Print this page
Saturday, 10 May 2014 11:21

አርቲስት ታምሩ ብርሃኑ ከድራማ ጨረታ ጋር በተያያዘ በኢቴቪ ላይ ቅሬታውን አሰማ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(2 votes)

•    ድርጅታችን አሸናፊ መሆኑ ከተገለፀልን በኋላ ያለ አግባብ ውጤቱ ተሰርዟል
•    ጉዳዩን ለፀረ ሙስና አቅርቧል

የ “ታምሩ ፕሮዳክሽን” ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አርቲስት ታምሩ ብርሃኑ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ለተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች ባወጣው ጨረታ ያለአግባብ በደል ፈጽሞብኛል ሲል ቅሬታውን ገለፀ፡፡
አርቲስቱ ትናንት ረፋድ ላይ ቦሌ በሚገኘው አምባሳደር ሆቴል በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው የቅሬታው መንስኤ ኢሬቴድ ነሐሴ ወር 2005 ዓ.ም ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎችን ለማቅረብ ፍላጐት ያላቸው ድርጅቶች እንዲወዳደሩ ባወጣው ጨረታ የተሳተፈው ድርጅቱ “ታምሩ ፕሮዳክሽን” አንደኛ መውጣቱ ከድርጅቱ የስራ ሃላፊዎች ከተገለፀለት በኋላ፣ ያለአግባብ ውጤቱ ተቀይሮ ከአሸናፊነት እንዲሰረዝ ተደርጓል፡፡
“ታምሩ ፕሮዳክሽን” አንደኛ መውጣቱ ከተገለፀለት በኋላ፣ ኢሬቴድ በጨረታ ሰነዱ ውስጥ ያልተካተተ “የመጨረሻ ዙር” የሚል ውድድር አዘጋጅቶ አንደኛ የወጣውን የታምሩ ፕሮዳክሽን ነጥብ በመሻር፣ ሚያዚያ 24 በተፃፈ ደብዳቤ ከጫወታ ውጭ እንዳደረገው የገለፀው አርቲስት ታምሩ፣ ድርጊቱ በጣም እንዳሳዘነው ጠቁሞ፣  “ከዚህ ጋር ተያይዞ የደረስብንን የሞራል የገንዘብ የጊዜና ሌሎች ኪሳራዎቻችን በህጋዊ መንገድ ለማካካስ ጥረት እናደርጋለን” ብሏል፡፡  ጉዳዩን ለኢፌዲሪ የስነ ምግባርና የፀረ - ሙስና ኮሚሽን አቅርቦ  እየታዬ መሆኑን ጠቁሞ፣ በተጨማሪም ለኢሬቴድ ዋና ዳይሬክተርና ለቦርድ ሰብሳቢው ለአቶ ሬድዋን ሁሴን አቤቱታ ማቅረቡንና ጉዳዩ ተመርምሮ በአጭር ጊዜ መፍትሔ እንደሚሰጥበት ቃል እንደገቡለት ተናግሯል፡፡ ድርጅቱ ተገቢውን መፍትሔ የማይሰጠው ከሆነ፤  ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት እንደሚወስደውም ገልጿል፡፡
ጉዳዩን ለማጣራት የኢሬቴድ ኮሚሽኒንግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ለሆኑት አቶ ገብረአምላክ ተካ በተደጋጋሚ ብንደውልም ስልካቸውን ባለማንሳታቸው ምላሻቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡ ወደ ድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅና ም/ሥራ አስኪያጅ ቢሮ ደውለን የነበረ ሲሆን ሁለቱም ስብሰባ ላይ በመሆናቸው ልታገኟቸው አትችሉም የሚል ምላሽ ከፀሐፊዋ አግኝተናል፡፡


Read 1614 times Last modified on Saturday, 10 May 2014 13:37