደሆነ የማያውቅ… እንዲህ አይነት ደደብ ማኅበር እኔም ትቸዋለሁ” ብሎ እስከመናገር የደረሰበት አጋጣሚ አለ (ገፅ 2004)፡፡
ለእንስሳት ልዩ ፍቅር የነበረው ጳውሎስ፤ በህዝብ እንደተወደደና እንደ ተከበረ የዘለቀ ምርጥ ጋዜጠኛ መሆኑን ጓደኞቹና የሥራ ባልደረቦቹ ሁሉ የመሰከሩለት ዕውነት ቢሆንም ቁጣው አፍንጫው ስር ነበር፤ ግን ወዲያው ይረሳል፤ ቂም አያውቅም፡፡
በአጭሩ ጳውሎስ ይህን ይመስላል፣ እንደ ደረጀ ትዕዛዙ መጽሀፍ፡፡ መጽሐፉ በዚህ ደረጃ መገኘቱ ጥሩ ነው፡፡ ሆኖም የጳውሎስ ሥራ፣ ማህበራዊ ህይወትና ቤተሰባዊ መዋቅር ይህ ብቻ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡
ደረጀ የጳውሎስን መጽሐፍ “ግለታሪክ” ነው ሲልም ደጋግሞ ጽፏል፡፡ ይህ ስህተት ነው፤ መጽሀፉ የጳውሎስን ታሪክ የሚያሳይ (biography) እንጂ የደረጀ ግለታሪክ (autobiography) አይደለም፡፡
ደረጀ ስለራሱ የህይወት ታሪክ ቢጽፍ ነበር “ግለታሪክ” የሚሆነው፡፡ አለዚያም ልክ እንደ ፊት አውራሪ ተክለሐዋርያት ተክለማርያም ወይም እንደ ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ ወይም እንደ ተመስገን ገብሬ፣ ጳውሎስም የራሱን ታሪክ ጽፎ ቢሆን ኖሮ “ግለታሪክ” ሊባል ይችል ነበር፡፡ ግለታሪክ ማለት የራስን ታሪክ በራስ መጻፍ ማለት ነው፡፡
መጽሐፉ የመዋቅር ችግርም አለበት፤ ለምሳሌ ጡረታ መውጣቱን ሲነግረን ይቆይና ስለትዳሩ ሊተርክልን ሞክሯል፤ በደጃዝማች ግርማቸውና በእርሱ መካከል ስለነበረው ዘላቂ ፍትጊያም ወዲያና ወዲህ እየተወራጨ ነው የሚነግረን፡፡ በቋንቋ ረገድ እንከን የለሽ ነው ባይባልም ሊነበብ የሚችል መጽሐፍ ነው፡፡ አልፎ አልፎም ቢሆን የፊደል ግድፈት ስላለበት ድጋሚ በሚታተምበት ጊዜ ግድፈቶቹ ሊታረሙ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡
ከሁሉም በላይ ግን የጳውሎስ ህይወት እንቆቅልሽ  ነው የሚባለው የቤተሰቡ ሁኔታ ነው፤ አባቱ ኞኞ መርከበኛ እንደነበር ተወስቷል፡፡ ግን ቁልቢ ድረስ የሄደበት ምክንያት፣ ለምን ሳይመለስና ልጁን ሳይጠይቅ እንደቀረ፣ “ሐዋርያው” የሚባለውና በስሙ የሚጠራው ወጣት “ልጁ አይደለም” የሚሉ ወገኖችም ስላሉ፣ ጥርት ብሎ ቢገለጥ መልካም ነበር የሚል እምነት አለኝ፡፡ በተረፈ የጳውሎስ መልእክት “ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ሆይ! እንዲሁም መላው የሃገሬ ህዝብ! እባካችሁ አንብቡ!!” የሚል ነው፡፡  ጳውሎስን ዳግም የፈጠረው ንባብ ነውና!

Read 3854 times