Saturday, 10 May 2014 11:30

ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ሁለት ሪዞርቶች እየገነባ ነው

Written by 
Rate this item
(0 votes)

             ከሩብ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ ለመኪና ማቆሚያ የሚሆን ፎቅ እንደሚያስገነባ የገለፀው ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ በቡራዩ እና በቢሾፍቱ ሁለት ዘመናዊ ሪዞርቶችን ሊያስገነባ ነው፡፡ ባለፈው ህዳር ወር ስራ የጀመረው ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ አለማቀፍ ደረጃዎችን በማሟላት በሃገራችን አሉ ከሚባሉ ሆቴሎች አንዱ መሆኑን የገለፁት ስራ አስኪያጁ ፕ/ር ኤዲ ባሬንቶ፤ በግንባታ ጥበቡ በውስጣዊ ይዘቱ፣ በቴክኖሎጂዎች አጠቃቀሙና በሰው ኃይል አደረጃጀቱ እጅግ ዘመናዊ በመሆኑ የአፍሪካ መዲና የሆነችው አዲስ አበባ ድምቀት እንደሆነ ማንም ሊመሰክር ይችላል ብለዋል፡፡ በ1690 ካሬ ሜትር ለመኪኖች ማቆሚያ (ፓርኪንግ) አገልግሎት የሚሰጥ አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ፎቅ በ 258 ሚሊዮን ብር እንደሚያስገነባ ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡

የኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ፤ ዘመናዊ የመዝናኛ ስፍራዎችንና ሰፋፊ የስብሰባ አዳራሾችን ያካተተ ሪዞርት በቡራዩ እያስገነቡ ሲሆን፤ ሪዞርቱ አዲስ አበባን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ከፍታ ቦታ ላይ መሆኑን ፕ/ር ባሬንቶ ገልፀዋል፡፡ በቢሾፍቱ ባቦጋያ ሃይቅ አካባቢ እየተገነባ ያለው ሌላው ሪዞርት እጅግ ዘመናዊ መሆኑን ፕ/ር ባሬንቱ ሲያስረዱ፤ በአገሪቱ የመጀመሪያው ተጠቃሽ እንደሚሆን ጠቁመው፤ 2500 ሰው መያዝ የሚችል የስብሰባ አዳራሽ የያዘ ነው ብለዋል፡፡

በሆቴል ዘርፍ በቢሊዮን ብር የሚቆጠር ሃብት ኢንቨስት ያደረጉት አቶ ገምሹ በየነ፤ በመሰረተ ልማት በተለይም በመንገድ ግንባታ ላይ የተሰማራ “ገምሹ በየነ ኮንስትራክሽን (GEBECON)” የተሰኘ ኩባንያ ባለቤት መሆናቸውን ፕ/ሩ ጠቅሰው፤ በሃገሪቱ የመሰረተ ልማት እድገትና የስራ እድል ፈጠራ ላይ የራሳቸውን አሻራ ለማሳረፍ እንደቻሉ ተናግረዋል፡፡ ከ6ሺ በላይ ሰራተኞች ያሉት የኮንስትራክሽን ኩባንያው፤ በእውቅ የምህንድስና ባለሙያዎች የተደራጀ መሆኑን የገለፁት ፕ/ሩ፣ ከገነባቸው መንገዶች መካከል በትግራይ ከማሃበሬ እስከ ዲማ እና ከዲማ እስከ ፈየል ውሃ፣ በጐንደር ከአዘዞ እስከ ጎርጎራ እና የመሃል ሜዳ መንገድ ይገኙበታል፡፡ በተጨማሪም ከድሬድዋ እስከ ደወሌ እንዲሁም በሶማሌና በሃረሪ ክልል የመንገድ ግንባታዎችን ያከናወነው ኩባንያው፣ በርካታ መንገዶችን ሰርቶ እንዳስረከበ ተገልጿል፡፡

ፕ/ር ባሬንቶ ስለ አቶ ገምሹ በየነ ሲናገሩ፤ ከኢንቨስትመንት ጋር በተለይ በበጐ አድራጐትና በአገር ወዳድነታቸው የሚታወቁ ናቸው ይላሉ፡፡ በዘርና በጎሳ የማያምኑ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን ባላቸው እውቀትና ብቃት ሰርተው ኑሯቸውን እያሻሻሉ፣ ሃገራቸውንም እንዲጠቅሙ የሚጣጣሩ በመሆናቸው፣ በፈተና እና በስራ ምዘና እንጂ በዝምድና እንኳ እንደማይቀጥሩ በማየት እናደንቃቸዋለን ብለዋል፤ ፕ/ር ባሬንቶ፡፡

Read 2481 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:31