Tuesday, 29 July 2014 15:07

ከአባት አርበኛ ጋር አዝናኝ ቃለምልልስ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የ95 ዓመት አባት አርበኛ ናቸው፡፡ ያልዘመቱበት የጦር አውድማ የለም። በዚህ ዕድሜያቸው ከ70 ዓመት በፊት የተደረጉ ጦርነቶችን ከእነ ዓመተምህረታቸው ያስታውሳሉ፡፡
ባለፈው ሳምንት በኢኮኖሚና ንግድ አምድ ላይ ቃለምልልስ የተደረገላቸው “የባላገሩ አስጐብኚ ድርጅት” ባለቤት፣ አባት አርበኞችን ወደ ታላቁ ህዳሴ ግድብ ወስዶ የማስጐብኘት ሃሳብ የመጣላቸው በእኚህ አዛውንት ጥያቄ መሆኑን ገልፀውልናል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛዋ ናፍቆት ዮሴፍ ከእኚህ የዕድሜ ባለፀጋ አባት ጋር ማራኪና አዝናኝ ቃለምልልስ አድርጋለች። እነሆ:-



ስምዎትን ያስተዋውቁኝ አባት…
ሃምሳ አለቃ ደምሴ ፀጋዬ እባላለሁ፡፡ ትውልድና እድገቴ ወሎና ጎንደር ነው፡፡ በአንድ ጎን ደባት ገብርኤል ነኝ፡፡ በሌላ ጎኔ ደግሞ ወሎ ውስጥ የጁ እና ላስታ ነው እድገቴ፡፡ ጠቅለል ስታደርጊው ዘር ሃረጌ ከወሎ እና ከጎንደር ይመዘዛል ማለት ነው፡፡
እስቲ ስለልጅነት ያጫውቱኝ?
እንዴ! የአስተዳደጌ ሁኔታማ ምን ይወራል። የተወለድኩት በ1911 ዓ.ም ታህሳስ 3 ቀን ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምረሽ እድሜዬን ማስላት ትችያለሽ፡፡ ጠላታችን ጣሊያን መጥቶ አባቶቻችን ሲዘምቱ የ18 ዓመት አፍላ ጎረምሳ ነበርኩኝ፤ በ1928 ዓ.ም ማለት ነው፡፡ አባቴ በውጊያው ቆስሎ ነበር ከዘመቻው የተመለሰው፡፡
የት ቦታ አባትዎ እንደቆሰሉ አልነገሩዎትም?
ነግሮኛል! ማይጨው ላይ ነው የተመታው፡፡ የዘመተው ከደጃዝማች አድማሱ ብሩ ጋር መሆኑንም አጫውቶኛል፡፡ ደጃዝማቹ እዚያው በውጊያው ሲሞቱ፣ አባቴ ግን ቆስሎ መጣ፡፡ የማስታውሰው እኔ የ19 ዓመት ወጣት ስለነበርኩ፣ አባቴ ውጊያ ሲሄድ የእርሻውን ስራ እኔ እሸፍን ነበር፡፡ አባቴ ከውጊያ የመጣ ቀንም ሞፈርና ቀንበሬን አነባብሬ እርሻ ወርጄ ማሽላ ስዘራ ነበር የዋልኩት፡፡ እነሱ ሲመጡ ጥይቱ እንደ ማሽላ ቆሎ… ጣ  ጣ   ጣ  ጣ ይላል፡፡ ምንድን ነው ነገሩ ብዬ ስጠይቅ፤ “አባትሽ መጣ” አሉኝ፤ አንቺ ነበር የሚሉኝ፡፡
ለምንድነው አንቺ የሚልዎት?
ምክንያቱ በግልፅ አይገባኝም፡፡ ስገምት ግን ስራመድ ከእግሬ እንደ ሴት ፈጠን እላለሁ፡፡ ለዚያ ይመስለኛል፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ ማሽላውን ዘርቼ ጨርሼ፣ ሞፈርና ቀንበሩን እዚያው ትቼ፣ መዋጆውን ይዤ በሬዎቼን እየነዳሁ ነበር፤ ወደ ቤት ለመግባት፡፡ በኋላ አባትሽ መጣ ሲሉኝ፣ መዋጆውንም በሬውንም ትቼ በሩጫ ወደ ቤት መጣሁ፤ ስደርስ አባቴን አገኘሁት፡፡
በጣም ተጎድተው ነበር?
በጣም እንጂ! ሚያዚያ ወር ላይ ነበር የመጣው፡፡ ከዚያ ግንቦት፣ ሰኔ፣ ሐምሌ እና ነሐሴን አስታመምነው፡፡ ከተሻለው በኋላ አሁንም የጠላት ጦር እያየለ ሲመጣ፣ “አገሬ ተወርራ አልቀመጥም” ብሎ ታላቅ ወንድሙን፣ የመጀመሪያ ልጁን (ታላቄን)፣ እኔን አስከትሎ ከአንድ ቤት አራት ሆነን ዘመትን!! ታች ጋይንት አርብ ገበያ ላይ በተደረገው ጦርነት ህዝብ አለቀ፡፡ ከላይ በአውሮፕላን እንደበደባለን፣ በመሬት ይህ ነው ብዬ በቁጥር የማልጠቅሰው እስከ አፍንጫው የታጠቀ የጣሊያን ወታደር አለ፡፡ ምን አለፋሽ… ምድር ቃጤ ሆነች፡፡ እኔ ነጭ ቃታ ቤልጂግ ይዣለሁ፣ አባቴ ረጅም ለበን የሚባል መሳሪያ ይዟል። አባቴ ጥይት ሲያልቅበት አፈሙዙን ድንጋጥ ሰብሮ መሃል ገባ፡፡ ይህን ነጫጭባ ሁላ አንጀት አንጀቱን ዘክዝኮ ዘክዝኮ ከጣለ በኋላ፣ እሱም ወንድሙም፣ የመጀመሪያ ልጁም እዚያው አለቁ (ሲያወሩኝ ስሜታቸው እየጋለ ነው)
እርስዎም በምን ተዓምር ተረፉ ታዲያ?
እኔ አብሬ መሞት ፈልጌ ነበር፡፡ ሰዎች “አንተ እንኳን ትረፍ” በሚል ወደ ኋላ ጎተቱኝና ከእነሱ ጋር አፈገፈግን፡፡ ከዚያ ተርፌ አምስቱን አመት ጣሊያን ከአገራችን እስኪወጣ ተዋግቼ ይኸው እዚህ ደረስኩኝ፡፡
ኮሪያ ዘምተዋል እንዴ?
እንዴታ! ኮሪያና የኤርትራ ዘመቻ አንድ ቀን ነው የዘመትነው፡፡ በወቅቱ ኤርትራ በፌዴሬሽን ነበር የምትተዳደረው፡፡
ራስ ገዝ ነበረች አይደል?
አዎ! ከዚያ በኋላ ከእኛ ጋር ተቀላቀለች፡፡ ይህ እንግዲህ በ1973 ነው፡፡ ከዚያ በኋላ “ወርቋ ኤርትራ ከእናቷ ኢትዮጵያ ጋር በሰላም ተቀላቀለች” ተባለ። ወታደሮቹና ኤርትራዊያኑ አምስት ቀን ሙሉ አብረውን ሲበሉና ሲጠጡ ቆይተው ጃንሆይ ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ፣ እኛ ወደ ምፅዋ ልንወርድ ስንል መንገድ ላይ ጠብቀው አይጠምዱንም መሰለሽ! አስቢው… ሁለት ሻምበል ጦር ወደፊት ሄዷል፡፡ የመሳሪያ ግምጃ ቤቱንና ጠቅላይ ሰፈሩን ሰዎች ከሁለት ቆርጠው ተኩስ ከፈቱብን፡፡
ከኢትዮጵያ ጋር ተቀላቀለች ከተባለ በኋላ ነው?
ታዲያስ! አብረውን በልተው ጠጥተው… የሻዕቢያ ነገር ተመልከቺ! ከዚያ እኔም በሁለት ጥይት ተመትቼ ወደቅኩኝ፡፡
ተጐድተው ነበር?
ታፋዬን ነው የተመታሁት፡፡ ከዚያ በኋላ የሆነውን የተደረገውን አላውቅም፤ ራሴን ስቼ ነበር፡፡ በኋላ ስነቃ አብረውኝ የነበሩት በመትረየስ ጭንቅላታቸውን ተመትተው እኔ ላይ ወድቀዋል። ሬሳ ሲነሳ እኔ ከእነ ነፍሴ ተገኘሁ፡፡ የሚያውቁኝ ሰዎች “አሞራዋ በነፍስ አለች” ብለው እኔን ጨምሮ ሰባት ቁስለኛ በሄሊኮፕተር ተጭነን፣ አዲስ አበባ ምኒልክ ሆስፒታል ገባን፡፡ ሁለቱ ጓዶቻችን ሆስፒታል እንደደረሱ ሞቱ፡፡ አምስታችን ተረፍን፡፡
ሆስፒታል ምን ያህል ጊዜ ለህክምና ቆያችሁ?
አንድ አመት ከዘጠኝ ወር ያህል ሆስፒታል ቆይተናል፡፡ ከዚያ በየቦታው አንድ አንድ ጋሻ መሬት ተሰጠን፡፡ ለእኔ ጉራጌ ዞን ጨወና ወረዳ፣ አመያ የተባለ ቦታ ደረሰኝ፡፡ ያንን መሬት ስቃበጥበት ኖርኩኝ፡፡
የትዳር ህይወትዎ ምን ይመስላል? ልጆችስ ወልደዋል?
ልጆች ወልደዋል ወይ ነው ያልሽው? ያውም በቁና ሙሉ ነዋ! ትዳር ይዤ መውለድ የጀመርኩት በ1937 ዓ.ም ነው፡፡ 19 ልጆች ወልጃለሁ፡፡
ሁሉም በህይወት አሉ?
19 ልጆች ወልጄ አሳድጌ ነበር፡፡ አምስቱ ሞቱብኝ፡፡ አሁን 14 ልጆች፣ 18 የልጅ ልጆች፣ ብዙ የልጅ ልጅ ልጆች አሉኝ፡፡ ከቅድመ አያትም እስከ ምንጅላትነት ደርሻለሁ፡፡
እንደ እርስዎ አርበኛ የሆነ የሆነ ልጅ አለዎት?
አይይይ…….የለኝም፡፡ ወደፊት አርበኛ ይሆኑ እንደሆነ እንጂ እስካሁን የለኝም፡፡
ሶማሊያ ኢትዮጵያን ስትወርር ዘምተዋል?
እንዴ ምን ነካሽ… በደንብ እንጂ! በኦጋዴን ዘጠነኛ ማካናይዝድ ጦር ውስጥ ነበርኩኝ፡፡ ይህ ሁሉ አልፎ መጨረሻ አካባቢ ጡረታ ልወጣ ስል አዲስ አበባ መጣሁ፡፡ በመከላከያ ሚኒስቴር በደሞዝና መዝገብ ቤት ተቀጥሬ ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ በሂሳብ አስተዳደርና በመዝገብ አያያዝ ባለሙያ ሆኜ ነው የሰራሁት፡፡
ተምረዋል ማለት ነው?
እስከ ስድስተኛ ክፍል ተምሬ ሚኒስትሪ ወስጃለሁ፡፡ በየነ መርዕድ ት/ቤት ነው የተማርኩት። እዚሁ አዲስ አበባ ውስጥ ከዚያ በኋላ በርካታ መስሪያ ቤቶች ሰርቻለሁ… ይገርምሻል!
አሁን በጥንታዊት ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ውስጥ ተሳትፎም ምንድነው?
በፊት በሌላ ኮሚቴ ውስጥ እሰራ ነበር፡፡ አሁን የመቃብር ኮሚቴ ነኝ፡፡
በጡረታ ደሞዝ ነው የሚተዳደሩት?
ጡረታም አለኝ ግን ብዙ ልጆቼ ከውጭ በየአቅጣጫው ብር ይልካሉ፤ የብር ችግር የለብኝም። ከባለቤቴ ጋር ዘና ብዬ ተደስቼ ነው የምኖረው፡፡
እድሜዎ 95 ዓመት እንደሆነ ነግረውኛል፡፡ ግን ሙሉ ጥርስ፣ ሙሉ ጤና አለዎት፡፡ አመጋገብዎ እንዴት ነው?
የተገኘውን እበላለሁ፤ መጠጥ ድሮም አሁንም በአፌ አይዞርም፤ ውሃ ብቻ ነው የምጠጣው፡፡ ጥሬ ስጋ ድሮ እበላ ነበር፤ አሁን ለጤና ጥሩ አይደለም ስለሚባል ትቻለሁ፡፡
የታላቁን የህዳሴ ግድብ ለመጎብኘት ከፍተኛ ጉጉት እንዳለዎት ሰምቻለሁ…?
ወይ ልጄ ሁሉም በየጊዜው በየትውልዱ ታሪክ ይሰራል፡፡ በእኛ ትውልድ ያለ በቂ መሳሪያ በጦርና በጎራዴ ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀውን ጣሊያንን አሳፍረናል፡፡ አክሱምን፣ ላሊበላን፣ ጎንደርን ገንብተው ያለፉ ትውልዶች አሉ፡፡ ይሄ ትውልድ ደግሞ ለም አፈር አዝሎ ሲጓዝ፣ ሌላ አገር ሲያለማ የነበረውን አባይን ሲገድብ እድሜ ሰጥቶኝ ከደረስኩ እንዴት አልጓጓ? ግድቡን ጠዋት ጎብኝቼ ማታ ብሞት ደስታውን አልችለውም፡፡
ከዚህ በኋላ ስንት ዓመት መኖር ይፈልጋሉ?
እየውልሽማ… እግዚያብሔር ለአብርሃም 500 ዓመት ሲሰጠው፣ ለዚህች አጭር እድሜ ብዬ ቤት አልሰራም ብሎ በድንኳን ኖረ፡፡ እኔ አሁን ወደ 95 ዓመት እየሄድኩ ነው፡፡ ለእኔስ 150 ዓመት ቢሰጠኝ ምን ይለዋል? (ረጅም …..ሳቅ)

Read 4465 times