Saturday, 10 May 2014 11:45

2ኛው “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006” በሚሊኒየም አዳራሽ ይቀርባል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

         የሼፎችና ባሬስታዎች ውድድር ይካሄዳል ሁለተኛው “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006”፤ ከግንቦት 8 እስከ 10 በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚካሄድ ኦዚ ሆስፒታሊቲ እና ቢዝነስ ግሩፕ አስታወቀ፡፡ በፕሮግራሙ ላይ የተለያዩ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ ማሽኖችና ሶፍትዌር አቅራቢዎች፣ የሆቴል አማካሪ ድርጅቶች፣ ሆቴሎች፣ ሪዞርቶች ፣ የሆቴል እቃ አቅራቢዎችና የአስጐብኚ ድርጅቶች የሚሳተፉበት የንግድ ትርኢት እንደሚቀርብ ተጠቁሟል፡፡ የሀገሪቱን የሆቴልና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ ወደተሻለ ደረጃ ለማድረስ እና ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችል ሲምፖዚየምም የዝግጅቱ አካል ሲሆን በሲምፖዚየሙ ላይ ከ400 በላይ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎች ምክክር ያደርጉበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የሼፎችና ባሬስታዎች ውድድርም የሚካሄድ ሲሆን ውድድሩ ከጣሊያን እና ቱርክ በመጡ ዳኞች እንደሚዳኝ ተገልጿል፡፡ “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006” በኢፌዲሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ድጋፍ እንደሚደረግለት የተገለፀ ሲሆን ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንዲጐበኘውና በዘርፉ ያለው ግንዛቤ እንዲሰፋ መግቢያ በነፃ እንዲሆን መወሰኑ ተገልጿል፡፡ ዝግጅቱን ከ35ሺህ በላይ ሰዎች ይጐበኙታል ተብሎ እንደሚጠበቅ አዘጋጁ ኦዚ ሆስፒታሊቲ እና ቢዝነስ ግሩፕ ጠቁሟል፡ የመጀመሪያው “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2006” ከመስከረም 30 እስከ ጥቅምት 2 ቀን 2006 ዓ.ም በተባበሩት መንግስታት የስብሰባ አዳራሽ መካሄዱ የሚታወስ ሲሆን ከ7500 በላይ ሰዎች የንግድ ትርኢቱን እንደጐበኙት ታውቋል፡፡

Read 1478 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:28