Saturday, 24 May 2014 15:25

ቀነኒሣና ጥሩነሽ በጐዳና ላይ ተሳክቶላቸዋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የዓለማችን የረጅም ርቀት ምርጥ አትሌቶች የሆኑት  ቀነኒሣ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በጐዳና ላይ ሩጫዎች ስኬታማ እየሆኑ ናቸው፡፡  ባለፈው ሳምንት  በእንግሊዝ በተካሄደው የቡፓ ግሬት ማንቸስተር ራን በ10 ኪ.ሜ የጐዳና ላይ ሩጫ በሁለቱም ፆታዎች አሸናፊ ሆነዋል፡፡
አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በወንዶች ምድብ ያሸነፈው ርቀቱን በ28.23 ደቂቃዎች በመሸፈን ነበር፡፡ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ ባለቤቱን ኬንያዊው ዊልሰን ኪፕሳንግ በ5 ሰኮንዶች በመቅደም አስከትሎት ገብቷል፡፡ ይህ ውጤት  ሁለቱ አትሌቶች ለመጀመርያ  በማራቶን የሚገናኙበትን ሁኔታ አጓጊነት ጨምሮታል፡፡ ዊልሰን ኪንሳንግ በ2013 አጋማሽ ላይ በበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ  የዓለም ሪከርድን ያስመዘገበ ነው፡፡ ከወር በፊት ቀነኒሳ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ሮጦ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ሲያሸንፍ በዚያው ሰሞን ዊልሰን ኪፕሳንግም በለንደን ማራቶን በተመሳሳይ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ማሸነፉ ይታወሳል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ከዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር በማራቶን መሮጥ ፍላጎት እንዳለውም የሰጠው፡፡ ከቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን በኋላ ቀነኒሳ በሰጠው አስተያየት አሁን ትኩረቱ ወደ ትራክ ውድድሮች መመለስ እንደሆነ ገልፆ፤ በተለይ በ10ሺ ሜትር አንድ ውድድር ማድረግ እንደሚፈልግ አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ርቀቱን በ32 ደቂቃ ከ20 ሰኮንዶች በመሸፈን አሸንፋለች፡፡ ጥሩነሽ  በቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን ዘንድሮ ያሸነፈችው ለሁለተኛ ግዜ  ሲሆን አምና ውድድሩን ስታሸንፍ በ30.49 ደቂቃዎች በሆነ ጊዜ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግባ ነበር ፡፡
ከወር በፊት በፓሪስ እና ለንደን በተካሄዱ የማራቶን ውድድሮች የመጀመርያ ማራቶናቸውን የሮጡት ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ አጀማመራቸው ስኬታማ እነደሆነ ያመለከቱ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ዓመታት በሁለቱም ፆታዎች የተያዙ የዓለም ማራቶን ሪከርዶችን ለመስበር ግንባር ቀደም እጩዎች ስለመሆናቸውም ግምት ሰጥተዋል፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ የሮጠው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የቦታውን ሪከርድ ካሸነፈ በኋላ ያሳየው ብቃት በሚቀጥሉት 5 ዓመታት የዓለም ማራቶን ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል ያመለክታል በሚል በርካታ ዘገባዎች አውስተውለታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ የፓሪስ ማራቶንን ሲያሸንፍ ርቀቱን የሸፈነበት 2 ሰአት ከ05 ደቂቃ ከ4 ሰኮንዶች ነበር፡፡ በረጅም ርቀት 5 የዓለም ሻምፒዮና እንዲሁም 3 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ያሏት ጥሩነሽ ዲባባ ደግሞ ከወር በፊት በለንደን የመጀመርያ ማራቶን ውድድሯን  በሁለት ሰዓት ከ20 ደቂቃ ከ54 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በሶስተኛ ደረጃ ጨርሳለች፡፡ ይሄው የጥሩነሽ ሰዓት በማራቶን የመጀመርያ ሩጫ ከተመዘገቡ ፈጣን ሰዓቶች በሶስተኛ ደረጃ ተመዝግቧል፡፡

Read 1440 times