Saturday, 03 May 2014 12:20

የዛሚ ሬዲዮ ሚሚ ስብሃቱ በታሰሩት ጋዜጠኞች፣ በፕሬስ ነፃነትና ያለመረጃ በሚሰሩ ውንጀላዎች ላይ

Written by  አበባየሁ ገበያው እና አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(19 votes)

የአለማቀፉ የፕሬስ ነፃነት ቀን በዛሬው እለት “Media freedom for abetter feauture` በሚል መሪ ቃል ይከበራል፡፡ ይህን ምክንያት በማድረግ በኢትዮጵያ የፕሬስ ካውንስል ለማቋቋም በሚደረገው ጥረት ተሣታፊ ከሆነችው ጋዜጠኛ ሚሚ ስብሃቱ ጋር ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው እና አለማየሁ አንበሴ ስለሀገራችን የፕሬስ ተግዳሮች ስለ ካውንስል ምስረታው እና የተለያዩ ጉዳዮች ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡፡  

የአገራችን የፕሬስ ተግዳሮቶች ምንድን ናቸው ትያለሽ?
እንደ ኢንዱስትሪ ተግዳሮቶቹ ሁለት ናቸው፡፡ ውስጣዊም ውጫዊም ናቸው፡፡ የመገናኛ ብዙሃን ኢንዱስትሪው ራሱን በራሱ የሚቆጣጠርበትና ራሱን በራሱ የሚያሻሽልበት ስርዓት እስከ አሁን ድረስ መገንባት አለመቻሉ ከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ መሆኑን ያሳያል፡፡ ብዙዎችን ለማስተናገድ፣ ብዙ የሰው ሃይል አቅፎ ለመንቀሳቀስ፤ እንደሀገሪቱ ግዙፍነት፣ እንደ ህዝባችን ብዛት የተደራሽነት አቅም እንዲኖር የማያስችል ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ሀገሪቱ ጥርት ያለ የሚዲያ ፖሊሲ የላትም፡፡ በሌሎች አገሮች መገናኛ ብዙሃን እንዲያብቡ፣ እንዲጐለብቱ ብዙ ድጋፍ ይደረጋል፡፡ ማተሚያ ቤቶች እንዲያቋቁሙ ሃሳብ ከመስጠት ጀምሮ በፓርላማ አማካኝነት ከመንግስት ገንዘብ የሚመደብበት አሰራር አለ፡፡ ለምሳሌ በአገራችን የማተሚያ ቤት ችግር አለ፡፡ የእሁዱን ጋዜጣ ረቡዕ እያነበብን ነው፡፡ እነዚህ ሁኔታዎችን ነው እንደ ተግዳሮት የምናስባቸው፡፡
ከ10 ዓመት በፊት ከነበረው ጋር ሲነፃፀር አሁን ያለው የፕሬስ ደረጃ ምን ይመስላል፡፡ ያኔ በመቶዎች የሚቆጠሩ ጋዜጦች ይታተሙ ነበር፡፡ አሁን በጣት የሚቆጠሩ ናቸው ያሉት….
ከአስር ዓመት በፊት የነበረው የህትመት መገናኛ ብዙሃን ብዛት እንጂ ጥራት አልነበረውም፡፡ መፃፍ የቻለው ሁሉ የፈለገውን የሚጽፍበት ጊዜ ነበር፡፡ ከብሔር ብሔረሰቦች ጀምሮ ግለሰቦች የሚብጠለጠሉበት፤ አንድ ገፅ እንኳን ትክክለኛ ዜናና መረጃ ተፈልጐ የማይገኝበት የህትመት መገናኛ ብዙሃን ነበር፡፡ መገናኛ ብዙሃን ህዝብን መለወጥ አለባቸው፡፡ የህዝብን ህይወት ለማሻሻል ትልቅ አስተዋጽኦ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ የሰው ልጅ የመገናኛ ብዙሀንን  የፈጠረው ለሰዎች የተሻለ ህይወት ለማምጣት ነው፡፡
ከዚህ አንፃር ሲታይ ከ10 ዓመት በፊት የነበሩት ምንም ዓይነት ዓላማ ያልነበራቸው፣ እንደውም ህብረተሰቡን ብዥታ ውስጥ የሚከቱ፣ ምንም ዓይነት መረጃ የማይሰጡ፣ በአሉባልታና በወሬ የተሞሉ ነበሩ፡፡ ከአስር ዓመት ወዲህ ያሉት ቁጥራቸው ቢያንስም የጋዜጠኝነት ሙያን እየተገበሩ ነው እስከዛሬ የዘለቁት፡፡ በእርግጥ ከ10 ዓመት በፊት የነበረው ጊዜ የመገናኛ ብዙሃን እድገት አንድ ምዕራፍ ነው፡
ያንን አልፈን አሁን ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ ነን፡፡ የመገናኛ ብዙሃን መርሆቻቸውንና ስነምግባሮቻቸውን አክብረው የሚንቀሳቀሱበት፤ መፃፍ የቻለ ሁሉ የፈለገውን የሚዘባርቅበት ሳይሆን ሙያተኞች ወደ ዘርፉ ገብተው የህዝብ ልሳንነታቸውንና አገልጋይነታቸውን በተግባር እያሳዩ ያሉበት ወቅት ነው፡፡ በአገራችን ያለውን የህትመት መገናኛ ብዙሃን ስንመለከት  ምንም የለም ለማለት ያስደፍራል፡፡ የኤሌክትሮኒክስ የመገናኛ ብዙሃን በተወሰነ ደረጃ አድጓል፡፡ በህትመት የመገናኛ ብዙሃን ከብዛት ይልቅ ጥራቱ የሚታይበት ደረጃ ላይ ነው ያለው፡፡
የፕሬስ ካውንስል ለማቋቋም እንቅስቃሴ ስታደርጉ ነበር፡፡  ምን ላይ ደረሰ?
ጨርሰናል ማለት ይቻላል፡፡ በተቋሙና በሥነምግባር ደንቡ (በኮድ ኦፍ ኮንዳክቱ) ላይ የመጀመሪያ ዙር ውይይት አድርገናል፡፡ በቀጣይ ያለውን ሂደት ለመጀመር እየተዘጋጀን ነው፡፡ በቅርቡ አዲስ ነገር ይኖራል፡፡
የአለም የፕሬስ ነፃነት በሚከበርበት ዋዜማ 6 ጦማሪዎች (ብሎገሮች) እና 3 ጋዜጠኞች ታስረዋል፡፡ ዓለማቀፍ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋቾች ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ከኤርትራ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ እንደምትገኝ ሪፖርት አውጥተዋል፡፡ በእዚህ ጉዳይ ላይ የአንቺ አስተያየት ምንድነው?
በመሠረቱ የጋዜጠኞች  መብት ተሟጋች ነን ብለው የሚንቀሳቀሱ ዓለምአቀፍ ተቋማት ላይ እምነት የለኝም፡፡ ተዓማኒነታቸው የወደቀ ነው፡፡ የሚሠሯቸውን ስራዎች ስለማውቅ ነው፡፡ የሀገራችን ሁኔታም አልጋ በአልጋ አይደለም፡፡ ታሰሩ ስለተባሉት ሰዎች ጉዳይ ፖሊስን ጠይቀን አጣርተናል፡፡ “ከውጭ ሃይሎች ጋር እየተገናኙ በሀገሪቱ ሁከትና ብጥብጥ ለመቀስቀስ ሙከራ ሲያደርጉ ደርሸባቸዋለሁ” ነው ያለው ፖሊስ፡፡
በእርግጥ ጋዜጠኛ አይታሰርም፤ ነገር ግን ጋዜጠኛ አይታሰርም ሲባል ከህግ በላይ ነው ማለት አይደለም፡፡ ህግ መከበር አለበት፡፡ በተለይ ደግሞ አገርን አደጋ ላይ ሊጥሉ ከሚችሉ ነገሮች ከማንም በላይ ቀድሞ ዘብ መቆም ያለበት ጋዜጠኛው ነው፡፡ በዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን የተለመዱት ጩኸቶች ይኖራሉ፡፡ የዘንድሮው የሚከበረው በጣሊያን ነው፡፡ በዛ ቦታ ያ ሩጫ ሊኖር ይችላል፡፡ ግን መታወቅ ያለበት ማንም ቢሆን ጋዜጠኛም፣ ተራ ዜጋም፣ መንግስትም ቢሆን  ከህግ በላይ አይደሉም፡፡ ነፃነት ከሃላፊነት ጋር ነው የሚመጣው፡፡
የሚፃፈው ነገር ምን ያስከትላል ተብሎ መታየት አለበት፡፡ ይሄ የሙያው መርህና ስነምግባር የሚያጐናፅፈው ክህሎት ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ሁኔታ መፈጠሩ (ሰዎቹ መታሰራቸው) ደስ የማይልበት ሁኔታ አለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የማናውቀው ነገር አለ፡፡ ፖሊስ አለኝ የሚለውን ማስረጃና የፍርድ ቤትን ውሳኔ ማየት አለብን፡፡
በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የፀረ ሽብር ህጉ ጋዜጠኞች በነፃነት እንዳይሰሩ እንቅፋት እንደሆነና ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትን እየሸረሸረ ነው የሚል ወቀሳ እየተሰነዘረ ነው፡፡ በዚህ ላይስ ምን ትያለሽ?
ሽብር ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን መላው ዓለም  እየተጋፈጠው ያለ አደጋ ነው፡፡ ብዙ ሃገሮች የፀረ ሽብር ህግ አላቸው፡፡ የፀረ ሽብር ህጉ የተለየ ሆኖ ትኩረት የሚስበው የተወሰኑ ሲቪል መብቶችን ስለሚገድብ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለደህንነት የሚከፈል መስዋዕትነት ነው፡፡ በሰላም ወጥቶ ለመግባት፣ በሰላም ልጆችን ለማሳደግ ህዝቦች እንደዚህ አይነቱን ህግ የሚቀበሉበት ሁኔታ አለ፡፡ የመከላከል ህግ እኮ ነው! የጭቃ ሹም አስተሳሰብ ያለው ሹመኛ ያለአግባብ ሊጠቀምበት ይችላል፤ በተገቢው መንገድ ተግባራዊ ከተደረገ ግን አሸባሪዎች ፍንዳታ ከማድረሳቸው በፊት ይያዛሉ፡፡ አወዛጋቢ የሆነው የፀረ ሽብር ህግ፣ በተለያዩ ሀገሮችም አለ፡፡ በተወሰነ ደረጃ በህገመንግስቱ ውስጥ አይነኬ የሆኑት ሁሉ ይነካሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ለመዳን ስንል የምናደርገው፤ የምንወስደው እርምጃ ነው፡፡ እኛም እንደባለሙያ መሳሪያ እንዳንሆን መጠንቀቅ አለብን፡፡ የምናገኛቸውን መረጃዎች ደግመን ደጋግመን ማረጋገጥ አለብን፡፡ መረጃ ስለተገኘ ብቻ አይደለም የምንጠቀመው፡፡ የፀረ ሽብር ህጉ ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ላይ ጫና ይፈጥራል ብዬ አላምንም፡፡ ሃሳባችንን መግለጽ፣ ጉዳያችንን ማስተጋባት እንችላለን፡፡ እንፅፋለን እናነባለን፡፡ ከህጉ ጋር የምንጋጨው፣ ነፃ አውጭነት ወይም ፋኖነት ሲሰማን ነው፡፡ የእኛ ብዕር ዓላማ ደግሞ ፋኖነት አይደለም፡፡ ተነስ፣ ውጣ ታገል፣ ታሰር… ማለት የእኛ ስራ አይደለም፡፡ ይሄንን ሚዛናዊ አድርጐ የመሄድ ጥያቄ ነው፡፡ የፀረ ሽብር ህጉ የት ላይ ነው ቀጫጭን መስመሮች ያሉት የሚለውን እኛ ማወቅ አለብን፡፡
የመንግስት የመረጃ ስስት የፕሬሱን ዕድገት አቀጭጮታል የሚሉ ሃሳቦች ይሰነዘራሉ፡፡ በዚህ ሃሳብ ትስማሚያለሽ?
መረጃ የማግኘት መብትን በተመለከተ በህግ ተቀምጧል፡፡ ብዙ አገሮች እንደውም የላቸውም፡፡ ኢትዮጵያ የመረጃ ነፃነት ህግ  አላት፡፡ ማህበረሰባችን የመጣበት ሁኔታ በራሱ መረጃ መስጠትን አያበረታታም፡፡ መረጃ መስጠት ግዴታቸው፣ ሃላፊነታቸው መሆኑን የማያውቁ የመንግስት ባለሥልጣናት አሉ፡፡ እንደማህበረሰብ ግልጽ አይደለንም፤ በጣም ዝግ ማህበረሰብ ነው፡፡ ያንን ዝግ ማህበረሰብ ነው ለመክፈትና መረጃ ለማግኘት የምንሞክረው፡፡ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መደበኛ ስራቸው የምርመራ ጋዜጠኝነት (Investigative Journalism) የምንለው ነው፡፡ ምክንያቱም መረጃ ለማግኘት ብዙ ርቀት መሄድ ያስፈልጋል፡፡
የመገናኛ ብዙሃኑ አበቃቀልና አስተዳደግ ታሪክም ለዚህ የሚያመች አይደለም ይፈራል፡፡ መረጃ ሰጪው አካልና ጋዜጠኛው እንደ አጋር ነው መተያየት ያለባቸው፡፡ የምንሰራበት ማዕቀፍ ግን መረጃ መጠየቅና መስጠትን እንደ አይጥና ድመት የሚታይበት ነው፡፡ የህግ ማዕቀፉ ግን ተቀምጧል፡፡ ማንም የመንግስት ባለስልጣን መረጃ የመስጠት ግዴታ አለበት፡፡
በመገናኛ ብዙሃን አሰራር የዳበረ ባህልና ልምድ ባላቸው አገሮች፣ ምንም ቢፃፍ ማንም ዞር ብሎ አያያቸውም፡፡ ህብረተሰቡ የፀሐፊው እብደት ነው ብሎ ነው የሚያስበው፡፡ የመገናኛ ብዙሃንን እንደ ተፅዕኖ ፈጣሪ (ኦቶሪቲ) የሚወስድ እንደኛ ያለ ማህበረሰብ ውስጥ ሲኮን ነው ፍጥጫው የሚመጣው፡፡ “ተነስ…የማይነሳ ህዝብ ፈሪ ነው፣ ዘላለም በፍርሃት የተጨማደደ” ተብሎ የሚፃፍበትን ጋዜጣ ግን ጋዜጣ ነው ብዬ ለመቀበልም፣ ለመናገርም ይቸግረኛል፤ ሙያውን ስለማውቅ፡፡
የእዚህ ዓይነት መገናኛ ብዙሃን ዓላማ ህዝቡ በመንግስትና በተቋማት ላይ እምነት እንዲያጣ ማድረግ  ነው፡፡ ተቋማትም ሆነ መንግስት የሚሻሻለው ግን ሚዲያው የጉዳዩ ባለቤት ሲያደርገው ነው፤ “እንዲህ አስተካክል” ሲለው እንጂ አሁን በሚታየው መንገድ አይደለም፡፡ በመንግስት ወገን የሚደረገውም ትክክል ነው እያልኩ አይደለም፡፡ እኔ መንግስትን ብሆን ጋዜጦቹን አልነካቸውም ነበር፡፡ በሌላ በኩል ግንበውጭ አገር ያሉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ነን ባዮች አይዋጡልኝም፡፡ ትክክለኛውን የጋዜጠኝነት ሙያ ተከትሎ የሚሠራ ሚዲያን አይፈልጉም፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ ሁከት የሚያመጣን ነው የሚደግፉት፡፡
በዛሚ ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ “የጋዜጠኞችየክብ ጠረጴዛ” ፕሮግራም ላይ ጋዜጦችና የጋዜጠኞች ማህበር ከውጪ ተቋማትና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ገንዘብና ድጋፍ ያገኛሉ የሚሉ ውንጀላዎች ይሰነዘራሉ፡፡ በዚህም ዛሚ ወንጃይ ሆኗል በሚል የሚተቹ ወገኖች አሉ፡፡
ይሄ ውንጀላ አይደለም፡፡ ዛሚም እኮ የሚዲያ ተቋም ነው፡፡ ዛሚም እኮ ሁኔታውን ያያል፣ የማይደራድርባቸው መርሆዎች አሉት፡፡ በዚህም ምክንያት ገንዘብና ድጋፍ አይደረግለትም፡፡ ከዚህ ቀደምም የተጠየቅንበት ሁኔታ ነበር፡፡ ገንዘቡ እንዳለ፣ ገንዘቡ እንደሚመጣ አውቃለሁ፡፡ የጋዜጠኞች የክብ ጠረጴዛ አላማም ሙያችን፣ ኢንዱስትሪው በጠንካራ እና ትክክለኛ መሠረት ላይ እንዲገነባ ብቻ ሳይሆን እንደዚህ ዓይነት ነገሮችን ህብረተሰቡ እንዲያውቅ ማድረግም ነው፡፡
በቀደም ዕለት በክብ ጠረጴዛ ፕሮግራም ላይ ከፖሊስ ያገኘሁትን መረጃ አውርቻቸዋለሁ፡፡ ከኬንያ የመጣው የ“አርቲክል 19” ሰውዬ… ኬንያዊ ያደረጉት እኮ… “አርቲክል 19” ነጭ አጥተው አይደለም፡፡ ነጩ ከመጣ  መንግስት ሊያየውናአይኑን ሊጥልበት ይችላል ብለው ነው፡፡ ይሄኛው ግን  ቪዛም አያስፈልገውም በሚል ነው መርጠው የላኩት፡፡ ይሄ ሰውዬ  አምስት ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ተመላልሷል፡፡ የተወሰኑ ጋዜጠኞችን ብቻ ነው የሚያሰለጥነው፡፡ ውጭ አገር የሚወስዱት፣ ትልልቅ ሆቴሎች ውስጥ ስብሰባ የሚያደርጉት ከተወሰኑ ጋዜጠኞች ጋር ብቻ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ለኢትዮጵያ ጋዜጠኞች እድገት አይጠቅምም፡፡
የፕሬስ አዋጁ ሲረቀቅ ሸራተን በተደረገው ስብሰባ “አርቲክል 19” የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉ ይነገራል፡፡ ይሄ እውነት ከሆነ የአሁኑ ስልጠና ለምን እንደ ወንጀል ተወሰደ?
“አርቲክል 19” ቶቢ ሜንደ የተባለ ባለሙያ በመላክ በኤክስፐርት ደረጃ እገዛ አድርጓል፡፡ ገንዘብ ግን አልሰጠም፡፡ ተቋሙ አዲስ አበባ ጋዜጠኞች አሰለጥናለሁ ብሎ ለምንድን ነው የተመረጡት ጋዜጠኞችን  ብቻ የሚወስደው? ለምንድን ነው ስልጠናውን በድብቅ የሚያካሂደው? ለሁሉም አዲስ አበባ ላሉ ጋዜጠኞች (ለየተቋማቱ) ደብዳቤ ልኮ ሥልጠናውን መስጠት ይችል ነበር፡፡ እነማን ናቸው የተመረጡት? ምንድን ናቸው? በመንግስት ቦታ ብትሆኑ እኮ አስተያየታችሁ ሌላ ይሆናል፡፡ ሰውየው እኮ ገንዘብ እያመጣ ይሰጣል፡፡ ይሄ ምን ሊባል ይችላል? “የጋዜጠኞች የክብ ጠረጴዛን” አነሳችሁ እንጂ… ግብፅና ኤርትራ በግልጽ እኮ ነው የተናገሩት፡፡ ምንም አይነት መንገድ ተጠቅመን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለመረጋጋትን እንፈጥራለን ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊትም ለኢሳት ገንዘብ መስጠታቸውን እናውቃለን፤ በተጨባጭ የተረጋገጠ ነው፡፡ ሁላችሁም ተጠንቀቁ ነው የምንለው፡፡ በዳያስፖራው ውስጥ ከፍተኛ ገንዘብ በማንቀሳቀስ ለመበጥበጥ የተዘጋጁ አሉ፡፡ በዚህች አገር ውስጥ ህገወጥ እንቅስቃሴ ለማድረግ ፈቃደኛ ለሆኑ ሰዎች ገንዘብ ተዘጋጅቶ ተቀምጧል፡፡ ስለዚህ በሉዓላዊነታችሁ ላይ አትደራደሩ፡፡ ማንም ሚዲያ የአገሩን ጥቅም አሳልፎ እንዳይሰጥ…እንላለን፡፡
በተለያዩ የህትመት ውጤቶች ላይ “የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛን” ተቃውመው ሲጽፉ አያለሁ፤ መንግስትን የሚደግፍ በሚል፡፡ መንግስትን ደገፉ የሚባለው “ልማትህን ጠብቅ፣ ከድህነት የምትወጣው በልማት ላይ ስትተጋ ነው” ስለምንል ነው፡፡ ይሄን ለማለት የመንግስት ደጋፊ መሆን አይጠይቅም፡፡ ወደ አገሬ የመጣሁት ይሄን ልሠራ ነው፡፡ አሜሪካንን ትቼ የመጣሁት ጠንካራና የበለፀገ “ቫይብራንት” የሆነ የሚዲያ ኢንዱስትሪ ለመገንባት ነው፡፡ መንግስትን መቆጣጠር የሚችል፣ የመንግስት ጠላት ሳይሆን እንደ አንድ ተቋም የህዝብን ደህንነት በጋራ የሚጠብቅ ሚዲያ ለመፍጠር ነው፤
ጋዜጠኝነት፤ ልማታዊ የሚባል ቅፅል አያስፈልገውም፡፡ ጋዜጠኝነት በራሱ ልማታዊ ነው፡፡ እኔ “የፖለቲካ” ወይም “የታይብሎይድ” ጋዜጠኝነት በሚል በሚሰጠው ቅፅል ተስማምቼ አላውቅም፡፡ ጋዜጠኝነት “ኢንስትሩመንት ፎር ሂዩማን ቢንግ” (ለሰው ልጅ የሚያገለግል እንደማለት) ብዬ ነው የምከራከረው፡፡
ከኤርትራና ከግብፅ ገንዘብ ወስደዋል ብላችሁ ተናግራችኋል፤ ገንዘቡ መቼ ተሰጠ? ለማን ተሰጠ? እንዴት ተሰጠ?
እኛ እኮ ያንን የተናገርነው ከፖሊስ መረጃ ነው፡፡ የፖሊስ መረጃ ከተለያዩ አካባቢዎች ፈንድ በተለይ ከውጪ እንደሚደረግ ነው የጠቀሰው፡፡ የሆነ ሆኖ ግን ሃገሪቱን ለማተራመስ ቅርጫት አስቀምጠው የሚለምኑ ወገኖች እንዳሉ እናውቃለን፡፡
እነማን ናቸው ይሄን የሚያደርጉት በስም እንወቃቸው
እንዴ! ብርሃኑ ነጋ ከግብፅ ተቀብሎ በኢሳት ሲታይ አልነበረም እንዴ?
ብርሃኑ ነጋ መቀበሉ እነዚህን የሃገር ውስጥ ሚዲያዎች እና አክቲቪስቶች ለመወንጀል እንዴት ያስችለናል?
አይደለም! እኛ እኮ ሃሳብ የሰጠነው ሲቀባበሉ በዓይናችን አይተናል ብለን አይደለም፡፡ ከአርቲክል 19 ጋር በስውር ሲንቀሳቀሱ ከፖሊስ መረጃ ማግኘታችንን ነው የተናገርነው፡፡
በአጠቃላይ በዚህች ሃገር ውስጥ የጎዳና ላይ ነውጥ እንዲካሄድ ግፊት የሚያደርጉና ገንዘብ የሚያሰባስቡ ሃይሎች እንዳሉ የታወቀ ነው አልን እንጂ እነሱ ተቀብለዋል የሚል ውንጀላ አላቀረብንም፡፡ ልንልም አንችልም፡፡ የጎዳና ላይ ነውጥ የሚናፍቁ ወገኖች ገንዘብ እንዴት እንደሚያገኙ ነው የተናገርነው፡፡ ይሄ ደግሞ በአለማቀፍ ደረጃ የሚታወቅ መረጃ ነው፡፡ እኛ ገንዘብ ሲቀበሉ አይተናል የሚል ቃል አልወጣንም፡፡
ከዚህ ቀደም ሪፖርተርስ ዊዝ አውት ቦርደር የአንቺን ፕሮግራም ስፖንሰር ያደርግ ነበር ዛሬ ላይ ከእነዚህ ተቋማት ገንዘብ ተቀብሎ መስራቱን እንዴት ትኮንያለሽ?
በድብቅ ሲሆን ነዋ! እኛ እኮ በግልፅ እየተናገርን ሪፖርተርስ ዊዝ አውር ቦርደርስ ገንዘብ ሰጥቶናል ብለን ተናግረን ነው የተጠቀምነው፡፡ አሁን ግን በድብቅ ጋዜጠኞችን በየሆቴሉ ሰብስቦ ሰጠ  የሚል ነው ከፖሊስ ያገኘነው መረጃ፡፡
በሰብአዊ መብትና በሚዲያ ጉዳይ ላይ የሚሰሩ አለማቀፍ ተቋማት ሁሉም መንግስትን ይተቻሉ፡፡ ይሄ መንግስት ጋር ድክመት መኖሩን አያሳይም?
አንድ አይነት ትችት የሚያቀርቡት ምንጫቸው አንድ አይነት ስለሆነ ነው፡፡ ፍልስፍናቸው፣ ተልእኮአቸው፣ የገንዘብ ምንጫቸው አንድ አይነት ነው፡፡ ስለዚህ አንድ አይነት ነው ሊያወሩ የሚችሉት፡፡
ለኢህአዴግ ትወግናለች ኢህአዴግም ነች ትባያለሽ አንቺ ደግሞ ማስረጃ የሌለው ውንጀላ ነው ትያለሽ፡፡ እናንተስ ፕሬሶችንና ጋዜጠኞችን የውጭ ሃይሎች ተላላኪ ናቸው ስትሉ ያለ ማስረጃ መወንጀል አይሆንም?
እኔ ላይ ማስረጃ ማንም ሊያቀርብ አይችልም፡፡ እኔ ሚዲያ ነኝ፡፡ ሚዲያ ደግሞ ትልቁ መርሁ ገለልተኛነት ነው፡፡ እኔ ፖለቲከኛ ሆኜም አላውቅም፡፡ ልሆንም አልችልም፡፡ እኔ ላይ የሚቀርበውን ውንጀላ ያመጣው ሻዕቢያ ነው፡፡ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጊዜ ዜናውን መጀመሪያ ይፋ ያደረኩት እኔ ነኝ፡፡ ወረራ የተፈፀመው ኤርትራ ጦር እንደሆነ በመናገሬ፣ በወቅቱ  የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ሱዛን ራይትስ የኤርትራ ጉዞዋን ልትሰርዝ ችላለች፡፡ ስለዚህ የእኔን ተአማኒነት ለመሸርሸር ነው ሻዕቢያ ይሄን ዘመቻ የጀመረው፡፡ ነገር ግን እኔ በራሴ ስለምተማመን ስራዬንም ህዝብ የሚያየው ስለሆነ የሚያስጨንቀኝ ነገር አይደለም፡፡
አንቺስ ያለማስረጃ ወንጃይ አልሆንሽም ወይ ለተባለው እኛ በመጀመሪያ ደረጃ እገሌ እንዲህ አድርጓል ብለን አይደለም የምንናገረው፡፡ ፖሊስ የሰጠንን መረጃ ነው የተናገርነው፡፡
በተደጋጋሚ በክብ ጠረጴዛ ፕሮግራሞች ላይ ፕሬሶቹ ገለልተኛ እንዳይሆኑ ያደረጋቸው ገንዘብ ከፓርቲ ስለሚቀበሉ ነው የሚሉ ትችቶችንና ውንጀላዎችን ታቀርቢያለሽ፡፡ ለዚህ ማስረጃ አለሽ?
መልስ ነው የሃገራችን ፕሬሶች የሙያውን መርህና ስነ ምግባር ተከትለውመንቀሳቀስ አለባቸው ነው የምንለው
ከገንዘብ ጋር የተያያዘ ነገር ይነሳል፣ ከፓርቲ ፈንድ ይደረግላቸዋል ትላላችሁ ለዚህ ማስረጃ አላችሁ ወይ ነው ጥያቄያችን?
እኛ እንደዚያ ብለን አልፈረጅንም፡፡ ነገር ግን እንደዚህ አይነት ነገሮች በሌላው አለም እንዴት ነው የሚስተናገዱት የሚለውን በልምድም እናውቀዋለን ነው ያልነው እንጂ ተቀብለዋል የሚል መደምደሚያ ያለው ነገር አልተናገርንም፡፡ ያለውንና የምናውቀውን ሁኔታ እየተናገርን ጥንቃቄ እንደሚያስፈልግ ነው መልእክት የምናስተላልፈው፡፡ ጋዜጦች የፖለቲካ ፅንፍ መያዝ ይችላሉ ብለናል ነገር ግን በሙያው ስም መጠቀም የለባቸውም ነው መከራከሪያችን፡፡ የተቃዋሚ ድርጅት ልሳን ነኝ ብሎ ራሱን ይፋ ማድረግ እንጂ በመገናኛ ብዙሃን ስም ማጭበርበር አይቻልም፡፡ አክቲቪዝም እና ጋዜጠኝነት መለያየት አለባቸው ነው የኛ አቋም፡፡ ትችት ለምን ታቀርቢያለሽ ከሆነ እነሱም እኮ በኛ ላይ ብዙ ነገር ይፅፋሉ ይተቻሉ፡፡ እኔ እንደውም አሉባልታቸው ሲበዛ ነው ከሙያው ስነምግባር ጋር እያጣቀስኩ መተቸት የጀመርኩት፡፡

Read 7734 times