Saturday, 05 July 2014 00:00

ኢትዮጵያውያን ባሎች ሚስቶቻቸውን በመደብደብ ከአፍሪካ 3ኛ ናቸው

Written by 
Rate this item
(3 votes)

87 በመቶ የማሊ ሴቶች ድብደባ ተገቢ ነው ይላሉ
የጊኒና የኢትዮጵያ ሴቶችም ድብደባ ተገቢ ነው ብለው ያስባሉ


የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የተለያዩ ተቋማት በቤት ውስጥ ጥቃት ዙሪያ ያወጧቸውን ሪፖርቶች መነሻ በማድረግ በቅርቡ በ37 የአፍሪካ አገራት ላይ የተሰራ አንድ ጥናት፣ ኢትዮጵያውያን ባሎች ሚስቶቻቸውን አዘውትረው በመደብድብ 3ኛ መሆናቸውን አረጋገጠ።
‘አፍሪካ ሄልዝ፣ ሂዩማን ኤንድ ሶሻል ዲቨሎፕመንት ሰርቪስ’ የተባለው አህጉራዊ ድርጅትና በሴቶች ጥቃት ዙሪያ የሚሰሩ ሌሎች ተቋማት በጋራ የሰሩት ጥናት እንደሚለው፣ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን ባሎች የትዳር አጋሮቻቸውን መደብደብ አግባብ ነው ብለው የሚያስቡና በተለያዩ ምክንያቶች ሚስቶቻቸውን የሚደበድቡ ናቸው፡፡
ጥናቱ ከተሰራባቸው የአፍሪካ አገራት የበለጠ ተደባዳቢ ባሎች ያሉባት አገር ናት ተብላ በቀዳሚነት የተቀመጠችው ኡጋንዳን ስትሆን፣ ሴራሊዮን ሁለተኛ፣ ኢትዮጵያ ደግሞ ሶስተኛ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡
60 በመቶ ያህሉ ኡጋንዳውያን ባሎች በትዳር ውስጥ የሚከሰቱ ግጭቶችን ለመፍታት ሚስቶቻቸውን መደብደብ ሁነኛ መላ ነው ብለው እንደሚያስቡ የጠቆመው የጥናቱ ውጤት፣ ለድብደባ ምክንያት ከሚያደርጓቸው ነገሮች መካከልም፤ ‘እዚህ ሄድኩ ሳትይኝ ከቤት ወጥተሸ ሄድሽ’፣ ‘የምልሽን አትሰሚኝም’፣ ‘ከእከሌ ጋር ያለሽ ነገር ምንድን ነው?’፣ ‘ልጆቼን በወጉ አልተንከባከብሽም’ እና ሌሎች ከወሲብና ከቅናት ጋር ተያያዙ ጉዳዮች እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
ጥናቱ በተሰራባቸው አገራት የሚገኙ አብዛኞቹ ባሎች የድብደባን አስፈላጊነት የሚያምኑበት ሲሆን፤ በአንዳንዶቹ አገራት የጥቃቱ ሰለባ የሆኑት ሚስቶችም ተመሳሳይ አመለካከት እንዳላቸው ተጠቁሟል፡፡ መሰል አመለካከት ከሚንጸባረቁባቸው አገራት መካከል ጥናቱ በቀዳሚነት ያስቀመጠው ማሊን ሲሆን፣ ከ15 እስከ 49 የዕድሜ ክልል ውስጥ ከሚገኙ የአገሪቱ ሴቶች 87 በመቶ ያህሉ፣ ባሎች ሰበብ አስባብ እየፈጠሩ ሚስቶቻቸውን መደብደባቸው ተገቢ ነው ብለው እንደሚያስቡ አረጋግጧል፡፡ የማሊን ሴቶች ተከትለው የጊኒና የኢትዮጵያ ሴቶችም ድብደባ ይገባል ብለው ያስባሉ ብሏል ጥናቱ፡፡
የኡጋንዳ መንግስት ቃል አቀባይ ኦፎኖ ኦፖንዶ ለ “ኒውስ ቪዥን” ጋዜጣ በሰነዘሩት አስተያየት፤ የጥናቱ ውጤት ትክክለኛ መሆኑን ገልጸው፣ በአብዛኞቹ የአገሪቱ የገጠር አካባቢዎች የቤት ውስጥ ጥቃት እንደሚፈጸምና ተገቢ ነው ተብሎ እንደሚታመን እማኝነታቸውን ሰጥተዋል፡፡
“አብዛኞቹ ባሎች የቤተሰቡ የገቢ ምንጭ በመሆናቸው በሚስቶቻቸው ላይ የፈለጋቸውን ጥቃት ቢሰነዝሩ ሃይ ባይ የለባቸውም፡፡ አንዳንዴ ደግሞ፣ ባሎች ሌላ ሚስት ወደቤታቸው ለማስገባት ሲሞክሩ ሚስቶች ነገሩን በመቃወም ከቤታቸው ለመውጣት ይሞክሩና በባሎቻቸው ድብደባና ግርፋት ይደርስባቸዋል፡፡” ብለዋል ቃል አቀባዩ፡፡

Read 4863 times