Saturday, 10 May 2014 11:26

አዲስ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ በሰንዳፋ ሊገነባ ነው

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(1 Vote)

•    ለግንባታው 31 ሚሊዮን ዩሮ ያስፈልጋል ተብሏል
በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚገኘውን የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ (የቆሼ - ረጲ ቆሻሻ ማስወገጃ) ለመለወጥ የሚያስችል የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ በሰንዳፋ ሊገነባ  ሲሆን ግንባታው 31 ሚሊዮን ዩሮ እንደሚፈጅ ታውቋል፡፡
አዲሱ የቆሻሻ ማስወገጃ ሥፍራ ከአዲስ አበባ ከተማ በተጨማሪ፣ በከተማዋ ዙሪያ የሚገኙ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችንም ተጠቃሚ ያደርጋል ተብሏል፡፡
ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከትናንት በስቲያ በቀረበው የብድር ስምምነት ማፅደቂያ ረቂቅ አዋጅ ላይ እንደተገለፀው፤ የአዲስ አበባ ከተማን የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ዘመናዊና ተደራሽ ለማድረግና ለነዋሪው ደረጃውን የጠበቀ ቀልጣፋ የቆሻሻ አወጋገድ አገልግሎት ለመስጠት እንዲቻል ጥረት ሲደረግ ቆይቷል፡፡ የከተማዋ አስተዳደር ከኦሮሚያ ክልል መስተዳድር ጋር በመመካከር፣ ለዚሁ ተግባር የሚውል ቦታ በሰንዳፋ አካባቢ እንዳዘጋጀም ተጠቁሟል፡፡
ለአዲሱ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ግንባታ፣ 31 ሚሊዮን ዩሮ የሚያስፈልግ ሲሆን 20 ሚሊዮን ዩሮ ያህሉ  ከፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ በብድር እንደተገኘ  ተገልጿል፡፡ ቀሪው ገንዘብ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሚሸፈን እንደሚሆን  ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው የብድር ስምምነት ማፅደቂያ ረቂቅ አዋጅ አመልክቷል፡፡

Read 2356 times