Saturday, 03 May 2014 12:19

የመጨረሻዋ ከሰአት ከተስፋለም ጋር

Written by  ኤልሳቤት ዕቁባይ
Rate this item
(7 votes)

         ተስፋለም ወልደየስን በጋዜጠኝነቱ እና በኢትዮጲያ የአካባቢ ጥበቃ ጋዜጠኞች አባልነቱ ምክንያት ከትውውቅ ያለፈ ጓደኝነት አለን፡፡ ከጀርባው የማትለየው ላብቶፑን አዝሎ ፈጠን ፈጠን እያለ በንቃት የሚንቀሳቀስ ለጋዜጠኝነት ሙያ ትልቅ ፍቅር እና ክብር ያለው ነው፡፡ ሙያው ልክ ተሳክቶላቸዋል በሚባሉ አገሮች ደረጃ  እንዲሆን ሁልጊዜም የሚመኝ ብቻ ሳይሆን ቅናቱን ለአፍታም ከመግለፅ የማይቆጠብ ነው፡፡ በየትኛውም መገናኛ ብዙሀን አሪፍ ነገር ተሰራ ሲል ያንን ከመናገር ወደ ሃላ የማይል የሰራውንም ሰው ማበረታታት ደስ የሚለው ነው፡፡
በህዳር ወር በኢትዮጲያ የተካሄደውን የሚዲያ ፎረም ማጠቃለያ የሆነውን ሰነድ ለአዘጋጇ ለኢትዮጲያ ለማስረከብ እና የቀጣዩን የሚዲያ ፎረም አዘጋጅ እና የፎረሙን መሪ ቃል ለማሳወቅ በኢሊሊ ሆቴል ባለፈው ሳምንት ረቡእ በተካሄደው ዝግጅት ላይ ከተስፋለም ጋር ተገናኝተናል፡፡ ምነው ጠፋሽ በሚል  ክፉኛ ወቀሰኝ፡፡ ስልኬን አትመልሺም  ብሎም ማዘኑን ነገረኝ ተለያየን፡፡ በማግስቱ ለአርብ ምሳ ለመብላት ተቀጣጠርን፡፡
አርብ እለት በቀጠሮአችን መሰረት ካዛንችስ በሚገኘው ሮሚና ሬስቶራንት በስድስት ተኩል ተገናኘን፡፡  ምሳ እየበላን ብዙ ነገሮችን አወራን፡፡ ልክ ሁልጊዜ እንደሚለው ሲኒሮቻችን የሆናችሁ ጋዜጠኞች ሙያውን ለምን ጣል ጣል ታደርጉታላችሁ አለና የተለመደውን የፕሮፌሽናሊዝም የኤቲክስ ጉዳዮችን አወራኝ፡፡ ፌስቡክ እንዴት እሱ የሚመኘውን ጋዜጠኝነት እየተገዳደርው እንደሆነ አዲስ ወደ ሙያው የሚገቡ ልጆች ኮትኳች እያጡ እንደሆነም ሲያወራኝ ነበር፡፡ ከዛም ሁለታችንም በቅርበት ስለምናውቀው በቅርብ አሜሪካን አገር ስለሄደ ልጅ አነሳንና ጨዋታችንን ቀጠልን እኔ የማዝነው  እሱን የመሰለ ልጅ አሜሪካን  ሲቀር አያሳዝንም እንዴት ይቀራል ብሎ በውስጡ የተፈጠረበትን ጥያቄ ጠየቀኝ፡፡
አባይን ለመጎብኘት ለጋዜጠኞች በተዘጋጀው የቅርብ ጊዜ ጉብኝትም ተስፋለም ተሳታፊ ስለነበርበተለይ በለስ ስለምትባል እናከተቆረቆች አስራ ሶስት አመት ስለሆናት ከተማ በስሜት ሲያወራኝም ነበር፡፡ አርቲስት ጆሲ ለማንአልሞሽዲቦ የሰራውን ፕሮግራምም በአድናቆት አውርቶኛል፡፡ ሰሞኑን እየተካሄደ በነበረው የጣና ፎረም ላይ ለመገኘት ፈልጎ የምዝገባው ጊዜ ስላመለጠው በቁጭት አውርቶኛል፡፡
ከምሳ በሃላ ቡና ለመጠጣት እዛው ካዛንችስ ሙንሽ ካፌ ገባን፡፡ የቴዲ አፍሮን ኮንሰርት እንዲያመልጠኝ አልፈልግም፡፡ ቴዲ እንዲህ አለ ተመልካቹ እንዲህ አለ የሚለውን ራሴ ማየት አለብኝ አለና ለጋዜጠኞች መግቢያ የያዙ ሰዎች ጋር ደወለ፡፡ ኤልሳቤት እቁባይም ትፈልጋለች አላቸው፡፡ ስልኩን ከዘጋው በሃላ እኔ ማምሸት ስለማልችል ካርዱን ትወስደዋለህ ስለው የስ ሰው እጋብዝበታለሁ አለኝ፡፡ ሌላ ቀጠሮ ስለነበረው ወደ ብሄራዊ ቲያትር ከመሄዱ በፊት እዛው ካዛንችስ ጫማ እያስጠረግን አንድ ጋዜ ማንበብ ጀመረ ጋዜጣው የአንድን ሰው ፎቶ አሳስቶ አውጥቶ ነበርና በሱ ተሳስቀን ይህህን ስካን አድርጌ እልክለታለሁ ሲል እኔ ደግሞ እባክህ እንደጋዜጣው አታርጅ በለው ብየው ተለያየን፡፡ ከዛ በሃላ ተስፋለም በፀጥታ ሀይሎች እንደተያዘ የሰማሁት ቅዳሜ ጠዋት ፌስቡክ ላይ ነው፡፡

Read 4264 times