Saturday, 10 May 2014 11:55

9 ጋዜጠኞችና ፀሐፊዎች ምን ሰርተው እንደታሰሩ እስካሁን አልተገለፀም

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(5 votes)

እስረኞች፤ ድብደባና ግርፋት ደርሶብናል አሉ

         ከአለማቀፍ የመብት ተሟጋች ተቋም ጋር በገንዘብና በሃሳብ ተደራጅተው በኢንተርኔት አገሪቱን ለማሸበር አሲረዋል በሚል የታሰሩት 9 ጋዜጠኞችና የ“ዞን 9” ፀሐፊዎች ላይ ምርመራ እንዳልጨረሰ በመግለጽ ተጨማሪ ጊዜ እንዲፈቀድለት ፖሊስ የጠየቀ ሲሆን፤ ፍ/ቤት የ10 ቀን ቀጠሮ ሰጠ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ተጠርጣሪዎች ሀገሪቱን ለማሸበር በኢንተርኔት ማህበራዊ ሚዲያዎች አሲረዋል ያለው ፖሊስ፤ ሰሞኑን ተጠርጣሪዎቹ ፍ/ቤት ሲቀርቡ፣ የተያዙት በማህበራዊ ድረገፆች ላይ በፃፉት ሳይሆን ከውጭ አሸባሪ ኃይሎች ጋር በመደራጀት፣ አገሪቱን ከቀጣዩ ምርጫ በፊት ለማሸበር እና የሽብር ሴራውንም ለመምራት ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸው ነው ማለቱን የተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ አቶ አመሀ መኮንን ተናግረዋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ መንግስትን ከምርጫው በፊት ለመጣል፣ ከ5 ጊዜ በላይ እንደ ኬንያና ስውዲን ባሉ አገራት ስልጠና መውሰዳቸውን ፖሊስ ለፍ/ቤቱ ማስረዳቱንም ጠበቃው አክለው ገልፀዋል፡፡ በሶስት መዝገብ ተከፋፍለው በአራዳ ፍርድ ቤት አንደኛ ወንጀል ችሎት ጉዳያቸው የሚታየው ጋዜጠኞችና ፀሃፊዎች፤ በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ የ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸው ለባለፈው ረቡዕ እና ሀሙስ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ መቀጠሩ ይታወሳል፡፡ ረቡዕ ዕለት ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ ኤዶም ካሳዬ፣ ናትናኤል ፈለቀና አጥናፍ ብርሃነ ችሎት ቀርበው ጉዳያቸው የታየ ሲሆን በመቀጠል ተስፋዓለም ወ/የስ፣ አስማማው ሃ/ጊዮርጊስ እና ዘላለም ክብረት ችሎት ቀርበዋል፡፡ ጉዳያቸው በዝግ ችሎታ የታየ በመሆኑ ቤተሰብ፣ እንዲሁም የውጭና የአገር ውስጥ ጋዜጠኞች የፍርድ ቤት ሂደቱን መከታተል አልቻሉም፡፡

የተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ አቶ አመሀ መኮንን፤ ከችሎት መጠናቀቅ በኋላ ለጋዜጠኞችና ለተጠርጣሪ ቤተሰቦች በሰጡት ማብራሪያ፤ ተጠርጣሪዎቹ መጀመሪያ ከተጠረጠሩበት ጉዳይ በተለየ በውጭ ከሚገኙ አሸባሪ ሃይሎች ጋር በመደራጀት፣ እንደ ኬኒያና ስዊድን ባሉ አገሮች ከአምስት ጊዜ በላይ ስልጠና በመውሰድና ገንዘብ በመቀበል፣ ከመጪው ዓመት ምርጫ በፊት አገሪቱን ለማሸበርና የሽብር ሴራውን ለመምራትም ጭምር ሲንቀሳቀሱ እንደደረሰባቸው ፖሊስ ለፍ/ቤቱ ማስረዳቱን ገልፀዋል፡፡ ከውጭ አሸባሪ ሀይሎች በተቀበሉት ገንዘብ፣ ላፕቶፕና ኮምፒዩተር እንደገዙም ፖሊስ ለፍ/ቤቱ ማስረዳቱን የተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ ገልፀው፤ “ፖሊስ የተጠርጣሪዎቹን ጉዳይ ከሽብርተኝነት ጋር አያይዞታል” ብለዋል፡፡

ደንበኞቻቸው የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው መጠየቃቸውን ያወሱት ጠበቃው፤ ፖሊስ ስድስት የተለያዩ ምክንያቶችን በመጥቀስ፣ የዋስትና መብታቸው እንዳይከበር መሟገቱን ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ የዋስትና መብታቸው ቢከበር ይጐዳኛል ካለባቸው ምክንያቶች ውስጥ ተጨማሪ ግብረ አበሮች ስላሏቸው ቢለቀቁ እነሱን ያስመልጡብኛል፣ ከውጭ አሸባሪ ሀይሎች ገንዘብ ተቀብለው የገዟቸውን ላፕቶፖችና ኮምፒዩተሮች ገና አልያዝኩም፣ ተጠርጣሪዎቹ የተገኙባቸው ሰነዶች በእንግሊዝኛ የተፃፉ በመሆናቸው አስተረጉማለሁ፣ ተጨማሪ ሰነዶችን ሊያሸሹብኝ ይችላሉ፣ ምስክር ገና አላሰማሁም እና የቴክኒክ ምርመራ አልጨረስኩም በማለት ለፍርድ ቤቱ ማስረዳቱን የተናገሩት አቶ አመሀ፤ የዋስትና መብታቸው አይከበር የሚለው የፖሊስ ጥያቄ በፍ/ቤቱ ተቀባይነት ማግኘቱን ተናግረዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ፤ በቤተሰብና በወዳጅ ዘመድ እንዲጐበኙ ፍ/ቤቱን መጠየቃቸውን የተናገሩት ጠበቃው፤ ከሐሙስ እለት ጀምሮ በወዳጅ ዘመድ እንዲጐበኙ መፈቀዱን ተናግረዋል፡፡ ከትናንት በስቲያ ፍ/ቤት የቀረቡት እነ ማህሌት ፋንታሁን፣ አቤል ዋበላና በፍቃዱ ሀይሉም የተጠረጠሩበት ጉዳይ ረቡዕ እለት ከቀረቡት ከእነ ኤዶም ካሣዬ ጋር ተመሳሳይ መሆኑን አቶ አመሀ መኮንን ገልፀዋል፡፡ በሀሙሱ ችሎት ተጠርጣሪዎቹ በብሎግ፣ በፌስቡክና በቲዊተር ላይ ባሰፈሩት ፅሁፍ ተጠርጥረው አለመያዛቸውን ፖሊስ መግለፁን ጠበቃው ተናግረዋል፡፡

ረቡዕ ዕለት የተጠርጣሪዎቹ ጉዳይ የታየው በዝግ ችሎት ቢሆንም በሀሙሱ ችሎት የሶስቱ ተጠርጣሪ አንድ አንድ የቤተሰብ አባላት ወደ ችሎቱ እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል፡፡ “ችሎቱ በዝግ እንዲሆን ተፈልጐ ሳይሆን ፍርድ ቤቱ የሚይዘው የሰው ብዛት አነስተኛ በመሆኑ ነው” ያሉት አቶ አመሀ፤ ባለችው ጠባብ ቦታ ቅድሚያ ለማን እንስጥ በሚል ስንነጋገር፣ ለቤተሰቦች በመባሉ፣ አንድ አንድ የቤተሰብ አባላት እንዲገቡ ተፈቅዷል፤ ተጨማሪ ማን ይግባላችሁ ተብለው የተጠየቁት ተጠርጣሪዎቹ፤ “ለጊዜው በቂ ነው” በማለት ምላሽ እንደሰጡ ጠበቃው ተናግረዋል፡፡ ከሶስቱ ተጠርጣሪዎች ሁለቱ አቤል ዋበላና በፍቃዱ ሀይሉ በእስር ቤት የሰብአዊ መብት ጥሰት እንደደረሰባቸው ለፍ/ቤቱ መናገራቸውን ያወሱት ጠበቃው፤ በደረሰባቸው ድብደባና ግርፋትም ለጉዳት መዳረጋቸውን ጠቁመው፤ የሚመለከተው አካል የሰብአዊ መብት ጥሰቱን እንዲያስቆምላቸው መጠየቃቸውን ገልፀዋል፡፡

በደንበኞቻቸው ላይ የሚፈፀመው የሰብአዊ መብት ጥሰት እንዲቆም ከፖሊስ ጋር መነጋገራቸውንም ጠበቃው አክለው ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ የጠቀሰው የሰነድ ምርመራና ማስተርጐም እንዲሁም የቴክኒክ ምርመራ ሂደት ደንበኞቻቸውን በእስር የሚያስቆይ ስላልሆነ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር፣ ካልሆነም አጭር የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጥ ፍ/ቤቱን መጠየቃቸውን ያወሱት ጠበቃው፤ እነ ኤዶም፣ ናትናኤል፣ አጥናፍ እንዲሁም ተስፋለም፣ አስማማውና ዘላለም ለግንቦት ዘጠኝ ሲቀጠሩ፤ ማህሌት፣ አቤልና በፍቃዱ ለግንቦት 10 ተቀጥረዋል ብለዋል፡፡ ማህሌት፣ አቤልና በፍቃዱ ከፍርድ ቤት ሲወጡ ፉጨት፣ ጭብጨባና የማበረታቻ ጩኸት ውጭ ከተሰበሰቡ ቤተሰቦችና ወዳጆች የተስተጋባ ሲሆን ጠበቃው ጩኸትና ጭብጨባው ሌሎች ችሎቶችን እየረበሸ ነው በሚል ከፍ/ቤት ማስጠንቀቂያ እንደደረሳቸው ገልፀው፤ “ጩኸትና ጭብጨባው ደንበኞቼን ስለሚጐዳ እንዳይደገም” በማለት ለቤተሰብና ወዳጅ ዘመድ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል፡፡

በሌላ በኩል፤ በረቡዕ ዕለት ችሎት ከሌሎች ጓደኞቹና ተጠርጣሪ ቤተሰቦች ጋር የጓደኞቹን ጉዳይ ውጭ ሆኖ ሲከታተል የነበረው የ“አዲስ ስታንዳርድ” መጽሔት የቀድሞ አምደኛ ኪያ ፀጋዬ፤ ተጠርጣሪዎቹ ከችሎት ሲወጡ ባልታወቀ ምክንያት ፖሊስ እየደበደበና እየተጎተተ ከታሳሪዎቹ ጋር የወሰደው ሲሆን ሃሙስ እለት ማምሻውን መለቀቁን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ከአንድ ቀን እስር በኋላ የተለቀቀው ኪያ ፀጋዬ በምን ጉዳይ እንደተያዘ ጠይቀነው “ወደ ማዕከላዊ የተወሰድኩት ፎቶ አነሳህ ተብዬ ነው” ብሏል፡፡ “ፎቶ ማንሳት በወቅቱ አልተከለከለም፤ ፈረንጆችም ሲያነሱ ነበር፤ ፎቶ ያነሳሁትም ፍ/ቤት ውስጥ ሳይሆን ፍ/ቤት ግቢ ውስጥ ነው” ያለው ኪያ፤ ፎቶ ያነሳሁት አንዳንድ ኮመንተሪዎችን ስፅፍ ፎቶ ለመጠቀምና ለማስታወሻም ጭምር ነው ሲል ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ማእከላዊ ከተወሰደ በኋላ ለምን ፎቶ አነሳህ፣ ፎቶ እንድታነሳ የቀጠረህ አካል ማን ነው፣ ለማን ነው የምትሰራውና መሰል ምርመራዎች እንደተደረጉበት ጠቁሞ ባለሙያ እንደሆነና፣ ፎቶውን ያነሳው ለማስታወሻ መሆኑን ለመርማሪዎቹ ካስረዳ በኋላ በአይፎን ስልኩ ያነሳቸው ፎቶዎች ተሰርዘው፣ በነፃ መለቀቁን ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡

Read 3605 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:04