አዴሌ በአልበምና በነጠላ ዜማ የደረጃ ሰንጠረዦች ላይ በነበራት የበላይነት የ2011 አንደኛ አርቲስት ስትሆን፤ ሪሃና፣ ኬቲ ፔሪ፣ ሌዲ ጋጋ እና ሊል ዋይኔ ተከታታይ ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በፖፕ ሙዚቃ ኬቲ ፔሪ፤ በራፕና ሂፕሆፕ ሊል ዋይኔ፤ በአር ኤንድ ቢ እና ሂፕ ሆፕ የ”ዓመቱ ምርጥ ራፐር” የተባለችው ኒኪ ማናጅ፤ በካንትሪ ቴይለር ስዊፍት ቀዳሚነቱን ይዘዋል፡፡ “ዘ ካርተር IV” በተሰኘ አልበሙ በአር ኤንዲቢ እና በሂፕሆፕ ዘርፍ የዓመቱ “ምርጥ አልበም” አሸናፊ የሆነው ሊል ዋይኔ በአሜሪካ የተለያዩ ግዛቶች ባቀረባቸው የሙዚቃ ዝግጅቶች 47 ሚሊዮን ዶላር እንዳገኘ ታውቋል፡፡ ኒኪ ማናጅ ደግሞ ሊል ዋይኔ፣ ድሬክና ካናዬ ዌስትን በማስከተል የቢልቦርድ የዓመቱ አንደኛ ራፐር ሆናለች፡፡ “360 ቱር” በሚል ስያሜ በመላው ዓለም ባቀረቡት የሙዚቃ ኮንሰርቶች 293.3 ሚ. ዶላር ያገኙት “ዩ2” የሙዚቃ ቡድን የአመቱ አንደኛ የኮንሰርት ባንድ ተብለዋል - በቢልቦርድ፡፡ በተመሳሳይ ፎርብስ መፅሄት እንዳመለከተው፤ ከሴት ሙዚቀኞች የዓመቱን ከፍተኛ ገቢ በማግኘት ሌዲ ጋጋ ትመራለች - 90 ሚ. ዶላር በማግኘት፡፡ ቴይለር ስዊፍት በ45 ሚ. ዶላር እንዲሁም ኬቲ ፔሪ በ44 ሚ. ዶላር ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃዎችን አግኝተዋል፡፡ ቢዮንሴ ኖውልስ በ35፤ ሪሃና በ29፤ ፒንክ በ22፤ ኬሪ አንደርውድ በ20፤ ሴሌንዲዮን በ19፤ አዴሌ በ18 እንዲሁም አሊሻ ኪስና ብሪትኒ ስፒርስ በ10 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡