Print this page
Saturday, 03 May 2014 12:12

የጋዜጠኞችና የፀሐፊዎች እስር የአፈና ዘመቻ ነው በሚል ተወገዘ

Written by  አበባየሁ ገበያው እና አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(7 votes)

            ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጋዜጠኞችና የድረገፅ ፀሃፊዎች (ጦማሪዎች) በአንድ ጊዜ ተይዘው ለእስር ሲዳረጉ የአሁኑ የመጀመሪያው ነው፡፡ እስሩን በመቃወም ኢንተርኔት ተጠቃሚ ኢትዮጵያዊያን ከእስከዛሬው ሁሉ የበለጠ ድምፅ ማሰማታቸውን ቢቢሲ የዘገበ ሲሆን፤ ዋና ዋናዎቹ ዓለማቀፍ የመብት ተሟጋችና የፕሬስ ነፃነት ተቋማት “የአፈና ዘመቻ ነው” በማለት አውግዘዋል በመንግስት ላይ ተፅእኖ እንዲያሳድሩ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጥሪ የቀረበላቸው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ጆን ኬሪ እስረኞቹ መፈታት ይገባቸዋል ብለዋል፡፡ የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽነር በበኩላቸው ሀሳባቸውን በነፃነት በመግለፃቸው ብቻ ነው የታሰሩት በማለት የመንግስትን እርምጃ ተቃውመዋል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ግን የፕሬስ ነፃነት ይከበር የሚል ጥቅል መግለጫ ከማውጣቱ በስተቀር ስለታሰሩት ሰዎች አላነሳም፡፡ የጋዜጠኞችና የፀሐፊዎች እስር አሳሳቢነት ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን በዓለም ደረጃ ሲያነጋግር ቢሰነብትም፣ የመንግስት አካላትና የመንግስት ሚዲያ አንዳችም መረጃ ያልሰጡበት ምክንያት አልታወቀም፡፡ ጋዜጠኞችና ፀሐፊዎች ላይ ክስ የሚቀርብ ከሆነ በእስር ማቆየት እንደማያስፈልግና በዋስ መለቀቅ እንዳለባቸው የፕሬስ ህጉ ላይ የተጠቀሰ ቢሆንም፤ ዘጠኙ ጋዜጠኞች ፀሐፊዎች የዋስ መብት አልተፈቀደላቸውም፡    
ባለፈው ሳምንት አርብ ምሽትና ቅዳሜ ካሉበት በፀጥታ ሃይሎች ተይዘው የታሰሩት ጋዜጠኞችና ፀሃፊዎች፤ ኢትዮጵያ ውስጥ አለመረጋጋትን ለመፍጠር አስበዋል የሚል ጥርጣሬ እንዳለው ፖሊስ ለፍ/ቤት ገልጿል፡፡ በዚህም ታሳሪዎቹ ከዓለም አቀፍ መብት ተሟጋች ተቋም ጋር በገንዘብና በሃሳብ በመተባበር ወይም በኢንተርኔት ማህበራዊ ድረገፆችን በመጠቀም ተንቀሳቅሰዋል-ብሏል ፖሊስ፡፡ የትኛው አለማቀፍ የመብት ተቋም እንደሆነ በስም ያልገለፀው ፖሊስ፤ ታሳሪዎቹ አለመረጋጋትን ለመፍጠር የፈፀሙት ተግባር ካለም ምን ምን እንደሆነ አልጠቀሰም፡፡ ፖሊስ የምርመራ ጊዜ እንደሚያስፈልገው በመጠየቁ በእስር እንዲቆዩ የተደረጉት ጸሐፊዎችና ጋዜጠኞች ከህግ ባለሙያ ወይም ከቤተሰብ ጋር እንዲገናኙ አልተፈቀደላቸውም ተብሏል፡፡
ሦስቱ ጋዜጠኞች፣ በቀድሞው አዲስ ነገር፤ የእንግሊዝኛው ፎርቹንና አዲስ ስታንዳርድ ላይ በፍሪላንሰርነት ይሰራ የነበረው ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ፣ የአዲስ ጉዳይ መፅሄት ከፍተኛ አዘጋጅ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ የቀድሞ አዲስ ዘመን ጋዜጠኛ ኤዶም ካሣዬ ናቸው፡፡ ኤዶምን ጨምሮ አቤል ዋበላ፣ ዘላለም ክብረት፣ በፍቃዱ ኃይሌ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ እና አጥናፈ ብርሃኔ “ዞን ዘጠኝ” በመባል የሚታወቁ የድረገፅ ፀሐፊዎች (ጦማሪዎች) ናቸው፡፡
ግራ የገባቸው የጋዜጠኛ ማህበራት
መንግስት አፈናውን ለማጠናከር በአዲስ ዙር የእስር ዘመቻ እያካሄደ ነው በማለት ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋችና የፕሬስ ነፃነት ድርጅቶች ተቃውሟቸውን ቢገልፁም፣ የአገር ውስጥ የጋዜጠኞች ማህበራት በበኩላቸው ግራ በመጋባት ሲዋልሉ ነው የሰነበቱት፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጋዜጠኞች ህብረት ሊቀመንበር አቶ አንተነህ አብርሃም፤ ባለፈው ማክሰኞ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “ታሣሪዎቹ ጋዜጠኛ ስለመሆናቸውና ከስራቸው ጋር በተገናኘ ስለመታሠራቸው ማጣራት ስላለብን፤ ለጊዜው ምንም ዓይነት የአቋም መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ለመስጠት ይቸግረናል” ብለዋል፡፡
ከአንድ ቀን በኋላ ሐሙስ እለት ማህበሩ ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ ግን፤ መንግስት ጋዜጠኞቹ እና ጦማሪዎቹ ስለታሠሩበት ጉዳይ ይፋዊ መግለጫ አለመስጠቱ እንዳሣሠበው አመልክቷል፡፡ “በጉዳዩ ላይ የመንግስት ዝምታ አሳስቦናል፤ ከመንግስት የጠራ መረጃ እንፈልጋለን” ያሉት አቶ አንተነህ፤ “ፍ/ቤት ስለቀረቡበት ሁኔታም ከመንግስት የጠራ መረጃ አለማግኘታችንም ያስጨንቀናል” ብለዋል፡፡ ማህበራቸው እንዲሁም የምስራቅ አፍሪካ ጋዜጠኞች ህብረትና የአለማቀፉ የጋዜጠኞች ፌደሬሽን፣ የእስረኞቹን ጉዳይ በትኩረት እንደሚከታተሉት አቶ አንተነህ ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል “ዩኔስኮ ጦማሪዎች ጋዜጠኞች አይደሉም ብሎ ፈርጇል፣ በኢንተርኔት የማህበራዊ ድረገፅ ሚዲያውም ሃላፊነት የሚሠማው አይደለም፤ ከዚህ አንፃር ለእነዚህ አካላት ጥበቃ ማድረግ እንዴት ይቻላል?” ሲሉ ይጠይቃሉ፤ አቶ አንተነህ፡፡
“ጋዜጠኞቹ የታሠሩት ከሙያቸው ውጪ በሆነ ጉዳይ ከሆነ መንግስት በህግ መጠየቅ ይችላል፤ ጉዳዩን ግን እንከታተላለን፡፡ ከሙያቸው ጋር በተገናኘ ከሆነም ጠበቃ አቁመን ከመከራከር ባለፈ፤ የአለማቀፍ ጋዜጠኞች ህብረትን አስተባብረን መንግስትን ስለጉዳዩ አጥብቀን እንጠይቃለን” ብለዋል አቶ አንተነህ፡፡
የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ መሠረት አታላይ በበኩላቸው፤ “እኛ በጋዜጠኝነት አናውቃቸውም፤ ጋዜጠኞችም አይደሉም፤ ብሎገሮች (ጦማሪዎች) ናቸው፤ በእነሱ መታሠር ጉዳይ እኛ የምናውቀው ነገር የለም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
“ሠሞኑን ከታሠሩት መካከል በጋዜጠኝነት የማውቀው ተስፋለም ወልደየስን ብቻ ነው” ያሉት የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ ወንድወሰን መኮንን፤ “ስለ ዞን 9 ፀሀፊዎች የጠራ መረጃ የለኝም፤ ጦማሪዎች በዩኔስኮ ድንጋጌ መሠረት ጋዜጠኛ አይባሉም፣ ስለጦማሪያኑ መሟገት ቢቸግረንም ስለጋዜጠኛው እስር እና ስለጉዳዩ መንግስት ለህዝብ መግለጽ አለበት” ብለዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በሽብርተኝነት እየተከሰሱ የተፈረደባቸው ጋዜጠኞችም፤ ለመንግስት ያቀረቡት የምህረት ጥያቄ ከግንዛቤ ገብቶ፤ ከእስር እንዲለቀቁ መንግስትን እንደሚጠይቁ አቶ ወንድወሰን ተናግረዋል፡፡
ጋዜጠኞቹና ፀሃፊዎቹ መታሰራቸው እንዳሳሰበው የገለፀው አዲስ በመቋቋም ላይ ያለው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ (ኢጋመ)፤ መንግስት የታሰሩበትን ጉዳይ ለህዝብ ይፋ እንዲያደርግና ጋዜጠኞቹ እንዲለቀቁ ጠይቋል፡፡   
ጠንካራ የጋዜጠኛ ማህበር በሌለበት አገር፣ ጋዜጠኞችና ጦማርያን ለእስር መዳረጋቸው አሳዛኝ ነው ያሉት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምህር ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ ሃሳብን በነፃነት መግለፅ ባልተከበረበት ሀገር የፕሬስ ቀንን ማክበር ለውጭ መንግስታት ድጋፍ ማግኛ ካልሆነ በስተቀር ትርጉም የለሽ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ “የፕሬስ ቀንን ማክበር ያለበት ፕሬስ ነበር፤ ነገር ግን እንኳን ሊያከብር ህልውናውንም አላረጋገጠም” ብለዋል ምሁሩ፡፡
የጋዜጠኞቹ እና የጦማርያኑ እስራት ሃሳብን መግለፅ እንደ አደጋ የሚታይበት ጊዜ መምጣቱን አመላካች ነው ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ በውይይትና በክርክር፣ በውድድርና በፉክክር ሳይሆን የአንድን ቡድን ሃሳብ ብቻ የበላይ በማድረግ ሌላው ፀጥ እንዲል እየተደረገ ነው ሲሉ ይተቻሉ፡፡
ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ባለሙያ በሰጡት አስተያየት፤ የመረጃ ነፃነትን ለመደንገግ የወጣው አዋጅ፣ ማንኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሃሳቡን የመግለፅ ነፃነት እንዳለው ይጠቅሳል ብለዋል፡፡ “ማንኛውም ሰው ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት የመሰለውን አመለካከት የመያዝ፣ ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት ሃሳቡን የመግለጽ ነፃነት አለው፡፡ ይህ ነፃነት ከሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ ወሰን ሳያደርግለት በቃል ሆነ በጽሑፍ ወይንም በህትመት በስነ ጥበብ መልክ ወይንም በመረጠው፣ ለማንኛውም የማሰራጫ ጣቢያ ማንኛውም ዓይነት መረጃ የመሰብሰብ፣ የመቀበል ሃሳብ ያካትታል፡፡ ነገር ግን የጦርነት ቅስቀሳዎች፣ ሰብዓዊ ክብርን የሚነኩ የአደባባይ መግለጫዎች በህግ የሚከለከሉ ይሆናል ይላል” ሲሉም የህግ ባለሙያው አስረድተዋል ፡፡
የጋዜጠኞቹንና ጦማሪያኑን መታሠር ተከትሎ መግለጫ ያወጣው አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችንና ፖለቲከኞችን የማሠር ልምድ እንዳላት ጠቅሶ፤ በአዲስ የአፈና ዘመቻ የታሰሩት ጋዜጠኞችና ጦማሪዎች  በአስቸኳይ እንዲለቀቁና አለማቀፉ ህብረተሰብም ግፊት እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
ተቀማጭነቱን በኒውዮርክ ያደረገው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (CPJ) በበኩሉ፤ “ጋዜጠኞቹንና ጦማሪያኑን በማሠር የኢትዮጵያ መንግስት ሠላማዊ የሆነውን ሃሳብን የመግለጽ መብትን ወደ ወንጀል እየቀየረው ነው” በማለት ዘጠኙ ጋዜጠኞች በአስቸኳይ እንዲለቀቁ ጠይቋል፡፡
“ዞን 9” በሚል የሚታወቁት ጦማሪያን፣ የተለያዩ ዜናዎችንና ትችቶችን የሚያቀርቡ፣ የሀገሪቱ የፕሬስ አፈና የወለዳቸው ስብስቦች ናቸው ያለው ይሄው ተቋም፤ በመንግስት በኩል በደረሰባቸው ወከባ ለበርካታ ወራት ስራቸው ተስተጓጉሎ እንደነበር ገልጿል፡፡ እንደገና ስራቸውን ለመጀመር ማቀዳቸውን በገለፁበት ሳምንት ነው የታሰሩት ብሏል ተቋሙ፡፡
ጋዜጠኞችን፣ የሚዲያ ተቋማትንና አሳታሚዎችን በአባልነት ያሰባሰበው የዓለም ፕሬስ ኢንስቲትዩት (IPI) በበኩሉ፤ ባለፈው ህዳር ወር የልዑካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ እንደተላከ ገልፆ፤ ከመንግስት አካላትና ከጋዜጠኞች ጋር እንደተወያየ በመጠቆም፣ የአገሪቱ ሁኔታ አሳሳቢ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ብሏል፡፡ በሽብር ህጉ ሰበብ ጋዜጠኞች መታሰራቸውን ሲቃወም እንደነበር ተቋሙ አስታውሶ፤ አሁን እንደገና አዲስ የእስር ዙር መጀመሩን አውግዟል፡፡
ተመሳሳይ ውግዘት የሰነዘረው ሂዩማን ራይትስ ዎች በበኩሉ፤ ከአፍሪካ ውስጥ ከፍተኛ ግምት ከሚሰጣቸው አንዷ ኢትዮጵያ መሆኗን ጠቅሶ፣ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ፤ የዲሞክራሲና የመብት አከባበርን እንደወትሮው ችላ ማለት አይኖርባቸውም ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ የፕሬስ ህግና የመረጃ ነፃነት አዋጅ በተዘጋጀበት ወቅት በመንግስት ፈቃድ በሙያ ምክርና በውይይት አስተባባሪነት እንዲሳተፍ የተደረገው አርቲክል 19 የተሰኘው ዓለም አቀፍ ተቋምም እንዲሁ እስሩን አውግዟል፡፡
ብዙዎች የመብትና የፕሬስ ነፃነት ተቋማት በኢትዮጵያ እንዳይሰሩ እየታገዱ ጥቂት መቅረታቸውን የገለፀው አርቲክል 19፤ ሳይታገዱ ከቆዩት ተቋማት መካከል አንዱ በመሆኔ የፕሬስ ነፃነትን በሚመለከት ለተባበሩት መንግስታት ሪፖርት የማቅረብ በሙያውና ህጋዊ ትንታኔ በዓለም ደረጃ ከፍተና አክብሮትን እንዳተረፈ የሚነገርለት አርቲክል 19፤ ለመንግስታት የህግ ማሻሻያ ሀሳብ በማቅረብና ለጋዜጠኛው የስልጠና ድጋፍ በመስጠት ላይ ያተኮረ በመሆኑ ከመንግስት አካላት ጋር ፊት ለፊት ፍጥጫ አይታይበትም፡፡ ለብዙ ጊዜ በኢትዮጵያ ሳይታገድ የቆየውም በዚህ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡ ባለሙያዎችን እየላከ ጋዜጠኞች ስልጠና እንዲያገኙ ይተባበር እንደነበረም የሚታወቅ መሆኑን ተቋሙ አመልክቶ፣ ለበርካታ ጊዜያት ከኬንያ እየተመላለሰ ስልጠና የሚሰጥ ባለሙያ የዛሬ ወር ገደማ በፖሊስ ተይዞ ከአንድ ቀን በኋላ ወደ ኬንያ እንዲባረር ተደርጓል ብሏል፡፡
ከኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋር ሊወያዩበት እንደሚገባ ገልጿል፡፡ ጆን ኬሪ በሰሞኑ ጉብኝታቸው በኢትዮጵያ የፕሬስ አፈና መባባሱ እንዳሳሰበው በመግለፅም፣ የታሰሩት ጋዜጠኞችና ፀሐፊዎች እንዲለቀቁ ጠይቋል፡፡ ፔን የተሰኘው የፕሬስ ነፃነት ማህበርም እንዲሁ ከተመሳሳይ ጥሪ ጋር፤ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ፤ ከኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋር ሊወያበት እንደሚገባ ገልጿል፡፡ ጆን ኬሪ በሰሞኑ ጉብኝታቸው ከመንግስት ባለስልጣናት ጋር የሶማሊያና የሱዳን ግጭት እንዲሁም የኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን በመጥቀስ በሰጡት የማጠቃለያ መግለጫ ላይ የጋዜጠኞቹና የፀሐፊዎቹን መታሰር አልጠቀሱም፡፡ ጉዳዩ የተነሳው ከጋዜጠኞች በቀረበ ጥያቄ ነው፡፡ ጆን ኬሪ በሰጡት ምላሽ፤ የታሰሩት ጋዜጠኞችና ፀሐፊዎች ሊለቀቁ ይገባል ብለዋል፡፡ የዩኤን ሰብዓዊ መብት ኪሚሽነር ከሰሞኑ በጋዜጠኞችና በድረገጽ ጸሃፊዎች ላይ እየተወሰደ ያለው የእስራትና የማስፈራራት እርምጃ እጅጉን እንደሚያሳስባቸው ገልጸው፣ መንግስት ሃሳባቸውን በነጻነት የመግለጽ መብታቸውን ስለተጠቀሙ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን ጋዜጠኞችና የድረገጽ ጸሃፊዎች እንዲፈታ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
መንግስት በስራ ላይ ያዋላቸው የጸረ ሽብር፣ የሲቪል ማህበረሰብና የመገኛኛ ብዙሃን ህጎች፣ የዜጎችን ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ፣ የመደራጀትና የመሰብሰብ መብቶች ለማፈን እየተጠቀመባቸው ነው ያሉት ፒላይ፣ ህጎቹን ከአለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ጋር በሚጣጣም መልኩ እንዲያሻሽልም ለኢትዮጵያ መንግስት ጥያቄ አቅርበዋል፡፡

Read 5196 times