Saturday, 31 May 2014 12:23

በእነ አቶ መላኩ ፈንታ የክስ መዝገቦች ላይ ብይን ተሰጠ

Written by 
Rate this item
(39 votes)

የተከሳሾች መቃወሚያ ውድቅ ሆኗል

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 15ኛ ወ/ችሎት የሙስና ክስ የቀረበባቸውን የቀድሞ ገቢዎችና ጉምሩክ ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታንና በሶስት መዝገቦች የተከሰሱ ሌሎች ተከሳሾችን የክስ መቃወሚያና የአቃቤ ህግን ምላሽ መርምሮ በትናንትናው እለት ብይን ሰጠ፡፡ ፍ/ቤቱ አብዛኛውን የተከሳሾችን መቃወሚያ ውድቅ አድርጓል፡፡
ፍ/ቤቱ ብይኑን ከመስጠቱ በፊት ተከሳሾቹ ያመለከቱትን የክስ መቃወሚያና የአቃቤ ህግን ምላሽ አስታውሷል፡፡
በመዝገቡ 1ኛ ተጠሪ የሆኑት አቶ መላኩ በዚህ መዝገብ በቀረቡባቸው ክሶች፤ የቀረቡብኝ ክሶች በስነ ስርአት ህጉ አንቀፆች መሰረት የተሟሉ አይደሉም፣ ከባለስልጣናት ጋር በመመሳጠር ክስ አንስተሃል ለተባልኩት ኃላፊነት የለብኝም” የሚሉና ሌሎች መቃወሚያዎችን ያስታወሰው ችሎቱ፤ አቶ ገ/ዋህድ በበኩላቸው፤ “በተነሱና በተቋረጡ ክሶች ልጠየቅ አይገባም፤ ክሶችን እንዳነሣ አዋጁም ይፈቅድልኛል፤ ከተፈቀደልኝ ወሰን በላይ ህግ አልጣስኩም” ማለታቸውን ጠቁሟል፡፡
ሌሎች በመዝገቡ የተካተቱ ተከሳሾች “የቀረበው ክስና ማስረጃ ግልፅ አይደለም፣ በተሻረ የህግ አንቀፅ ተከሰናል፣ ኮሚሽኑ በማይመለከተው ስልጣንና በሌለው ውክልና ነው የከሰሰን፣ ክሱ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ነው” የሚሉና ሌሎች በርካታ መቃወሚያዎች እንዳቀረቡም ችሎቱ አስታውሷል፡፡
ለተከሳሾቹ መቃወሚያ ከአቃቤ ህግ ከተሰጡ ምላሾች መካከልም፤ ከማስረጃና ከክስ ጭብጥ ጋር ተያይዞ የቀረቡት መቃወሚያዎች በብይን ሳይሆን በክርክር ሂደት ነው መታየት ያለባቸው የሚለው ይገኝበታል፡፡
እነ አቶ መላኩ በእርግጥም ክስ የማንሳት ስልጣን በአዋጅ እንደተሰጣቸው የጠቀሰው አቃቤ ህግ፤ ነገር ግን ተከሳሾቹ ከተፈቀደላቸው የህግ ወሰን በላይ የተሰጣቸውን መብት ተጠቅመዋል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ሁሉም ተከሳሾች ያቀረቡት የክስ መቃወሚያም ሙሉ ለሙሉ ውድቅ እንዲደረግለት አቃቤ ህግ የጠየቁ ሲሆን፡፡
የግራ ቀኙን መከራከሪያ ሲመረምር መቆየቱን ያስታወሰው ፍ/ቤቱም፤ በዚህ መዝገብ ላይ ክሱ መስፈርቱን አሟልቶ መቅረቡን እንዲሁም ገቢዎችና ጉምሩክ ለፀረ-ሙስና ኮሚሽን ውክልና መስጠት እንደሚችል በመግለፅ በመዝገቡ ከተጠቀሱት 93 ክሶች 90ዎቹ ባሉበት እንዲቀጥሉ ሶስቱ ተሻሽለው እንዲቀርቡ በይኗል፡፡
ፍ/ቤቱ ቀጣይ ሂደቱን ለማየት ሁሉንም መዝገቦች ለሰኔ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

Read 12889 times