Print this page
Saturday, 10 May 2014 11:52

ዓረናን የሚደግፉ ባለሃብቶች ዛቻና ማስፈራሪያ ደረሰባቸው ተባለ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(5 votes)

በትግራይ ክልል ዓረናን ትደግፋላችሁ የተባሉ አራት ባለሀብቶች፣ ዛቻና ማስፈራሪያ እንደደረሰባቸው ምንጮች ሲገልፁ ፓርቲው በበኩሉ፤ ዛቻውና ማስፈራሪያው እውነት መሆኑን ጠቁሞ የአረና ደጋፊዎች ግን ሁለቱ ባለሃብቶች ብቻ ናቸው ብሏል፡፡ በመጪው ምርጫ በክልሉ ዋና የህወሐት ተፎካካሪ ሆኖ ለመወዳደር ያቀደው ዓረና፤ በየከተሞቹ ህዝባዊ ስብሰባ በመጥራት ፕሮግራሙን እያስተዋወቀ እንደሚገኝ የፓርቲው ተወካይ አቶ አብርሃ ደስታ የጠቆሙ ሲሆን የክልሉ ባለሥልጣናትና የደህንነት ሃላፊዎች፣ የፓርቲው ደጋፊ ናቸው በተባሉ ባለሃብቶች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ እያደረሱባቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ባለሃብቶቹ በሚደርስባቸው ማስፈራሪያ የተነሳ ለራሳቸውና ለቢዝነሳቸው ሲሉ ድጋፍ ማድረጋቸውን ሊያቋርጡ ይችላሉ የሚል ስጋት እንዳደረባቸውም ተወካዩ ገልፀዋል፡፡ ከክልሉ ባለሥልጣናት ዛቻና ማስፈራሪያ ደርሶባቸዋል የተባሉትን ባለሃብቶች፣በስልክ ብናገኛቸውም “ለደህንነታችን እንሰጋለን” በሚል ምንም ዓይነት አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ ዓረና በሚቀጥለው ሳምንት አርብ፣ በሀውዜን ከተማ የፓርቲውን ፕሮግራም ለማስተዋወቅ፣ ህዝባዊ ስብሰባ የጠራ ሲሆን በቀጣይም በአክሱም ተመሳሳይ ስብሰባ እንደሚጠራ አቶ አብርሃ ገልፀዋል፡፡

Read 2777 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:12