Print this page
Saturday, 10 May 2014 11:49

አየር መንገድና የቱር ኦፕሬተርስ አሶስዬሽን ለቱሪስቶች 40 እና 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ አደረጉ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

         የኢትዮጵያ አየር መንገድና የቱር ኦፕሬተርስ አሶስዬሽን የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ቱሪስቶችን ቁጥር ለመጨመር፣ በትራንስፖርትና በአገልግሎት ክፍያ ዋጋ ላይ ቅናሽ ማድረጋቸውን አስታወቁ፡፡ የሆቴሎች ዋጋም ይቀንሳል ተብሏል፡፡ በቅርቡ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድና አገልግሎት ሰጪ የሆነው የአስጐብኚ ድርጅቶች ማኅበር (ቱር ኦፕሬተርስ አሶስዬሽን) ከትናንት በስቲያ በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ ኢትዮጵያ በርካታ የቱሪስት መዳረሻ ባለቤት ብትሆንም፣ የቱሪስቶች ፍሰት ከቁጥር የማይገባ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በውጭ አገራት ያሉ የተፎካካሪ አገራት የቱሪስት ወኪሎች “ኢትዮጵያን ለመጐብኘት የትራንስፖርትና የሰርቪስ ዋጋ ውድ ነው፣ የአገልግሎት አሰጣጡ (የሆቴሎች ንፅህና፣ መስተንግዶ) ጥራት ዝቅተኛ ነው፤….” በማለት የሚያሰራጩትን የአገሪቱን ገጽታ አፍራሽ ፕሮፓጋንዳ ለማክሸፍ፣ አዲስ ስትራቴጂ ቀርፀው መንቀሳቀስ መጀመራቸውን ድርጅቶቹ ተናግረዋል፡፡ በዚሁ መሠረት የኢትዮጵያ አየር መንገድ የቱሪስቶችን ቁጥር ለማብዛት በትራንስፖርት ክፍያ ላይ 40 በመቶ ቅናሽ ማድረጉን የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማርያም የገለጹ ሲሆን፣ የቱር ኦፕሬተሮች አሶስዬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ፍፁም ገዛኸኝ በበኩላቸው፤ አስጐብኚ ድርጅቶች ከሚያስከፍሉት የአገልግሎት ዋጋ ላይ 20 በመቶ እንደሚቀንሱ አስታውቀዋል፡፡

የሆቴሎች ማኅበር ፕሬዚዳንት አገር ውስጥ ባለመኖራቸው ምን ያህል እንደሚቀንሱ አልታወቀም፡፡ አዲሱ ስትራቴጂ የኢትዮጵያ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቱሪስት መስህቦች አውቆ መለየትና ለቱሪስቶች ማስተዋወቅ ነው ያሉት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ታደሰ፣ ለቱሪስት መዳረሻዎቹ አስፈላጊ መሠረተ ልማት (የአየርና የየብስ ትራንስፖርት፣ የንፁህ ውሃና የመብራት) አገልግሎት ማሟላት በቱሪስት መዳረሻዎቹ አካባቢ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ንፅህናው የተሟላ የመኝታ፣ የምግብ፣ አስተማማኝ ጥበቃና የደህንነት አገልግሎት በመስጠት፣ የኢትዮጵያ እምቅ ተፈጥሮዊና ታሪካዊ መስህቦች ለዓለም ማስተዋወቅ፣ የቱሪስቶችን ቁጥር ማብዛትና ከቱሪዝም ዘርፍ የሚገኘውን ገቢ ማሳደግ የስትራቴጂው ግብ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ ቀደም ሲል በረሃብ፣ ድርቅና ጦርነት የምትታወቀው ኢትዮጵያ፤ ባለፉት 20 ዓመታት ባሳየችው የልማት እንቅስቃሴ በዓለም አቀፍ ደረጃ ገጽታዋ እየተለወጠ ነው ያሉት አቶ ተወልደ፤ ሚዲያውና በዘርፉ የተሰማራን ሁሉ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም፣ ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ አገልግሎት በመስጠት፣ ቱሪስቶችን ለመሳብ እንረባረብ ብለዋል፡፡

የምሥራቅ አፍሪካ አገሮችን (ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ታንዛንያ) የሚጐበኙ ቱሪስቶች ቁጥር በርካታ እንደሆነ የገለፁት አቶ ተወልደ፤ ለምሳሌ በዓመት ኬንያን የሚጐበኙ ቱሪስቶች ቁጥር ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ሲሆን ኢትዮጵያን የሚጎበኙት ቱሪስቶች ከግማሽ ሚሊዮን በታች እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም ታዋቂና የአፍሪካ መዳረሻውም ብዙ ስለሆነ፣ ቱሪስቶች ወደ ምስራቅ አፍሪካ አገራት የሚጓዙት በእኛ አውሮፕላን ነው፡፡ በአዲሱ ስትራቴጂ ዋጋችን ተመጣጣኝና ተወዳዳሪ ስለሚያደርገን፣ የምንሰጠውም አገልግሎት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የሚያሟላ ስለሚሆን ብዙ ቱሪስቶች ወደ አገራችን ይመጣሉ ብለዋል፡፡ የቱሪስት መስህቦቻችንን ማልማትና ማስተዋወቅ/ በቅርቡ የተቋቋሙት የኢትዮጵያ ቱሪዝም ቦርድና ኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዋነኛ ተግባር ናቸው ያሉት አቶ ፍፁም፤ 80 በመቶ መስህቦቻችንን ለማልማት፣ 20 በመቶ ዳግም ለማስተዋወቅ ሥራ የተሰጠ በመሆኑ፣ የቱሪስት መዳረሻዎችን መሰረተ ልማት ማሟላት፣ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት፣ ማህበረሰቡን ማስተማር ሰፊ ድርሻ የተሰጠው በመሆኑ፤ የቱሪስቶች ቅሬታ ስለሚወገድ ብዙ ጎብኚ ይኖረናል ብለዋል፡፡

Read 3251 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:16
Administrator

Latest from Administrator