Saturday, 31 May 2014 12:21

“ዴልታ” ሼፎችን በውጭ ባለሙያ ሊያሰለጥን ነው

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ከኦስትሪያ የሚመጡት አሰልጣኝ በቀን 28 ሺ ብር ይከፈላቸዋል

ለዳቦና ኬክ ምርቶች ጥሬ እቃዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ዴልታ የማምረቻና የንግድ ኩባንያ፤ የኢትዮጵያ የዳቦና የኬክ ሼፎችን በውጭ ባለሙያ ሊያሰለጥን እንደሆነ ተገለፀ፡፡ ከኦስትሪያ ቪየና የሚመጡት የዳቦና የኬክ ሥራ አሰልጣኝ ሚስተር ገንተር ኮክሲደር፤ በቀን 28 ሺህ ብር እንደሚከፈላቸው ታውቋል፡፡
ስልጠናው የሚሰጠው በክልልና በአዲስ አበባ የሚገኙ ሆቴሎች ለሚልኳቸው የዳቦና የኬክ ሼፎች ሲሆን በሀርመኒ ሆቴል በሚሰጠው ስልጠና ላይ በቀን 30 ሼፎችን በነፃ ለማሰልጠን መዘጋጀታቸውን የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ አደም ሙዲ ገልፀዋል፡፡ ከ10 አይነት በላይ በሆኑ የኬኮችና የዳቦ አይነቶች አሰራር ላይ የሚሰጠው ስልጠና፤ በአገራችን የሚመረተውን የኬክና የዳቦ የጥራት ደረጃ በማሳደግ፣ ከየትኛውም አለም ለሚመጡ ሰዎች የሚመጥን እንዲሆን ያስችላል ተብሏል፡፡
ዴልታ ኩባንያ፤ የኬክና የዳቦ ምርቶችን ጥራት ባለው ደረጃ ለማምረት የሚስችል ፋብሪካ እየገነባ እንደሆነ የጠቆሙት አቶ አደም፤ ፋብሪካው የስልጠና ማዕከል እንደሚያካትትም ገልፀዋል፡፡ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ሥልጠና ለመስጠት ምን እንዳሳሰባቸው የተጠየቁት የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ሥራ አስኪጅ አቶ አደም ሲመልሱ፤ “ከውጭ የምናስገባቸው ለኬክና ለዳቦ ምርት የሚውሉ ጥሬ እቃዎች ጥሩ ሙያተኞች ጋ ካልደረሱ እኛ ዋጋ እናጣለን፤ ለዚህ ነው ባለሙያዎችን ለማሰልጠን የወሰንነው” ብለዋል፡፡ ስልጠናው የተዘጋጀው ጥሬ እቃ ከውጭ ከሚልኩላቸው ድርጅቶች ጋር በመተባበር እንደሆነም ጨምረው ገልፀዋል፡፡

Read 3415 times